የሰሜኑ ኢትዮጵያ ጦርነት በድርድር ለመፍታት የአፍሪካ ኅብረት ከጀመረው ጥረት ውጪ ሌላ ተወዳዳሪ የሰላም ሒደት ለመጀመር የሚሞክሩ አካላት ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡ መንግሥት አሳሰበ፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደኤታ ተስፋዬ ይልማ (አምባሳደር) ከስዊዘርላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሪ ዋልት ጋር ጳጉሜን 1 ቀን 2014 ዓ.ም. በአዲስ አበባ የሁለትዮሽ ግንኙነት አስመልክተው ባደረጉት ውይይት፣ የአፍሪካ ኅብረት የሰላም ሒደትን በሙሉ በመደገፍ እንዲቆሙና ሌላ ተወዳዳሪ የሰላም ሒደቶች እንጀምር የሚሉ ወገኖች ከድርጊታቸው ተቆጥበው፣ የተጀመረውን ጥረት እንዲያግዙ ማሳሰባቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ድረ ገጽ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
በተመሳሳይ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኮንን ከሳምንት በፊት በአዲስ አበባ ለሚገኙ የዲፕሎማቲክ ማኅበረሰብ አባላት ወቅታዊ ጉዳዮችን አስመልክተው በሰጡት ማብራሪያ፣ ተመሳሳይ መልዕክት ማስተላለፋቸው ይታወሳል፡፡
በዚህም የሰላም ድርድሩ በአፍሪካ ኅብረት ማዕቀፍ ሥር ሆኖ እንደሚቀጥልና የጎንዮሽ የሰላም ሒደት እንደማይኖር ያሳሰቡት ሚኒስትሩ፣ አክለውም አንዳንድ አካላት መንግሥትን ከሕግ ውጪ ከሆነ አሸባሪ ድርጅት ጋር ማስተካከል ማቆም እንዳለባቸውና ግጭቱን የሚያባብሱ እንዲሁም የኢትዮጵያን ሉዓለዊነት አደጋ ላይ የሚጥሉ ዕርምጃዎች ከመውሰድ እንዲቆጠቡ አሳስበው ነበር፡፡
የፌደራል መንግሥቱና የሕወሓት ታጣቂዎች የሦስተኛ ዙር ጦርነት ከመጀመራቸው በፊት፣ በአፍሪካ ኅብረት አደራዳሪነት ይካሄዳል ተብሎ ይጠበቅ የነበረውን የድርድር ሂደት ሕወሓት የድርድሩ ቦታ እንዲሁም አደራዳሪው እንዲቀየር በተደጋጋሚ ጥያቄ ሲያቀርብ ነበር፡፡
ሕወሓት ምንም እንኳን ‹‹የአፍሪካ ኅብረት ዋና አደራዳሪ በሆኑት ኦሊሴንጎ አቦሳንጆ እምነት የለኝም፣ በህብረቱ ገለልተኝነትም አላምንም›› ቢልም የኢትዮጵያ መንግሥት አደራዳሪው እንዳለ ሆኖ የድርድሩ ቦታ የትም ሊሆን እንደሚችል፣ ነገር ግን ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ድርድሩ እንዲጀመር ሲጠይቅ ነበር፡፡
ድርድሩ ሳይጀምር ሁለቱም አካላት እርስ በዕርስ በመወቃቀስ ወደ ጦርነት ከገቡ ሁለተኛ ሳምንት ተቆጥሯል፡