- በአምስት ወራት ውስጥ ከ70 በላይ አሽከርካሪዎች በሥራ ላይ እያሉ ተገድለዋል
የአገር አቋራጭ ከባድ መኪና አሽከርካሪዎች በሥራ ላይ ሳሉ የሚደርስባቸው እስከ መገደል የሚደርስ አደጋና እንግልት በአስከፊ ደረጃ መጨመሩን የአሽከርካሪዎች ማኅበር አደራጅ ኮሚቴና የኢትዮጵያ ትራንስፖርት አሠሪዎች ፌዴሬሽን ገለጹ፡፡
እንደ ደመወዝና የአበል ማነስን ጨምሮ በዘርፉ የሚታዩት ችግሮች በርካታ መሆናቸውና ከሁሉም በላይ ግን የደኅንነት ሥጋት በሰፊው መንሰራፋቱን የአሽከርካሪዎችን አደጋ እንዳሰፋው የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች ማኅበር አደራጅ ኮሚቴ ለሪፖርተር ገልጿል፡፡
በቀን በፀሐይ መታገትን፣ መገደልንና ከእገታ ማስለቀቂያ ገንዘብ መጠየቅን ጨምሮ በርካታ አደጋዎች በማይታወቁ ሰዎች እየደረሰባቸው እንደሆነ የአደራጅ ኮሚቴው ዋና ሰብሳቢ አቶ ፍሰሃ አየለ ገልጸዋል፡፡
ባለፉት አምስት ወራት ብቻ ከ70 በላይ አሽከርካሪዎች መገደላቸውን ያሳወቁት አቶ ፍሰሃ፣ ይህ ቁጥር ኮሚቴው የሚያውቀውና የመዘገበው ብቻ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በኮሚቴው ያልታወቀና ያልተመዘገበ በርካታ ሌላም ሊኖር እንደሚችል ተናግረዋል፡፡ ‹‹ኅዳር 7 ቀን 2015 ዓ.ም. ታግቶና ተገሎ ከእነ ልብሱ የተቀበረ የአሽከርካሪ ሬሳ ተገኝቷል፤›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡
አቶ ፍሰሃ እንደገለጹት ከአዲስ አበባ አዋሽ መስመር ላይ፣ ከአዳማ አለፍ ብሎ ከወለንጪቲ ከተማ ጀምሮ እስከ አዋሽ ሰባት ድረስ ያለው መንገድ እጅግ አስፈሪና አሥጊ ሲሆን፣ የማይታወቁ ሰዎች በፓትሮል መኪና እየመጡ አሽከርካሪዎችን በጠራራ ፀሐይ ጭነው እንደሚሄዱና ጫካ በመውሰድ የመግደል አደጋ እንደሚያደርሱባቸው አልያም ገንዘብ በመጠየቅ እንደሚያስሯቸው ተናግረዋል፡፡ ‹‹ይህ መንገድ በጣም ምጥ ነው፡፡ የሚገርመው ከእነቤተሰብህና ማንነትህን አጥንተውና መክፈል መቻል አለመቻልህን አውቀው ነው ይህን የሚፈጽሙት፤›› ሲሉ ይገልጻሉ፡፡
ሌላኛው የኮሚቴው አመራር አቶ አብዱራሂም መሐመድ የአሽከርካሪዎች ማኅበርን እንደ አዲስ በማደራጀት ላይ መሆናቸውን በመግለጽ ማኅበሩ እንዲራጅና ሕጋዊ አቋም እንዲይዝ በተለያዩ አካላት እንደማይፈለግ ተናግረዋል፡፡ ‹‹አሁንም ውስጥ ለውስጥ እንዳይደራጅ ይፈለጋል፡፡ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሾፌር እንዳለ ነው የሚገመተው፣ አንድ ባለመሆናችን ነው ይህ ሁሉ ችግር የሚገጥመን፤›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡
ከዚህ በፊት አንድ ማኅበር እንደነበረና ይህም በተለያዩ ጫናዎች የፈረሰ በመሆኑ እንደ አዲስ ለማደራጀት ይህ አደራጅ ኮሚቴ ከአንድ ዓመት በፊት ተዋቅሮ ሥራ መጀመሩን አቶ ፍሰሃ ይገልጻሉ፡፡
የኢትዮጵያ ትራንስፖርት አሠሪዎች ፌዴሬሽን በበኩሉ የአሽከርካሪዎች ጉዳት በከፍተኛ ደረጃ ላይ እንደደረሰ እንደሚያውቅና በመንግሥት ቸልተኝነትም ችግሮቹ እየበዙ እንደሆነ የፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት አቶ ብርሃኔ ዘርዑ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡ ‹‹አንደኛ ይህን ያህል ልምድ ያላቸውና ባለ 25 ጎማ መኪና የሚያሽከረክሩ ባለሙያዎች አይገኙም፤›› ሲሉ ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል፡፡ እሳቸውም ማኅበሩን ለማደራጀት በግላቸው ጥረት እንዳደረጉ ገልጸዋል፡፡
አቶ ብርሃኔ ሲናገሩ በበፊቱ ትራንስፖርት ባለሥልጣን በኩል የአሽከርካሪዎችን መደራጃ መንገድ እንዲያዘጋጅ፣ በቅጥር ውል ሥራ እንዲሠሩ፣ ሥልጠና እየተሰጣቸውና የደኅንነት ምስክር ወረቀት (Safety License) እየተሰጣቸው አደጋን ከመከላከል አኳያ እየታሰበበት እንዲሠሩ ጥረት ተደርጎ እንደነበርና ይህም እስካሁን እንዳልተሳካ ነው፡፡