በኢትዮጵያና በደቡብ ሱዳን ድንበር አካባቢ ለከፍተኛ ችግር ተጋልጠው የሚገኙ ነዋሪዎች ተጠቃሚ የሚሆኑበት ፕሮጀክት ይፋ ማድረጉን፣ ‹‹አክሽን ፎር ዘ ኒድ ኢን ኢትዮጵያ›› አስታወቀ፡፡
በምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥት (ኢጋድ) እና በአክሽን ፎር ዘ ኒድ ኢን ኢትዮጵያ ስምምነት መሠረት ተግባራዊ የሚደረገው ይህ ፕሮጀክት፣ ቁጥራቸው ከፍተኛ የሆነ ነዋሪዎች ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ዓርብ መስከረም 20 ቀን 2015 ዓ.ም. ተገልጿል፡፡
የአክሽን ፎር ዘ ኒድ ኢን ኢትዮጵያ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ሳልሁ ሡልጣን እንደገለጹት፣ በደቡብ ሱዳንና በኢትዮጵያ ድንበር ጠረፋማ አካባቢ የሚገኙ ዜጎች ተገቢውን የሆነ የሰብዓዊ ዕርዳታ ድጋፍ እንዲያገኙ ተቋሙ የተለያዩ ፕሮጀክቶችን ቀርፆ ወደ ሥራ ገብቷል፡፡
በኢትዮጵያና በደቡብ ሱዳን ድንበር አካባቢ የሚገኙ ነዋሪዎችን ተጠቃሚ ለማድረግ 200 ሚሊዮን ብር መነሻ ካፒታል በኢጋድ ድጋፍ መደረጉን የገለጹት ዳይሬክተሩ፣ በተገኘው የገንዘብ ድጋፍ የትምህርት፣ ዘላቂ የሆነ የመሠረተ ልማትና መልሶ የማቋቋም ሥራ እንደሚከናወን አስረድተዋል፡፡
በቋሚነት ፕሮጀክቱ ተግባራዊ የሚሆነው ከተለያዩ አጋር ድርጅቶች በሚደረግ የገንዘብ ድጋፍ እንደሆነ ጠቅሰው፣ ከአጋር ድርጅቶቹ የሚገኘው ገንዘብ በሁለቱ አገሮች ድንበር የሚገኙ ነዋሪዎች ወጥ የሆነ ድጋፍ እንዲያገኙ ይረዳል ብለዋል፡፡
ከዚህ ቀደም በኢትዮጵያ በስምንት ክልሎች የትምህርት፣ የጤና፣ የመንገድና ሌሎች የመሠረተ ልማት ሥራዎችን ተከናውነዋል የሚሉት ዳይሬክተሩ፣ በክልሎቹ የተከናወኑ ሥራዎችን ተግባራዊ ለማድረግ ከ2.8 ቢሊዮን ብር በላይ ፈሰስ መደረጉን ጠቁመዋል፡፡
ተቋሙም በአብዛኛው በዋናነት የሚሠራው መሠረተ ልማት ላይ እንደሆነ፣ ይህንንም ተግባራዊ ለማድረግ የተሰጠውንም ተልዕኮ እየተወጣ መሆኑን አክለው ገልጸዋል፡፡
የኢጋድ ዋና ጸሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ለአምስት ዓመታት በሚቆየው ፕሮጀክት ላይ በተለያየ ችግር ውስጥ ለሚገኙ ነዋሪዎች ሰብዓዊ ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል፡፡ በአፍሪካም በተለያዩ ችግሮች ምክንያት የሚፈናቀሉ ዜጎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መሆኑን የተናገሩት ወርቅነህ (ዶ/ር)፣ ‹‹እነዚህን ዜጎች ለመታደግ ሁሉም የበኩሉን ሊወጣ ይገባል፤›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡
በኢትዮጵያና በደቡብ ሱዳን ድንበር አካባቢ የሚገኙ ነዋሪዎች ሰብዓዊ ድጋፍ እንዲያገኙ ተቋሙ ትልቁን ድርሻ በመወጣት ላይ መሆኑን ዋና ጸሐፊው አስረድተዋል፡፡