በበዛወርቅ ሺመላሽ መርዳሳ
የኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 40 ማንኛውም የኢትዮጵያ ዜጋ የግል ንብረት ባለቤት መሆኑ ይከበርለታል፣ ይህ መብት የሕዝብን ጥቅም ለመጠበቅ ተብሎ በሌላ ሁኔታ በሕግ ካልተወሰነ በስተቀር፣ ዜጋው ንብረቱን የመያዝና በንብረቱ የመጠቀም መብትን ያካትታል ይላል፡፡ ሲስተር ኬንያ ግዛው የኢትዮጵያ ዜጋ ናት፡፡ ሕገ መንግሥቱም ሌሎቹም ሕጎች ተጥሰው የፍትሕ ተቋማት በፈጸሟቸው ቀያይ ስህተቶች ከአባቷ የወረሰችውን መኖሪያ ቤት ተነጠቀች፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡
የነገሩ አነሳስ
ሲስተር ኬንያ ግዛው ከአባቷ ከአቶ ግዛው ድክር የወረሰቻቸው ብዙ ቤቶች ነበሩ፡፡ በወታደራዊው ዘመነ መንግሥት በወጣው አዋጅ መሠረት “ትርፍ ቤቶች” የተባሉትን በሙሉ ለመንግሥት አስረክባ፣ አዲስ አበባ ፍልውኃ አካባቢ የሚገኘውን ቁጥሩ 1297 የሆነውን ቤት ግን ለመኖሪያነት መርጣ ያዘች፡፡ በጊዜው ቅጽ 004 የሚባለውን ፎርም ሞልታ ስለነበር በጊዜው የነበሩት ሹሞች መብቷን አውቀውላት፣ እሷ ከቤተሰቦቿ ጋር ስድስት ኪሎ ተከራይታ በነበረው ቤትና በዚህ በመረጠችው ቤት ያለውን የኪራይ ልዩነት ማለትም 16 ብር ብቻ እንድትከፍል አድርገውላት ነበር፡፡
ነገሮች የተገለባበጡት ሲስተር ኬንያ ከባለቤቷ ከአቶ ካሳዬ ደመና ጋር ሥራ አግኝተው ወደ ኬንያ አገር በሄዱ ጊዜ ነው፡፡ በዚያን ጊዜ ቤቱ ባለቤት የሌለው መስሎት የመንግሥት ቤቶች ድርጅት በእጀ መናኛ ይዞት ነበርና ሲስተር ኬንያ ቤቱን ያላግባብ ይዘሃል ብላ ክስ መሥርታበት፣ የኢትዮጵያ ፕሪይቬታይዜሽን ኤጀንሲ ቤቱ ከሕግ ውጪ በድርጅቱ የተወሰደባት መሆኑን አረጋግጦ እንዲመለስላት በግንቦት 1980 ዓ.ም. ወስኖላታል፡፡ ይግባኝ ያቀረበ ወገን የለም፡፡ ሲስተር ኬንያ ከዚህ ውሳኔ በኋላ ቤቱን እሷም ሆነች ቤተሰቦቿ ለ12 ዓመታት ያህል በሰላም ኖረውበታል፡፡ ከዚህ በኋላ ነው ቀያይ ስህተቶች መፈጸም የጀመሩት፡፡
የመጀመርያው ቀይ ስህተት
የመንግሥት ቤቶች ድርጅት በድንገት ተነስቶ ያንኑ ውሳኔ ያረፈበትን ቤት እንድረከብ የፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ አዝዞኛልና ቤቱን እንድትለቂ ብሎ በታኅሳስ 2002 ዓ.ም. የተጻፈ ደብዳቤ ላከላት፡፡ በተደጋጋሚም ደብዳቤ ላከላት፡፡ የፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ ላስተላለፈው ትዕዛዝ መሠረት ያደረገው ያላግባብ ስለተመለሱ የመንግሥት ንብረቶች የሚደነግገውን አዋጅ ቁ/572/2000ን ነው፡፡ አዲሱ አዋጅ ወደ ግል የተመለሱ ቤቶችን እንደገና እንድረከብ ፈቅዶልኛል ነው የሚለው፡፡ አዋጁ ‹‹በቂ ባልሆኑ ወይም ሐሰተኛ ማስረጃዎች›› ላይ ተመሥርተው ወደ ግል የተመለሱ ቤቶችን ነው አጣርቶ (እደግመዋለሁ አጣርቶ) ወደ መንግሥት እንዲመለሱ የመወሰን ሥልጣን የሰጠው እንጂ፣ እንዲሁ በድንገት ተነስቶ ቤቱን መልሺ እንዲል አልነበረም፡፡
ቤቱን ራሱ የፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ ነው አጣርቶ ያንቺ ንብረት ነው ያላት፡፡ ሐሰተኛ ማስረጃ የሚባል ነገር አልተነሳም፣ የለምም፡፡ ሐሰተኛ ማስረጃ ሳይኖር ቤቱን መልሺ ልትባል አይገባም ነበር፡፡ ቀይ ስህተት አንድ፡፡
ሁለተኛው ቀይ ስህተት
ከላይ የተጠቀሰው አዋጅ ‹‹በቂ ባልሆነ ማስረጃ›› የሚል ሐረግ እንዳለው ጠቅሻለሁ፡፡ ይህንን ለማሟላት በሚመስል መልኩ የፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ ለቤቶች ድርጅት ነሐሴ 14 ቀን 2001 ዓ.ም. በጻፈው ደብዳቤ፣ ሲስተር ኬንያ ኦርጅናል ሰነዶች አላቀረበችም በማለት ጽፏል፡፡ ኦርጅናል ሰነዶች አላቀረበችም በማለት ያሰፈረው ቃል ስህተት ነው፡፡ አንደኛ፣ ራሱ ኤጀንሲው ከ12 ዓመት በፊት የማስረጃዎቹን ቅቡልነት ዓይቶ ነው የወሰነላት፡፡ ሁለተኛ፣ መሥሪያ ቤቱ በአዲስ ዘመን ጋዜጣ መስከረም 27 ቀን 2001 ዓ.ም. የ407 ሰዎች ስም ዝርዝር ጠቅሶ ኦርጅናል ሰነዶች በ30 ቀን ውስጥ እንዲያቀርቡ በጠየቀው መሠረት፣ ሲስተር ኬንያ ጥቅምት 6 ቀን 2001 ዓ.ም. ከተጻፈ ማመልከቻ ጋር አቅርባለች፡፡ አላቀረበችም ያለው ስህተት ነው፡፡
ሦስተኛው ቀይ ስህተት
ሁለቱ ድርጅቶች ተባብረው ቤቱን ለቅቀሽ እንድታስረክቢ እያሉ ስላስቸገሩና በይዞታዋ ላይ ችግር ስለፈጠሩ ሲስተር ኬንያ ሁከቱ እንዲወገድላት በመጠየቅ፣ በመንግሥት ቤቶች ድርጅትና በፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ ላይ ክስ መሠረተች፡፡ በጥር 2002 ዓ.ም. በመዝገብ ቁ/163916 በፌዴራል መጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት፡፡ ክሱ የቀረበለት ፍርድ ቤት ግን የተከሳሾቹን ክርክር ተቀብሎ ጉዳዩ ለፕራይቬታይዜሽን ቦርድ የሚቀርብ እንጂ፣ ለፍርድ ቤት የሚቀርብ አይደለም ብሎ ክሱን ዘጋው፡፡ በይግባኝም ፀና፡፡
የዳኝነት ሥልጣን ‹‹የፍርድ ቤቶች ብቻ ነው›› ተብሎ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 79 (1) ተደንግጓል፡፡ ይህን ሥልጣን ፍርድ ቤቶች በቀናኢነት ሊጠብቁት ይገባ ነበር፡፡ በቀናኢነት ሊጠብቁት የሚገባውን የዳኝነት ሥራ ሥልጣን ላልተሰጠው አካል የአመልካቿ ክስ ለፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲና የበላዩ ለሆነው የሥራ አመራር ቦርድ ማለትም ራሱ ከሳሽ፣ ራሱ መርማሪ፣ ራሱ ፈራጅ የሆነው ዘንድ ቀርበሽ አመልክቺ ብሎ ማስተላለፍ ሌላ ቀይ ስህተት ነው፡፡
አራተኛው ቀይ ስህተት
ፍርድ ቤቱ ሥልጣኑ የእኔ አይደለም፣ የፕራይቬታይዜሽን የሥራ አመራር ቦርድ ነው ስላለ ሲስተር ኬንያ አቤቱታዋን ለሥራ አመራር ቦርድ አቅርባ ነበር፡፡ ቦርዱ ግን አቤቱታዋን ሳያይ፣ እሷን ወይም ጠበቃዋን ሳያነጋግር በቦርዱ ሰብሳቢ በሰኔ 2002 ዓ.ም. በተጻፈ ደብዳቤ ‹‹ያቀረቡት አቤቱታ በቦርዱ ሊታይ የሚችል አይደለም፤›› በማለት አቤቱታዋን ዘጋው፡፡ ቦርዱ የአመልካቿን የመደመጥ መብቷን፣ ፍትሕ የማግኘት መብቷን ነፍጓል፡፡ ሌላ ቀይ ስህተት፡፡
አምስተኛው ቀይ ስህተት
አመልካቿ ክሷን ፍርድ ቤትም አልቀበልም ሲላት የፕራይቬታይዜሽን ቦርድም አልቀበልም ሲላት፣ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 37 የተደነገገው ‹‹ፍትሕ የማግኘት መብት ተጥሶብኛል›› ብላ ለሕገ መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔ በግንቦት 2005 ዓ.ም. አቤቱታ አቀረበች፡፡ አጣሪ ጉባዔው አመልካቿንም ሆነ ጠበቃዋን ሳያነጋግር ከቶውኑ ለውሳኔው መነሻና ምክንያት የሆነውንም ነገር ሳይጠቅስ፣ ጉዳዩ የሕገ መንግሥት ትርጉም የሚያስፈልገው አይደለም ብሎ መዝገቡን ዘጋው፡፡ አመልካቿ ፍትሕ የተጠማች መሆኑ እየታወቀ በሕገ መንግሥት ትርጉም ውሳኔዎች መጽሔት (ቁ3፣ 2012) እንደተጠቀሰው፣ ለምሳሌ በአንድነት ከበደ ኬዝ በተወሰነው ዓይነት ጉባዔው መወሰን ሲገባው ትርጉም አያሻውም ብሎ መወሰኑ ስህተት ነው፡፡
ስድስተኛው ቀይ ስህተት
ስድስተኛው ቀይ ስህተት የተፈጸመው የፕራይቬታይዜሽን ቦርድን በተካው በመንግሥት ልማት ድርጅቶች ተቆጣጣሪ ኤጀንሲ ነው፡፡ ሲስተር ኬንያ ዕረፍት የሌላት ሴት ናት፡፡ የሕገ መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔ አቤቱታዋን አልቀበልም ባላት ጊዜ፣ የበላዩ አካል ለሆነው ለፌዴሬሽን ምክር ቤት በታኅሳስ 2007 ዓ.ም. አቤቱታዋን አቀረበች፡፡ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ለሲስተር ኬንያ ፈርዷል ሊያስብል በሚችል መልክ ‹‹ቦርዱ (የፕራይቬታይዜሽን ቦርድ) ድፍን ያለ ውሳኔ መስጠቱ ከሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 37 ጋር የሚጋጭ ነው፣ ነገር ግን አቤት ባይዋ ኦርጅናል ሰነዶቿን ካቀረበች እንደገና ሊታይላት እንደሚችል በደብዳቤ ስለገለጸና የመደመጥ መብቷን ስላረጋገጠ የሕገ መንግሥት ትርጉም አያሻውም፤›› በማለት መጋቢት 3 ቀን 2008 ዓ.ም. ውሳኔ ሰጠ፡፡
በዚህ ውሳኔ መሠረት ያላትን ማስረጃዎች ሁሉ አያይዛ ቦርዱን ለተካው ማለትም ለመንግሥት የልማት ድርጅቶች ተቆጣጣሪ ኤጀንሲ በነሐሴ 2008 ዓ.ም. ማመልከቻ አቀረበች፡፡ ቦርዱን የተካው ኤጀንሲ ከበላይ አካል በተሰነዘረው አቅጣጫ (ወይም መመርያ) መሠረት ኦርጅናል ሰነዶችሽ የታሉ ብሎ ጠይቆ ሊያስተናግዳት ሲገባ፣ ‹‹ኦርጅናል ሰነዶች ካቀረበች እንደገና ይታያል›› ብሎ የጻፈው የቦርዱ ሠራተኛ በስህተት የጻፈው ስለሆነ ማስተናገድ አንችልም ብሎ በሩን ዘጋው፡፡ ሌላ ቀይ ስህተት፡፡
ሰባተኛው ቀይ ስህተት
ትልቁን ሰባተኛውን ቀይ ስህተት የፈጸመው የፌዴሬሽን ምክር ቤት ነው፡፡ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 62 መሠረት ሕገ መንግሥቱን የመተርጎም ሥልጣን የተሰጠው ለእሱ ስለሆነ ሥልጣኑን በከፍተኛ ኃላፊነት ሊወጣው ይገባል፡፡
በሲስተር ኬንያ ግዛው ጉዳይ አቤቱታ መጀመርያ በቀረበለት ጊዜ የፕራይቬታይዜሽን ቦርድ አቤቱታው በቦርድ ሊታይ የሚችል አይደለም ብሎ ድፍን ያለ ውሳኔ መስጠቱ የሕገ መንግሥቱን አንቀጽ 37 የሚፃረር ነው፡፡ ነገር ግን አመልካቿ ኦርጅናል ሰነዶቿን ካቀረበች እንደገና ሊታይላት አንደሚችል በደብዳቤ ስለገለጸ፣ የመደመጥ መብቷን አረጋግጧልና የሕገ መንግሥት ትርጉም አያሻውም በማለት ወስኖ ነበር፡፡ ይህም ማለት ኦርጅናል ሰነዶቿን እያቀረበች ዳኝነት የሚያይላት አካል ከሌለ ሕገ መንግሥቱ ተጥሷል ማለት እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡
የፌዴሬሽን ምክር ቤት አቤቱታ ለሦስተኛ ጊዜ በቀረበለት ጊዜ ግን እንዲህ ብሎ መወሰኑን ረስቶ፣ በጥቅምት 1 ቀን 2015 ዓ.ም. ባካሄደው ስብሰባ የሕገ መንግሥት አጣሪ ጉባዔ ጉዳዩን እንደገና መልሰን የምናይበት የሕግ አግባብ የለም ብሎ የሰጠውን ውሳኔ አፅንተናል ብሏል፡፡ ሌላ ቀይ ስህተት፡፡
ቦርዱን የተካው የመንግሥት ልማት ድርጅቶች ተቆጣጣሪ ኤጀንሲ ከፌዴሬሽን ምክር ቤት ዘወርዋራ በሆነ መንገድም ቢሆን፣ የተመራለትን ጉዳይ ማለትም ኦርጅናል ሰነዶችን ካቀረበች እንደገና ሊታይላት ይችላል ባለው መሠረት ማስረጃዎቼ አልታዩልኝም የሚል አቤቱታ ሲቀርብለት፣ ምክር ቤቱ ለዚያ አቤቱታ ምንም ውሳኔ ሳይሰጥ ማለፉ ሌላ ስህተት እንደፈጸመ ያስቆጥራል፡፡
ከዚህ ሁሉ በላይ በፌዴሬሽን ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት የሕገ መንግሥት ትርጉምና ሕገ መንግሥታዊ መብቶች ዳይሬክቶሬት የካቲት 5 ቀን 2006 ዓ.ም. በተጻፈ ማስታወሻ በቦርዱ ሊታይ የማይችልበትን ምክንያት ቦርዱ ሳይገልጽ በደፈናው ‹‹በቦርድ ሊታይ የሚችል አይደለም›› ብሎ ማሳወቁ፣ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 37 የተደነገገውን ፍትሕ የማግኘት መብት የሚጥስ ስለሆነ ትርጉም ያስፈልገዋል በማለት የሰጠው የሕግ አስተያየት በአንክሮ እንዲታይላት ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ያቀረበችው አቤቱታ ሳይታይ፣ ሳይመረመር፣ እንዲሁም በአጠቃላይ የሕገ መንግሥት አጣሪ ጉባዔ የፈጸማቸውን ስህተቶች ይግባኝ ባይዋ ነቅሳ ያወጣችበት 7 ገጽ ማመልከቻ ጨርሶ ሳይነበብ፣ ከቶውኑ በአዋጅ ቁጥር 1261/2013 አንቀጽ 15 (5) መሠረት ባለጉዳይዋ ወይም ጠበቃዋ እንደዚህ ያለ ረዥም ጊዜ የፈጀና ብዙ አካላት እጃቸውን ያስገቡበት ኬዝ ሲያጋጥም ቀርበው ስለጉዳዩ ማብራሪያ ወይም አስተያየት እንዲሰጡ ማድረግ ሲገባ፣ ይህ ሳይደረግ የሕገ መንግሥት ትርጉም አያስፈልገውም ተብሎ መወሰኑ ቀይ ስህተት ነው፡፡ ከላይ በተገለጹት ቀያይ ስህተቶች ሳቢያ ሲስተር ኬንያ ግዛው ከአንጡራ ንብረቷ እንድትለይ ተደረገ፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡