የኢትዮጵያ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ከዚህ ዓለም በሞት ከተለየ እሑድ ነሐሴ 15 ቀን 2014 ዓ.ም. አሥር ዓመት ይሞላዋል፡፡ አቶ መለስ ለአገሪቱ ታላላቅ ሥራዎችን ከሠሩ መሪዎቻችን ተርታ የሚሠለፍ ሰው ነበር፡፡ መሪዎቻችንን ለማድነቅም ሆነ ለመኮነን አንድ ሰበዝ መዝዞ በማውጣት መሆን የለበትም፡፡ የሠሯቸው በጎ ሥራዎች፣ ጠንካራ ጎናቸውና ያበላሿቸው ነገሮች ማለትም ደካማ ጎናቸው በዝርዝር እየተመዘገቡ፣ በሚዛን እየተቀመጡ ነው ማለፍ መውደቃቸውን ማረጋገጥ ያለብን እላለሁ፡፡
አንዳንድ ሰዎች አቶ መለስ አገሪቱን ያለወደብ አስቀርቷታል ብለው ይኮንናሉ፡፡ በወቅቱ የኢትዮጵያ መንግሥትና የጦሩ ሠራዊት በደንብ የተደራጀና ጠንካራ ስላልነበር አሰብ ወደብ ታስፈልገናለች የሚል አቋም መለስ ቢይዝ ኖሮ ኢትዮጵያና ኤርትራ ጦር ይማዘዙ ነበር፣ ምናልባትም ኢትዮጵያ ሽንፈት ይደርስባት ነበር፡፡ መለስ ያንን ነው ያስወገደው ኮናኞቹ ‹‹አይ መሬት ያለሰው›› እንደሚባለው ያንን ያስተዋሉ አይመስልም፡፡
አንዳንዶች ደግሞ ዘረኛነትንና መከፋፈልን ያመጣብን እሱ ነው ይላሉ፡፡ ይኼ አስተያየት የተሳሳተ ለመሆኑ ዓይነተኛ ማስረጃው በሕገ መንግሥቱ መግቢያ ‹‹ጥቅማችንን፣ መብታችንና ነጻነታችንን በጋራና በተደጋጋፊነት ለማሳደግ አንድ የኢኮኖሚ ማኅበረሰብ የመገንባቱን አስፈላጊነት›› አምነናል የሚለውን፣ በአንቀጽ 2 ሰንደቅ ዓላማው ‹‹በእኩልነትና በአንድነት ለመኖር›› ያለንን ተስፋ የሚያንጸባርቅ ይሆናል የሚለውን፣ በአንቀጽ 41 ‹‹ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በአገሪቱ ውስጥ በማንኛውም የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ የመሰማራትና ለመተዳደሪያ የመረጠውን ሥራ የመሥራት መብት አለው›› የሚለውን ድንጋጌ ማየት ብቻ ይበቃል፡፡
የአገሪቱ አጠቃላይ ፖሊሲ የተቀየሰበትን ይኼን ሕገ መንግሥት ካለመረዳት፣ ካለማወቅ፣ ካለመገንዘብ አንዳንድ ሰዎች ‹‹ይኼ የኔ ክልል ነው፣ ውጣልኝ›› ቢሉ ወይም ‹‹የኔ ብሔረሰብ ካንተ ይበልጣል›› እያሉ አጉል ቢኩራሩ፣ ቢያስቸግሩ መለስ ያመጣብን ጣጣ ነው ማለት እንዴት ይቻላል፡፡
አሉ ደግሞ አንዳንድ ሰዎች መለስ ‹‹የአክሱም ሐውልት ለወላይታው ምኑ ነው?›› ብሎ ተናግሯል ይላሉ፡፡ ይኼን በእርግጥ ተናግሮ ከሆነ እንዲህ መናገር ስህተት ነው ማለት ይቻላል፡፡ ነገር ግን ከላይ እንደጠቆምኩት ይቺን ተናግሯል በማለት አካብዶ (በማጦዝ) የመለስን አስተዋፅኦ ዝቅ ለማድረግ መሞከር አያስኬድም፡፡ ሌሎችም ስህተቶች ካሉ (ይኖራሉም) እንመዝናቸው፣ እናነጻጽራቸው ነው የምለው፡፡
ወደ መለስ ጠንካራ ጎን መለስ (ለ ይጠብቃል) ስል ታሪክ ጸሐፊዎች የበለጠ ዝርዝር አርገው ያቀርቡታል ብዬ አምናለሁ፡፡ ሰሞኑን እልል እያልን ‹‹እንኳን ደስ አለን›› የተባባልንበትን ታላቁን የሕዳሴ ግድብ ሦስተኛ የውኃ ሙሌት እንኳን ብንወስድ ግድቡ እንዲገነባ ውሳኔ የሰጠውና መሠረት የጣለው መለስ ዜናዊ ነው፡፡ የኢትዮጵያ የቀድሞ መሪዎች ቢጠይቁም ያልተሳካላቸውን የአክሱም ሐውልት ከቆመበት ከሮማ አደባባይ ተነቅሎ ወደ እናት አገሩ እንዲመለስ ያደረገው መለስ ዜናዊ ነው፡፡ የአፍሪካ ኅብረት ዋና ከተማ ከአዲስ አበባ ተነቅሎ ወደ ሌላ አፍሪካ አገር እንዲዛወር አሳብ በቀረበ ጊዜ በጥሩ ቋንቋ ተሟግቶ ያንን ሐሳብ ያከሸፈው መለስ ነው፡፡
በኢትዮጵያ ኋላቀርነትን ለመዋጋት/ለመቅረፍ ዓይነተኛው መሣሪያ በትምህርት መስፋፋት ላይ ማተኮር ነው ብሎ ብዙ ትምህርት ቤቶችና ዩኒቨርሲቲዎች እንዲከፈቱ ያደረገው፣ አገሪቱ በመሠረተ ልማት ወደ ኋላ መቅረቷን በመገንዘብ ዘርፍ ልዩ ትኩረት እንዲያገኝ ያደረገው መለስ ዜናዊ ነው፡፡
መለስ በ‹‹ኢንተርናሽል›› መድረክ ላይ በተለይ የአየር ለውጥ ስብሰባዎች ላይ ጥቁር አፍሪካን ወክሎ ያቀርባቸው በነበሩ ሪፖርቶች ኢትዮጵያ በሌላው ዓለም ዓይን ገዝፋ እንድትታይ ያስቻላት መለስ ነው፡፡ መለስ ሌላ ነው፣ ‹‹ጁንታው›› ሌላ ነው፡፡
እኔ አንድ ተራ ኢትዮጵያዊ ነኝ መለስ ዜናዊ የሞተበትን አሥረኛ ዓመት ለማስታወስ ለአገር ያበረከተውን፣ ቶሎ በአዕምሮዬ የመጣውን ለማስፈር ደፈርኩ እንጂ ሌላው የታሪክ ጸሐፊ ብዙ በጣም ብዙ እንደሚያሰፍር እርግጠኛ ነኝ፡፡
ፈጣሪ ነፍሱን በገነት ያኑር!
በዛወርቅ ሽመላሽ (ኤዲኤፍ)