በኢትዮጵያ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ ኤምባሲ ለአንደኛ ዓመት የቱሪዝም ማሠልጠኛ ኢንስቲትዩት ተማሪዎች በቱሪዝም፣ በእንግዳ አቀባበልና በሌሎች የትምህርት ዘርፎች ዙሪያ ሥልጠና ሰጠ፣፣
ሥልጠናው የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ ኤምባሲ፣ ሃያት ሬጀንሲ ሆቴልና የቱሪዝም ማሠልጠኛ ኢንስቲትዩት በጋራ ያዘጋጁት መሆኑን፣ ነሐሴ 24 ቀን 2014 ዓ.ም. በሃያት ሬጀንሲ ለሠልጣኞች የምስክር ወረቀት ሲሰጥ ተገልጿል፡፡
የኤምባሲው የሚዲያ፣ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ኃላፊ ሚስተር ጠላል አብደላ አልአዚዚ እንደተናገሩት፣ ሥልጠናው የሴቶችን አቅም መገንባትና በጥሩ የእንግዳ አቀባበል ዙሪያ ዕውቀትን የሚያዳብር ነው፡፡
በትምህርት ላይ ለሚገኙ ሴት ወጣቶች በሥራው ዓለም ያለውን አሠራር በተግባር እንዲያገኙ ከማድረግ በተጨማሪ፣ ዓለም አቀፍ የሥራ ገበያውን እንዲቃኙ የሚያደርግ ነው ብለዋል፡፡
ለሁለት ቀናት በሃያት ሬጀንስ የተሰጠው የሙያ፣ የክህሎት ሥልጠና ለ54 የአንደኛ ዓመት የቱሪዝም ማሠልጠኛ ኢንስቲትዩት ተማሪዎች ነው፡፡
ዕድሉን ያገኘችው ወጣት መክሊት ብርሃኑ እንዳስረዳችው፣ ሥልጠናው የአገልግሎት አሰጣጥና ቱሪዝም ላይ ትኩረቱን ያደረገ ይህ ለሴቶች ጥሩ አጋጣሚ መሆኑንም ገልጻለች፡፡
ሴቶች በአብዛኛው በቱሪዝምና በሆቴል ዘርፎች ላይ እንደሚሠሩ የተናገረችው ወጣቷ፣ በሆቴል ማኔጅመንትና በሌሎች በከፍተኛ ሥራዎች ላይ ወንዶች መሆናቸውን ተናግራለች፡፡
ለሴቶች የክህሎት ሥልጠና በመስጠትና በማብቃት ሴቶችን ወደ አመራርነት ማምጣት እንደሚገባም ጠቁማለች፡፡
የቱሪዝም ማሠልጠኛ ኢንስቲትዩት ሌላኛዋ ተማሪ መቅደላዊት አብዱ እንደተናገረችው፣ ሥልጠናው በትምህርት ከሚሰጠው በተጨማሪ በሥራ ላይ ያለውን አሠራር ለማወቅ እንዳገዛቸው ተናግራለች፡፡ በተለይም ያሠለጠኗቸው ረዥም ዓመታት በሙያቸው ያገለገሉ በመሆኑ፣ ልምድና ክህሎት መቅሰማቸውን ገልጻለች፡፡
የቱሪዝም ማሠልጠኛ ኢንስቲትዩት ዳይሬክተር አቶ ጌታቸው ነጋሽ በበኩላቸው፣ የኢንስቲትዩቱ የአንደኛ ዓመት ተማሪዎች በሥልጠና መልክ ብዙ ዕውቀትና ክህሎት አግኝተዋል፡፡
በወጣት ሴቶች ላይ ያተኮረ በመሆኑ፣ ሴቶች በኢኮኖሚ ውስጥ ተጠቃሚ እንዲሆኑና የላቀ አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ የሚያግዝም መሆኑንም አክለዋል፡፡
የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ መሰል ሥልጠናዎችን በቀጣይነት ቢኖረው ኢንስቲትዩቱ የሚያስተምራቸው ወጣቶች ከዓለም የሥራ ገበያው ጋር ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ያግዛል ብለዋል፡፡
በዕለቱ ለወጣቶቹ የምስክር ወረቀት የተሰጣቸው ሲሆን፣ ይህም በኢትዮጵያ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ ኤምባሲ አምባሳደር መሐመድ ሳሌም አራሺድ፣ የሃያት ሬጀንሲ ሆቴል ዳይሬክተር ሚስተር ኪራም ሱገር በተገኙበት ተከናውኗል፡፡
ኤምባሲው ሴቶችን በኢኮኖሚና በማኅበራዊ ዘርፎች ተጠቃሚና አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ለማድረግ በሌላ ዘርፎች ሥልጠና እንደሚያመቻች ተገልጿል፡፡