የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ጥር 29 ቀን 2015 ዓ.ም በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ክልል ሊያካሄድ ላቀደው ህዝበ ውሳኔ ማስፈጸሚያነት ከጠየቀው 541.3 ሚሊዮን ብር በጀት ውስጥ 75.7 በመቶው ማለትም 410.1 ሚሊዮን ብር እንደተፈቀደለት አስታወቀ።
ምርጫ ቦርድ ይህንን ያስታወቀው ዛሬ ጥቅምት 10 ቀን 2015 ዓ.ም በዋሽንግተን ሆቴል በሰጠው መግለጫ ነው።
ቦርዱ 3.1 ሚሊዮን መራጮች እንደሚሳተፉበት ለሚጠበቀው ህዝበ ውሳኔ የተፈቀደለት በጀት ከጠየቀው በ131.3 ሚሊዮን ብር ያነሰ ነው።
የቦርዱ ዋና ሰብሳቢ ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ፣ ቦርዱ የበጀት እቅዱን ያዘጋጀው ከዚህ ቀደም ካካሄዳቸው ምርጫዎች ተሞክሮ በመነሳትና ተጨባጭ የገበያ ሁኔታውን በመመልከት መሆኑን አስረድተዋል።
ይሁንና በጀቱን የሚፈቅደው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት “አንዳንድ” የቦርዱ ጥያቄዎች “የተጋነኑ” ናቸው ፣ እንዲሁም “በመረጃ ላይ የተደገፉ አይደሉም” በሚሉ ምክንያቶች ቦርዱ ከጠየቀው ያነሰ በጀት መፍቀዱን ተናግረዋል።
ወ/ሪት ብርቱካን አክለውም፣ “ስራውን እያከናወንን ስንሄድ [የበጀት] እጥረት የሚያጋጥም ሆኖ ከተገኘ ግን ተጨማሪ በጀት እንጠይቃለን” ብለዋል።
ይሄንን ተከትሎም ቦርዱ የተፈቀደለትን በጀት በመጠቀም ህዝበ ውሳኔውን የወጪ ቅነሳ አማራጮችን በመጠቀም ለማካሄድ ማቀዱንም ገልጸዋል።
ቦርዱ ጥር 29 ቀን 2015 ዓ.ም. ሊያካሂድ ባሰበው በዚህ ህዝበ ውሳኔ በደቡብ ክልል ውስጥ የሚገኙ ስድስት ዞኖች እና አምስት ልዩ ወረዳዎች በክልልነት ለመዋቀር ያሳለፉት ውሳኔ ላይ የአካባቢዎቹ ነዋሪዎች ድምጻቸውን ይሰጣሉ።