- እኔ ምልህ፡፡
- አቤት ክቡር ሚኒስትር?
- የሰሜኑ ተዋጊዎች ከሠራዊታችን ጋር መቀራረብ ጀመሩ የሚባለው እውነት ነው?
- አዎ። እውነት ነው ክቡር ሚኒስትር።
- ከማንም ትዕዛዝ ሳይጠብቁ ነው ከእኛ ሠራዊት ጋር መቀላቀል ጀመሩ የተባለው?
- አዎ።
- እንዴት ሊሆን ይችላል?
- እንዴት መሰልዎት ክቡር ሚኒስትር…
- እ…
- ከሰሜኑ ተዋጊዎች መካከል አንዱ ታጣቂ ብቻውን ሆኖ አቅራቢያው ወደሚገኙ የእኛ ወታደሮች እየጮኸ እንደቀረባቸው ነው የገለጹልኝ።
- ምን እያለ ነው የሚጮኸው?
- እንዳትገለው …እንዳትገለው እያለ ነው የቀረባቸው።
- እና የእኛ ወታደሮች ዝም ብለው ጠበቁት?
- ታጣቂው ብቻውን ስለነበረ ሥጋት አልፈጠረባቸውም። ነገር ግን በጥንቃቄ ነበር ይከታተሉት የነበረው።
- እሺ…
- ታጣቂው አሁንም አትግደለው እያለ ወደ አንዱ የእኛ ወታደር መጠጋቱን ቀጠለ።
- አትግደለው የሚለው፣ አትግደሉኝ ለማለት ነው?
- የእኛ ወታደሮች እንደዚያ ነበር የመሰላቸው።
- እና ምን እያለ ነበር።
- ታጣቂው ግን አትግደለው ነበር የሚለው።
- ምኑን ነው አትግደለው የሚለው?
- ትምባሆውን ነው ክቡር ሚኒስትር።
- ምን?
- አዎ፣ አንዱ የእኛ ወታደር እያጨሰ ነበር። አትግደለው የሚለው አትጨርሰው ለማለት ፈልጎ ነው ክቡር ሚኒስትር።
- ምን ድራማ ነው የምታወራልኝ።
- ይመስላል ክቡር ሚኒስትር፣ ነገር ግን የተፈጠረውን ነው ያጫወትኩዎት።
- እና ከዚያ በኋላ ምን ተፈጠረ?
- የእኛ ወታደሮች በነገሩ እየተገረሙም፣ እየሳቁም አዲስ ትምባሆ ለታጣቂው አቀበሉት።
- ከዚያስ?
- ከዚያ በኋላማ አካባቢው ሳቅ በሳቅ ሆነ። ይህንን የሰሙ ሌሎች ታጣቂዎችም ቀስ እያሉ መሣሪያቸውን እያሰቀመጡ ትምባሆውንና ሳቁን መቀላቀል ጀመሩ። የሚበላውንም በጋራ ተካፈሉ።
- ይደንቃል።
- በጣም እንጂ ክቡር ሚኒስትር። ለማያውቅ ሰው እኮ የተጋጨነው በዚህ ነው የሚመስለው፡፡
- በምን?
- በሲጃራ!
- አንተ መቼም ቀልደኛ ነህ። እኔ ምልህ?
- እየሰማሁ ነው ክቡር ሚኒስትር ይቀጥሉ።
- እና ታጣቂዎቹ አሁንም ከእኛ ወታደሮች ጋር አንድ ላይ ናቸው እያልከኝ ነው።
- አዎ ክቡር ሚኒስትር። እንዲያውም በጋራ መሥራት ጀምረዋል።
- ምንድነው በጋራ የሚሠሩት ደግሞ?
- በውጊያው የሞቱ ሰዎችን በጋራ እየቀበሩ እንደሆነ ነው የሰማሁት።
- አትለኝም?!
- እውነቴን ነው! ምን ችግር አለው እንዴ ክቡር ሚኒስትር?
- አይ የለም… ያንን ጉዳይም በጋራ እንዳይሉ ሠግቼ ነው።
- የቱን ጉዳይ?
- የትጥቁን ጉዳይ!
- ትጥቅ መፍታቱን?
- እ…
- ምን ሊሉ ይችላሉ?
- በጋራ እንፍታ!
[ክቡር ሚኒስትሩ አመሻሹን ወደ መኖሪያ ቤታቸው ሲገቡ ባለቤታቸው ስለ ሰላም ስምምነቱ ያልገባቸውን ይጠይቋቸው ጀመር]
- እኔ ምልህ?
- እ… አንቺ ምትይው?
- እንዲያው አንድ ነገር ልጠይቅህ ነበር?
- ስለምን?
- ተፈረመ ስለተባለው የሰላም ስምምነት?
- ስለስምምነቱ ምን?
- የሰሜኑ ኃይል ትጥቅ ለመፍታት መስማማቱን ሰምቼ ስገረም ሌላ የተስማማው ጉዳይ እንዳለም ሰማሁ?
- ምን?
- የሽግግር መንግሥት እንዲመሠረት ተስማምቷል የሚል። እውነት ነው?
- አዎ። ትጥቅ ከፈታ በኋላ የፌዴራሉ መንግሥት የሽግግር መንግሥት ያቋቁማል።
- እና ይህንን ተስማምቶ ተቀብሏል?
- አዎ። ምንድነው ያስገረመሽ?
- ያልተፈቀደ ምርጫ አካሂዶ መንግሥት መመሥረቱ አይደል እንዴ አንዱ የግጭቱ ምክንያት?
- አዎ፣ ትክክል ነሽ።
- የሽግግር መንግሥት እንዲቋቋም የሚፈቅድ ከሆነ እዚህ ሁሉ እልቂት ውስጥ ለምን ገባን? ያሳዝናል!
- ልክ ነሽ። ያሳዝናል ከማለት ውጭ ምን ማለት ይቻላል።
- እንዲያው እነዛኞቹንም ትጥቅ ብታስፈቷቸው ሰላም እናገኝ ነበር።
- የትኞቹን?
- በምዕራብ በኩል ያሉትን።
- እነሱን ትጥቅ ለማስፈታት እንኳ መድከም የሚያስፈልግ አይመስለኝም።
- ለምን?
- ከክላሽና ዲሽቃ የዘለለ ከባድ መሣሪያ የላቸውም።
- ቢሆንስ? መፍታት አለባቸው!
- ቀላል መሣሪያ ማስፈታት ከጀመርንማ አንዘልቀውም።
- እንዴት?
- ስንቱን አስፈትተን እንችለዋለን?
- እኔ ግን ትጥቅ ባይኖራቸው እንኳን ማስፈታት አለባችሁ ባይ ነኝ!
- ትጥቅ ባይኖራቸውም?
- አዎ!
- እና ሌላ ምን እናስፈታቸው?
- ፀጉራቸውንም ቢሆን ይፍቱ!