የመኖርያ ቤት ኪራይ መጨመርም ይሁን ተከራይን ማስወጣት የሚከለክለው ደንብ ለቀጣይ ስድስት ወራት ተራዘመ፡፡
የመኖርያ ቤት ኪራይ መጨመርም ይሁን ተከራይን ማስወጣት የሚከለክለው ደንብ ለሚቀጥሉት ስድስት ወራት መራዘሙን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አስታዉቋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ዜጎች ላይ የሚደርሰውን የኑሮ ጫናን ለመቀነስ በመኖርያ ቤት ተከራዮች ላይ የኪራይ ዋጋ ጭማሪ እና ተከራይን ማስለቀቅን የሚከለክል ደንብ አውጥቶ ተግባራዊ ማድረጉ ይታወቃል፡፡
ይህም ደንብ በተለያየ ጊዜ እየተራዘመ ላለፈው አንድ አመት ተግባራዊ ተደርጎ ቆይቷል፡፡
በመሆኑም የከተማ አስተዳደሩ አሁን ያለውን አጠቃላይ ነባራዊ ሁኔታ እና የህብረተሰቡን የኑሮ ጫና ከግምት ባስገባ ወቅቱን በአብሮነትና በመተሳሰብ ለማለፍ ይረዳ ዘንድ ይህ ደንብ ለሚቀጥሉት ስድስት ወራት እንዲራዘም ወስኗል፡፡
ይህንን ክልከላ በመተላለፍ ተከራዮችን የሚያስወጡ እና የኪራይ ዋጋን የሚጨምሩ አካላት ላይ ማህበረሰቡ በ 9977 አጭር ቁጥር ጥቆማውን ለከተማ አስተዳደሩ ማድረስ እንደሚችል የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደሩ አስታዉቋል፡፡