ክብረት ያለው በሰው ከእጅ ላይ ወይም በቀን ተግባሩ ነው፡፡ አላዋቂ ሰው ግን ክብረት በገዛ እጁ ሳለ ይህንኑ ለማግኘት የሰው እጅ ይመለከታል፡፡ ሰው በገዛ እጁ የማያገኘው ክብረት ስለሌለ የሰው እጅ ብቻ እየተመለከተ እጁን ወደ ሥራ ባይዘረጋው (ከእጅ አልባዎቹ) እንዳንዱ ሊቆጠር ይገባዋል፡፡ ተግባረ እድ እደ ጥበብ፣ እጅ ሥራ እየተባለ የሚተረከው ጥበባዊ ሥራ ሰውን ሲያከብረውና ብልህ ሲያሰኘው ይኖራል፡፡
ምንም የጉልበት ግማሽ አፍ ነው ቢባል ማን እንደ እጅ፤ ለሕይወት ምግብ ማስገኛ የሚሆነው የግብርና ዕቃ የሚያዘጋጀውና ከተዘጋጀም በኋላ በሬ ተጠምዶ፤ መሬቱ የሚታረሰው ዘሩ የሚዘራው፣ አረሙ የሚታረመው፣ እህሉ የሚታጨደው፣ የሚወቃው፣ የሚመረተው፣ በሪቅ የሚከተተው፣ ከሪቅ ወጥቶ የሚበስለው በእጅ ነው፡፡ የጦር መሣሪያ የሚቀጠቀጠው፣ የሚነዘረውና የሚወረወረው፤ የሚተኮሰውና የሚፈነዳው በእጅ ነው፡፡ ለማጥፊያ ለማልሚያም የሚሠራው ሥራ ሁሉ በእጅ ስለሆነ ሰው እጁን ሰብስቦና ኰርትሞ ካልዋለና ከሥራዎች አንዱን ሥራ ከያዘ ራሱን ከችግር ላይ እንደማይጥል የታወቀ ነው፡፡
ስለዚህ ክብር ያለው ወዴት ነው? ተብሎ ሲጠየቅ በእጅ ነዋ ተብሎ ሊመልስ ይችላል፡፡ እነሆ እሳትንና ውኃን አቀረብሁልህ፣ እጅህን ወደ ወደድኸው አግባ የተባለውም ይህንኑ የመሰለ ትምህርት ነው፡፡ እሳቱ መፋጀቱ፣ ውኃ መቀዝቀዙ ስለሚታወቅ ማንም ሰው ቢሆን ያኰማትረኝ ብሎ እጁን ወደ እሳት አያገባም፡፡
ችግርም እንደ እሳት ነው፡፡ ያኰማትራልና እጅን በስንፍና ገመድ ማሰር የሀብቱ ደመኛ መሆን ነው፤ አንዳንድ ሰዎች እንደተቀባይ በሰው ትከሻ እየዋሉ የሰውን የድካሙን ወዝ ለመምጠጥ፣ ሥራን ዕርም ብለው ጠልተው ቀኑ መሸት ሲል ጨለማን ተገን አድርገው አጥር ሲጥሱ፤ ግንብ ሲያፈርሱ፣ የሰው ገንዘብ ሲዘርፉና ሲገፉ፣ ሰውን ሲያንገላቱና ሲያጉላሉ ለልባቸው ርኅራኄ አይሰማውም፡፡
- ሰንደቅ ዓላማችን (1934)