ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ በደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ክልላዊ መንግስት ስር በሚገኙት ስድስት ዞኖችና አምስት ልዩ ወረዳዎች ለሚያካሂደው የህዝበ ውሳኔ ምርጫ ላይ ለመሳተፍ 2.9 ሚሊየን መራጮች መመዝገባቸው ተገለጸ።
በዛሬው እለት ጥር 1 ቀን 2015 ዓ.ም. በሞዛይክ ሆቴል ስለ መራጮች ምዝገባ ሂደት መግለጫ የሰጡት የቦርዱ ዋና ሰብሳቢ ወ/ሮ ብርቱካን ሚደቅሳ፣ ህዝበ ውሳኔው ጥር 29 ቀን 2015 ዓ.ም. እንደሚካሄድ አስታውሰው ቦርዱ ይህን ምርጫ ለማካሄድ የሚያግደው ምንም ነገር እንደሌለና አስፈላጊ ዝግጅቶች እንደተደረጉ ተናግረዋል።
ቦርዱ ለሚያካሂደው ሶስተኛው የህዝበ ውሳኔ ምርጫ የመራጮች ምዝገባ በዛሬው እለት የተጠናቀቀ ሲሆን፣ መራጮች በ3,769 የመደበኛ፣ 11 የዞኖችና የልዩ ወረዳዎች ማስተባበሪያ ጽ/ቤት አማካኝነት ተመዝግበዋል።
የአሰራር ጥሰት የተፈጸመባቸው 24 ምርጫ ጣቢያዎች ተገኝተው እንደነበር ወ/ሮ ብርቱካን በመግለጫቸው ገልጸዋል። “የመራጮች ካርድ መሰጠት ለሌለባቸው ሰዎች ተሰጥቷል፣ ምርጫ ጣቢያ ያልተገኙ ሰዎች በመራጭነት ተመዝግበዋል፣ ከጣቢያ ውጪ ካርዶች ሲታደሉ ተገኝተዋል፤” ሲሉ ቦርዱ ባደረገው ክትትል በ24 ጣቢያዎች የተገኙትን የአሰራር ጥሰቶች ተናግረዋል።