ከ16 ዓመታት በላይ ያስቆጠረው የኢትዮጵያ የውኃ ሀብት አጠቃቀም ፖሊሲ፣ የመንግሥትና የግሉ ዘረፍ በአጋርነት እንዲሠሩ እንዲያስችል ሆኖ እየተሠራ መሆኑ ታወቀ፡፡
በውኃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የበላይ አዘጋጅነት እየተዘጋጀ ያለው ይህ ፖሊሲ፣ ካሉት በርካታ ለውጦች ውስጥ አንደኛውና ዋነኛው በመንግሥትና በግል አጋርነት፣ በውኃ ሀብት ላይ እንዲከናወን የሚያስችል መሆኑን ሚኒስትሩ ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
እንደ ሚኒስትሩ ገለጻም፣ ይህ ትልቁ አጽንኦት የግሉ ዘርፍን ማሳተፍ አድርጎ የታቀደው ፖሊሲ፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ ከካቢኔ አልፎ እስከ ፓርላማ ማድረስና ማፀደቅ የመሥሪያ ቤቱ ዕቅድ ነው፡፡ ሌላው ትልቁ የፖሊሲው ዓላማም፣ የፋይናንስ ተቋማትን በዘርፉ እንዲሳተፉ ማድረግ ሲሆን ባንኮች፣ አነስተኛና ጥቃቅን የብድር ተቋማት የፋይናንስ አቅም በመሆን እንዲያግዙ የሚያደርግ ነው፡፡
‹‹ባንኮች ለአንድ ተቋም እንዳያበድሩና ተቋሙም በከተማው መሠረተ ልማት ዘርግቶ ከሚሠራጨው ውኃ እየሰበሰበ ብድሩን ይከፍላል፤›› በማለት ሚኒስትሩ የገለጹ ሲሆን፣ ይህም በሌሎች አገሮች የተለመደ አሠራር እንደሆነ አውስተዋል፡፡ በዚህኛው በኩል ሚኒስቴሩ ትልቅ ለውጥ ይመጣል ብሎ እንደሚያቅድ ሚኒስትሩ አስረድተው፣ የፋይናንስ ተቋማትም በዚህ በኩል መዋዕለ ንዋይ ማፍሰስ እንደሚፈልጉ ገልጸዋል፡፡
ሚኒስቴሩ እንደ አዲስ ሲቋቋም ከተሰጡት ኃላፊነቶች ውስጥ አንደኛው በኃይልና በውኃ ዘርፎች ላይ የመንግሥትና የግሉ ዘርፎች በአጋርነት እንዲሠሩ ማስቻል ነበር፡፡ በተለይ ለኃይል አቅርቦት በኩል ሚኒስቴሩ በጅምር ላይ ያሉ የመንግሥትና የግል ዘርፉን በማስተሳሰር ላይ የሚገኙ ሥራዎች እየሠራ እንደሚገኝ ሚኒስትሩ ገልጸው፣ የመሥሪያ ቤቱ ከገንዘብ ሚኒስቴር ጋር በመሆን ተጨማሪ ሥራዎች መሥራት እንደሚጠበቅባቸው ተናግረዋል፡፡ ባለፉት የተወሰኑ ወራትም ቱርክንና ጀርመንን ጨምሮ በርካታ የውጭ ባለሀብቶች ፍላጎት ያሳዩ መሆናቸውንና ሥራም የጀመሩ መኖራቸውን፣ ጨምረው ገልጸዋል፡፡ የበርካታ ባለሀብቶች ፍላጎት ከውኃው ባሻገር በኃይል ዘርፉ ላይ ለመሳተፍ እንደሆነም ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡
የውኃና ሳኒቴሸን ዘርፉ ላይ የመንግሥና የግሉን ዘርፍ አጋርነት አብሮ ለመሥራት የተጀመረ ነገር የሌለ ሲሆን፣ ሚኒስትሩ በመሥሪያ ቤታቸው በኩል ፖሊሲውን ከማዘጋጀት በተጨማሪ፣ ሌሎች ሥራዎችን ማሠራት እንደሚጠበቅባቸው ገልጸዋል፡፡ ‹‹እንደሚታወቀው ኢትዮጵያ ውስጥ ውኃም ሆነ ኤሌክትሪክ ኃይል ሲቀርብ በድጎማ ነው እንጂ፣ ወጪን ችሎ አይደለም፤›› በማለት የፖሊሲውን መዘጋጀትና ተጨማሪ ሥራዎችን ማዘጋጀት አስፈላጊነት ይገልጻሉ፡፡
በሌላ በኩል ሚኒስቴሩ፣ ‹‹ግድቤን በደጄ›› በሚል መሪ ቃል ንቅናቄ የጀመረ ሲሆን፣ ይህም የውኃ ሀብትን እንዳይባክን መጠቀም፣ ከዝናብ የሚገኘውንም ውኃ በማጠራቀምና በማጣራት ኅብረተሰቡ መጠቀም እንዲችል የታቀደ ነው፡፡ ‹‹በትምህርት ቤትና መሰል ቦታዎች ላይ እንዲህ ዓይነት ሥራዎችን በመሥራት ተቋማት በውኃ ራሳቸውን እንዲችሉ ማድረግ ይቻላል፤›› ሲሉ ሚኒስትሩ የንቅናቄውን ጥቅም አስረድተዋል፡፡