ዛሬ የምንጓዘው ከሜክሲኮ ወደ አየር ጤና ነው፡፡ ዛሬም፣ ነገም እንጓዛለን፡፡ በሒደት ላይ ነን ማለት ነው፡፡ ወያላው መጥራት ከመጀመሩ ታክሲው ውስጥ የገባን ተሳፋሪዎች ሁለት ብቻ ነን። ታክሲው እስኪሞላ ከወዲያ ወዲህ የሚመላለሰውን በማየት እየተደበርን ነው። ከትርምስ መሀል ቁም ነገር መልቀም በዋዛ ፈዛዛ ጊዜን ከመሸኘት በእጅጉ የተሻለ ነው። ለነገሩ ዘንድሮ ‹‹ቀላል›› ከሚባለው ቃል ሌላ ሲጠሩት ለአፍ ቀለል የሚል ነገር እያጣን ነው። ጊዜው የውድድር ነው ካልን ወዲያ ‹‹ከረር›› እንጂ ‹‹ቀለል›› የሚል ነገር መፈለጋችን በራሱ እንዴት ከባድ እንደሆነ ተመልከቱ። ‹‹በቃ መንገዱ ተጨናንቆ መተላለፊያ ጠፋ እኮ፡፡ ምናለበት ያኛው ወደ እዚያ አስፍቶ ቢያሳልፈው?›› ይላል ሾፌሩ በሩቅ መንገዱን ዘግተው የሚነታረኩ የከባድ መኪና አሽከርካሪዎችን እያየ። በጥሩንባ ጩኸት አካባቢው ይደበላለቃል። የትራፊክ ፖሊስ ፊሽካ ያለማቋረጥ ይነፋል። ወያላው ደግሞ በሻከረ ድምፁ፣ ‹‹ዝሆኖች ተጣልተው ሰበሩት ድንበሩን…›› እያለ ያቀነቅናል፡፡ ‹‹ምንጩ ያልታወቀ ሀብት ዋጋና ክብር በሚያሰጥበት በዚህ ዘመን፣ የትንንሽ ነፍሶች ጩኸት ከዜማ አልዘል ብሎ ቀርቶ ይሆን?›› እያለ አንደኛው ያጉረመርማል፡፡ ወሬ ሊጀመር ነው!
አሁን የተሳፋርነው ስድስት ገደማ ደርሰናል። አንዲት ወይዘሮ ዘንቢላቸውን ራሳቸው ይዘው አንድ ወጠምሻን ደግሞ መለስተኛ የሶፋ ጠረጴዛ አሸክመው ወደ ታክሲው ተጠጉ። ወያላው ፈንጠር ብሎ ከቆመበት ቦታ ሮጦ መጣ። ዞር ብለው እያዩት፣ ‹‹ምነው አንተ እንዲህ የሰው ቀልብ የምትገፈው? እንደምታስከፍለኝ ሳትነግረኝ አውቃለሁ፡፡ ለዕቃዬ አሁን ቦታ ትሰጥልኛለህ አትሰጥልኝም?›› ብለው ሲጮኹበት የሚናገረው ጠፍቶት አተኩሮ ያያቸዋል። እንዲህ በር ዘግተው በቆሙበት አንድ ወንድና ቦርሳ ያነገበች ታዳጊ ይቅርታ ጠይቀው ገብተው ቦታ ያዙ። ወይዘሮዋ በጣም መበሳጨት ጀመሩ። ‹‹ባለጌ፣ ስድ ሁሉ። አሁን እናት ቆማ እናንተ ገብታችሁ ስትቀመጡ አታፍሩም? በአጭር ቅሩ በአጭር ያስቀራችሁ…›› እያሉ እርግማኑን ሲያወርዱት ልጆቹ ደንግጠው ተያዩ። ወይዘሮዋ ከአሰልቺ ንጭንጭና ንትርክ በኋላ ዕቃቸው ከላይ ተጭኖ ገብተው ተሳፈሩ። አጠገባቸው የተቀመጠ ጎልማሳ ቆየት ብሎ፣ ‹‹ለመሆኑ እንዲህ በትንሽ በትልቁ ተቃጥለው ይችሉታል?›› ብሎ ጠየቃቸው። ‹‹ምን አባቴ ላድርግ ብለህ ነው? ጋኖች አለቁና ምንቸቶች ጋን ሆኑ ይሉ ነበር አባቴ (የአባታቸውን ስም ከእነ ደጃዝማችነት ማዕረጉ ጠርተው)፡፡ ለመሆኑ ሰው አለ እንዴ አሁን? ለመሆኑ ዘመንስ አለ?›› ብለው ሳግ በሚተናነቀው ድምፅ መልሰው ጠየቁት። ‹‹ለማንኛውም ረጋ ይበሉ በሽታውም ይደራረባል…›› እያለ ለደቂቃዎች መከራቸው። ትልቅ ነኝ ባዩ ሲያንስ፣ ሙሁር ነኝ ባዩ ግራ ሲጋባ፣ አልሚ ነን ባዮች ሲያከስሩ የተቃርኖ ሕግ በሕይወት ውስጥ ሳይዛነፍ ጉዞአችን ይቀጥላል። ትውልድ ይመጣል ትውልድ ይሄዳል፡፡ ትልቁ ታናሹን እያበረታታ ከማስተማር ይልቅ መርገምና ማጥላላት ለማን ይጠቅማል? ለማንም!
ታክሲያችን ከተሠለፈበት ተራ ወጥቶ ዋና መስመሩን መያዝ ከመጀመሩ፣ ‹‹ቆይ በፈጠረህ አንዴ… ሾፌር አንዴ አንዴ…›› የሚል ድምፅ ከኋላ መቀመጫ ተሰምቶ ታክሲው ቆመ። ሁላችንም ወደ ኋላችን ስንዞር መስኮት ለመክፈት እየታገለ በዓይኑ አንድ ጋዜጣ አዟሪ የሚጣራ ወጣት ተሳፋሪ አስተዋልን። አዟሪው አየሮጠ መጥቶ፣ ‹‹ምን ልስጥህ?›› ሲለው፣ ‹‹የስፖርት ጋዜጣ…›› አለው፡፡ ወያላው ይኼኔ ገነፈለበት። ‹‹ምነው ለዚህ ነው ሥራ የምታስቆመን? የስንት ሰው ጊዜ እኮ ነው እያቃጠልክ ያለኸው?›› አለው ዓይኑን አጉረጥርጦ። ይኼኔ ከኋለኛው መቀመጫ ፊት ላይ ከተቀመጡ ጓደኛማቾች አንደኛው፣ ‹‹ምን ጊዜያችንን ብቻ? የግድባችን ሦስተኛ ዙር ሙሌት ተጠናቆ ዕልል እያልን የአውሮፓ ቅሪላ ማባረር ምን የሚሉት ነው›› ሲል አንደኛው፣ ‹‹የግድቡ ሁለተኛ ተርባይን ኃይል ማመንጨቱን ስላልሰማ ነው ተፋታው…›› አለ ሌላው። ወጣቱ ጋዜጣውን ገዝቶ መስኮቱን ከመዝጋቱ ሾፌሩ በንዴት ይመስላል ታክሲውን ያከንፈው ጀመር። ‹‹አይ የእኛ ነገር በአገር ጉዳይ አንድ መሆን ሲያቅተን ያሳዝናል፡፡ በፖለቲካውስ እሺ መቼም ፈጣሪ ሰፊ ሆድ እስኪሰጠን ይሁን። ቢያንስ ግን ምናለበት ለአገር ጠቃሚ የሆነ የልማት ሥራ ላይ አንድ ሐሳብ የማይኖረን?›› ሲሉ ወይዘሮዋ፣ ‹‹ምን እናድርግ ብለው ነው ቀልባችን እየተዘበራረቀ ነው….›› አላቸው አንድ ታዳጊ ወጣት። እንዲህ እርስ በርስ ብንተዛዘብስ!
‹‹ይታይሃል? ይታይሃል ይኼኛው? እርግጠኛ ነኝ የዚህ ሕንፃ ዲዛይን በባለሙያ አይደለም የተሠራው። ተመልከት የፍሳሽ መስመሩን በውጭ በኩል አድርገው እንዴት እንደሠሩት?›› ትለዋለች ቦርሳ አንጋቿ ታዳጊ ለጓደኛዋ። እርሱም ሐሳቡንና ግምቱን መልሶ ይነግራታል። ‹‹እኛ እኮ እንዲያው ነው ተማርን የሚባለው፡፡ ዘመኑ ከተራቀቀበት የግንባታ ዕድገት አንፃር ስንታይ አለን ይባላል?›› ቢላት፣ ‹‹ትቀልዳለህ? እዚህ አገር ምንም ነገር ብትችል እንድታስብ የምትገደደው ሌላው ማሰብ እስከቻለበት ደረጃ ድረስ ብቻ ነው። አለቀ ደቀቀ…›› አለችው። በአነጋገራቸው እየተገረምን ጨዋታቸውን ስናዳምጥ ብዙ ቆየን። ድንገት፣ ‹‹ተመልከት እንግዲህ ገና በዚህ ዕድሜያቸው አቃቂር ማውጣቱን እንዴት እንደሚችሉበት…›› ይላሉ ወይዘሮዋ በታዳጊዎቹ ላይ ንዴታቸው አልበርድ ብሎ። ‹‹የሕንፃ ግንባታ የዕድገት ጫፍ ይመስል ታዳጊው ሁሉ የሚመለመለው ለዚሁ ሆነ በቃ?›› ብሎ ከሾፌሩ ኋላ የተቀመጠ ወጣት አጠገቡ የተቀመጠችውን ቀዘባ ሲጠይቃት ሰማን። ‹‹ይኼማ ድልድይና የባቡር መስመር ጭምር የሚዘረጉ ዜጎች ለማግኘት ታስቦ ነበር። ለእንጀራ እንጂ ለሙያ ፍቅር የሚማር እየጠፋ፣ መንግሥትም የጥራቱን ነገር ችላ ብሎት ቻይና ተንሰራፋብን እንጂ…›› ብላ መለሰችለት። ታክሲ ውስጥ አንድ ሐሳብ ተነስቶ ሳይጠናቀቅ ሌላ ይተካና መንገዳችን እያጠረ እንጓዛለን። ሒደት ነውና ካለፈው በመማር ለሚመጣው መዘጋጀት ግድ እየሆነብን ነው፡፡ ምን ይደረግ ታዲያ!
መዳረሻችን እየተቃረበ ነው። ወሬው ቀጥሏል። ‹‹ዛሬ ሁሉም ነገር በምርጫ ሆኗል። ለነገሩ ጥንትም የሰው ልጅ ሲፈጠር ተፈጥሯዊ ሆኖ የተሰጠው የመራጭነት መብት ነው…›› እያለ ጎልማሳው ለወይዘሮዋ ያስረዳል። ‹‹ጠቅላይ ሚኒስትራችን የህዳሴ ግድቡ ሁለተኛው ተርባይን ሥራ ሲያስጀምሩ የተናገሩትን ሰማህ?›› ይለዋል ሦስተኛው ወንበር ላይ ያለው ጎልማሳ ጓደኛውን። ‹‹አዎ ሰምቻለሁ። ዋናው ቁምነገር አገሪቱ ምን ዓይነት ትውልድ እያፈራች ነው የሚለው ጉዳይ ሊታሰብበት ይገባል፡፡ በህዳሴ ግድቡ ምክንያት ድልና ዕድል ያሉትንም ሰምቻለሁ፡፡ ዕድለኛ ትውልድ ባለድል ሲሆንም ደስ ይላል፡፡ ነገር ግን ብዙ ነገሮች ይቀሩናል፡፡ ሥራ ለመቀጠር፣ ስኮላርሺፕ ለማግኘት፣ የተሻለ ኃላፊነት ላይ ለመቀመጥ፣ ጥቅማ ጥቅም ለማጋበስ ብሔር እንደ መሥፈርት የሚቀመጥበት ደረጃ ላይ እንገኛለን፡፡ አገር የምታድገው በዚህ መንገድ እንዳልሆነ አስረግጠው ቢነግሩልን መልካም ነበር…›› እያለ ቁና ቁና ተነፈሰ፡፡ አንዱ ደግሞ፣ ‹‹ኧረ ወሬ የሚባል ነገር ሰልችቶናል። አፋችን ከሥራችን እየቀደመ መስሎኝ ከብሔርተኝነት አስተሳሰብ መውጣት አቅቶን እንደ ግመል ሽንት ወደኋላ የምንለው…›› አለ ወያላው። ሾፌሩ ደግሞ፣ ‹‹አንተም እኮ እንዲህ ወሬው ሲጦፍ ተቺ ትሆናለህ እንጂ መደብህ እዚያው እንደሆነ የማላውቅ እንዳይመስልህ…›› ሲለው፣ ‹‹በዚህ ምድር ማንም የማይለወጥ ስለሌለ መለወጤን ስነግርህ በከፍተኛ ኩራት ነው…›› ብሎት ከደረቱ ሥር ያለውን አረንጓዴ፣ ቢጫና ቀይ ዓርማ ሲያሳየው ሳቅ በሳቅ ሆንን፡፡ እንሳቀው እንጂ!
ታክሲዋ ጠርዝ ታካ ልትቆም ስትታገል ጠያቂው ጎልማሳ፣ ‹‹ለማንኛውም ዓለም ዛሬ ከመቼውም ጊዜ በላይ በብዙ አማራጮች ተሞልታለች፡፡ መምረጥ መብት ሲሆን፣ ምርጫ ደግሞ ተዓማኒና ንፁህ መሆን ይገባዋል፡፡ ዳሩ መመራረጥ ብቻ ዋጋ የለውም። ለተመረጡለት ሕዝብ ሠርቶ ማሳየት ወሳኝ ነው። ከፉከራ በፊት ሥራ ይቅደም ብለህ ጥቅስ ለጥፍ ወያላ…›› ሲለው ወያላው ራሱን በእሺታ ነቀነቀ፡፡ አንዱ ደግሞ፣ ‹‹እንዲህ እየተሰበሰቡ ኮሚክ ነገር ሲያበዙ ስትሰማ ‹ደግሞ ምን አሉ?› የሚል መጠነኛ ስክሪፕት ጫር ጫር ብታደርግ አሪፍ ኮሜዲ ፊልም አይወጣውም?›› አለ፡፡ ወይዘሮዋ ዘንቢላቸውን ጠበቅ አድርገው ይዘው እየተዘገጃጁ፣ ‹‹ማነህ ወያላው?›› ብለው ጠሩት፡፡ ወያላው ‹‹አቤት እማማ?›› ሲላቸው፣ ‹‹ከአቅም በላይ ማሰብ ያደርሳል ከሰበብ የሚባለውን የድሮ ጥቅስም እንዳትረሳ…›› ሲሉት ታክሲው በሳቅ ተናጋ፡፡ ወይዘሮዋ በሳቃችን መሀል፣ ‹‹አዳሜ በልክሽ አታቅጂ ከዚያ ደግሞ የሰበብሽ ብዛቱ…›› እያሉ ከመቀመጫው ሲነሱ ሳቃችንን አልጨረስንም ነበር፡፡ በዚህ መሀል ግን ወያላው ‹‹መጨረሻ!›› ሲለን፣ የሰበባችን ብዛቱን እያሰብን ነው መሰል ሳቃችን አላቋረጠም ነበር። መልካም ጉዞ!