በወጣትነት ዘመኔ የሥነ ጽሑፍን አድማስ እየቃኘሁ በለጋ አዕምሮ በጉጉ መንፈስ ሕይወትን ‹‹ልወቅሽ ታውቂኝ›› እያልኩኝ ስፍጨረጨር ዙሪያዬ ሁሉ በግጥም ውበት በቃላት ኃይል ሊገለፅ እንዲችል ብዬ ከሐሳብ ከፊደል ጋር ስሟገት ሳለሁ እቤታችን ከሚመጡት የእናቴ ወዳጆች አንደኛዋ ስሙኒም ሽልንግም የእህል ዱቄቱንም እንጀራውንም አስቋጥራ ከምትሸኛቸው ምስኪን አንደኛዋ ‹‹እመት ደስታ›› ይሰኙ ነበር።
‹‹እመት ደስታን›› አይቶ ለሥዕል የማይመኝ ድም ሰምቶ ‹‹ምን ይሆን የሕይወታቸው ዓይነትና ጠረን?›› ብሎ የማይመሰጥ ከያኒ አይገኝም። እንዲሁ ሲያዩዋቸው ተመራመሩኝ ፈልጉኝ እሹኝ የሚል ዓይነት ፊደል ካላያቸው ይነበባል።
እኔም ሆዬ እንኳን ደርሰውብኝ ፈልጌ አስሼ የምመራመር ዓይነት በለስ በመሆኔ ‹‹እመት ደስታ›› ብዬ በመሰየም ከግጥም ወደ ስድ ጽሑፍ ዓምድ የተሻገርኩበትን የመጀመሪያዬን ተረክ በአፍላው ዕድሜ ጻፍኩኝ።
ከረዥሙ በአጭሩ ቀበና ወንዝ ዳር ሐኪም ሜዳ ከሚሰኘው መንደር በታች ጭቃ ምርግ አንዲት ክፍል ቤት ተዘግተው የሚኖሩ አፅመ ርስታቸውን ፍርደ ገምድል ዳኛ በግፍና በውሸት ምስክሮች ተነጥቀው ራሳቸውን የሳቱ የተረፈች ሕይወታቸውን ከጨለማ ክፍላቸው እሳቸው ራሳቸው አንዴ ዳኛ አንዴ ጠበቃ አንዴ ከሳሽ አንዴ ተከሳሽ በመምሰል ተውኔት የገዛ ድምፃቸውን ሲያዳምጡ ወፍ ጪጪ ጪጪ የሚልላቸው ሴት ነበሩ።
ጉሊት ይዘዋት የሚወጥዋት ስድስት አናት ሽንኩርትና የማሽላ የአሻሮ ቂጣ ያፈራቻቸው ወዳጆች አንዳንዴ ድምፃቸው ሲጠፋ ‹‹ዛሬስ ምነው ዝም አሉ ምን ክፉ ቢገጥማቸው ይሆን?›› ብለው በር ከሚቆረቁሩት በስተቀር የደረቀው የመንደር ሰንሰል ያህል እንኳን ለሰፈር ዓይን ገብተው አይታዩም ነበር።
የእመት ደስታን ሕይወት መርምሬ ጽፌ ያስነበብኳቸው ሁሉ ለጊዜው በጥልቁ ነበር መንፈሳቸው የተነካው። የመሬትን የርስትን ነገር ቁጣና መከራ ጣጣ ግፍን በደልን አስታወሳቸው።
ይህ የሆነው ሳይጋነን ከ33 እና ከ34 ዓመታት በፊት ነበር። ጊዜ ተተክቶ ሰባት ባህር ሦስት ውቂያኖስ 60 ወንዞች አቋርጩ ብዙ የብስ እግሬ ረግጦ ብዙ ብዙ ነገር ሰው እንደሆነው ሆኜ አይሆነው ሆኜ ዛሬ እዚህ አካል ሰውነቴ ካለበት እንግሊዝ ምድር ሎንዶን እንደገና እመት ደስታን አገኘኋቸው። አብሮኝ የኖረን የልማድ የአመል ሙያ እንደወትሮው ሁሉ ከአንድ ቤተ መጻሕፍት ጥግ ይዤ ስቸከችክ እመት ደስታ በቀጥታ ወደተቀመጥኩበት መጥተው ካልጠፋ መቀመጫ ካልጠበበ ቦታ እየገፋፉኝ ከመደርደሪያው መጽሐፍ ለማውጣት ይታገላሉ። የጸሐፊ አንጎል አንዳንዴ ያለፈ ትውስታውን የሌሊት ህልሙንና የቀን የእውኑን ትዕይንት ስለሚያጠናግር እራሴውኑ መላልሼ በመጠየቅ ‹‹እውን የማየውን እመት ደስታን ነውን? ከሆነስ እንዴት ሳያረጁ? ደሞስ ምንስ ነፋስ ቢነፍስ ነው ከቀበና ወንዝ ከስንት ባህር ባሻገር ከሎንዶን ምድር ያሳረፋቸው? ደሞስ ከ30 ዓመታት በኋላ እንደገና ቦታ እርስት ብለው ከእኔ ጋር መጋፋት ምን አመጣው?›› እያልኩ ስጠይቅ እንኳን የዘንድሮ አቅለቢስ ሰው ድሮም ቢሆን ሰው ይመሳሰላልና ‹‹ድንገት ተመሳስለውስ ቢሆን? አማርኛ ተናጋሪ በግንባሩ አይለይም። ፈረንጁም አፍሪካውም ጃማይካውም የሚናገረው ነው ዛሬ…›› እንዲህ እንዲህ እያልኩኝ ሳሰላስል ድንገት ነጠቅ ብለው ከአጠገቤ ሄዱ። አስቤ ሳልጨርስ ደሞ ተመልሰው መጡና ያልጠፋቸውን መጽሐፍ ፍለጋ ከንቱ ይባዝኑ ጀመር።
– ጃእርስዎ ሞትባይኖር ኪሩቤል ‹‹ከደመና በላይ›› (2014) — ክብሩ ቡክስ