Wednesday, March 29, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

የምግብ ችግር አገራዊ ሥጋት ስለደቀነ ፈጣን ዕርምጃ ይወሰድ!

ኢትዮጵያ ውስጥ የሰው ልጆችን አቅም በብርቱ እየፈተኑ ያሉ በርካታ ችግሮች አሉ፡፡ ከችግሮቹ ብዛት የተነሳ አንዱን ከሌላው ለማስቀደም የማይቻልበት ደረጃ ላይ የተደረሰ ቢሆንም፣ የምግብና የሰላም ዕጦት ግን ጊዜ የማይሰጥና አንገብጋቢ መሆኑ ለማንም ግልጽ ነው፡፡ ሰላም ሲደፈርስና መረጋጋት ሲጠፋ ሰዎች ከቦታ ወደ ቦታ ተንቀሳቅሰው ለመሥራት ይቸግራቸዋል፡፡ የምግብም ሆነ የሌሎች ምርቶች እንቅስቃሴ ይስተጓጎላል፡፡ ሰላም አስፍኖ ወደ ልማት መሰማራት የወቅቱ ዋነኛ ጉዳይ መሆን ቢገባውም፣ 120 ሚሊዮን ሕዝብ በሚኖርባት ኢትዮጵያ ውስጥ ይህንን ፍላጎት ዕውን ለማድረግ ያዳገተ ይመስላል፡፡ በዚህም ምክንያት የምግብና የሌሎች መሠረታዊ የፍጆታ ምርቶች ዋጋ በየቀኑ አልቀመስ እያለ ነው፡፡ በተለይ ደግሞ የምግብ ዋጋ ንረት የብዙዎችን ሕይወት እያመሰቃቀለ ነው፡፡ ገበያ ውስጥ በቂ የምግብ ምርቶች አቅርቦት ካለመኖሩም በላይ፣ የአቅርቦት ሰንሰለቱም በሕገወጦችና በተባባሪዎቻቸው ተቀፍድዶ በመያዙ ብዙኃኑ ሕዝብ ለከፍተኛ ችግር ተጋልጧል፡፡ የምግብ ዋጋ ንረት በፍጥነት ካልተረጋጋ ቀውስ ሊያስከትል ይችላል፡፡ በምግብ ዋጋ ንረት ዚምባቡዌን በመከተል ከአፍሪካ ሁለተኛ፣ ከዓለም ደግሞ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ናችሁ ሲባል ደንገጥ ማለት ተገቢ ነው፡፡ ከ22 ሚሊዮን በላይ ሰዎች አስቸኳይ የምግብ ዕርዳታ ሲለመንላቸውም፣ ችግሩ አስፈሪ መሆኑን መረዳት የግድ ይላል፡፡

የምግብ ዋጋ ንረት ከፍተኛ ትኩረት ካልተሰጠውና ፈጣን ዕርምጃ ካልተወሰደ፣ አገራዊ ሥጋት ሆኖ እንደሚቀጥል ያስታወቀው የኢትዮጵያ ፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ነው፡፡ ኢንስቲትዩቱ ባለፈው ሳምንት ባዘጋጀው ዓውደ ጥናት እንዳስታወቀው፣ ከሃምሳ በላይ በሚሆኑ ትርፍ አምራችና የምግብ እጥረት ባለባቸው አካባቢዎች የዳሰሳ ጥናት አድርጓል፡፡ በጥናቱም የአቅርቦትና የፍላጎት አለመጣጣም፣ የማምረቻ ወጪዎች መናር፣ የመንግሥት ወጪዎችና የገንዘብ ፍሰትና ከትክክለኛው የኢኮኖሚ ዕድገት ጋር አለመጣጣም፣ እንዲሁም የግብይት ሥርዓቱ ኋላቀር መሆን ወይም አለመዘመን የሚሉት ተጠቅሰዋል፡፡ በአጭር ጊዜ በምግብ ዋጋ ንረት በጣም ተጎጂ የሆኑ አነስተኛ ገቢ ያላቸውን የኅብረተሰብ ክፍሎችን ለመደገፍ ከውጭ ገበያዎች መሠረታዊ የምግብ ምርቶችን በማስገባት አቅርቦትን ማሳደግ፣ ኢኮኖሚው ውስጥ የተሠራጨውን ገንዘብ ከትክለኛው ዕድገት ጋር እንዲጣጣም ማድረግ ያስፈልጋል ተብሏል፡፡ በረዥም ጊዜ ደግሞ የአነስተኛ አርሶ አደሮችን ምርታማነት መጨመር፣ የመካከለኛና ከፍተኛ የእርሻ ኢንቨስትመንቶች ማስፋፋት የሚሉት ምክረ ሐሳብ ቀርቧል፡፡ በዚህ ደረጃ የምግብ ችግር ብሔራዊ ሥጋት ሲሆን ያስደነግጣል፡፡

ለምግብ ዋጋ ንረት በምክንያትነት ከተጠቀሱት በተጨማሪ በርካታ ጉዳዮች ስለሚኖሩ ሰፋ ያለ ጥናት ማድረጉ አስፈላጊ ሲሆን፣ አሁን ካለው አጣዳፊ ሁኔታ አኳያ መንግሥት የችግሩን ፅናት ተገንዝቦ ፈጣን ዕርምጃ መውሰድ አለበት፡፡ በአሁኑ ጊዜ እንኳንስ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ዜጎች፣ መካከለኛ ገቢ ያላቸው ሳይቀሩ በከባዱ እየተፈተኑ ናቸው፡፡ መንግሥት በተለያዩ ሥፍራዎች የዘረጋቸው በርካታ ፕሮጀክቶች ለአገር ልማትና ዕድገት ያላቸው ፋይዳ አሌ ባይባልም፣ ነገር ግን ያን ያህል አንገብጋቢነት የሌላቸው ፕሮጀክቶች ደግሞ የአገር ሀብት እየፈሰሰባቸው ሕዝብ መራብ የለበትም፡፡ አሁን ካለው የመሠረታዊ ምግቦች ዋጋ ንረት አኳያ ማናቸውም ፕሮጀክቶች ከሕዝብ ህልውና ሊቀድሙም አይገባም፡፡ የምግብ ዋጋ ብቻ ሳይሆን ምግብ ነክ ያልሆኑ ምርቶች ዋጋቸው አልቀመስ ብሎ ብዙኃኑ ሕዝብ ሲቸገር፣ በጣም አንገብጋቢ ካልሆኑ ፕሮጀክቶች በስተቀር ቅድሚያ ለምግብ መሰጠት አለበት፡፡ ሕዝብ የሚበላው አጥቶ ሰላም ሊኖር ስለማይችል መንግሥት ለምግብ አቅርቦትና ሥርጭት ትልቅ ትኩረት ይስጥ፡፡ የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ያቀረበው ምክረ ሐሳብም በአንክሮ ተደምጦ ፈጣን ውሳኔ ላይ ይደረስ፡፡

የምግብ ዋጋ ንረት ብሔራዊ ሥጋት መቀደቀኑ በጥናት ላይ ተመሥርቶ ለመንግሥት ምክረ ሐሳብ ሲቀርብ፣ በኃላፊነት ስሜት ፈጣን ዕርምጃ መውሰድ የመንግሥት ጊዜ የማይሰጠው ተግባር ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ በምግብ አቅርቦትና ፍላጎት መሀል ያለው ልዩነት በጣም ሰፊ በመሆኑ፣ መንግሥት በአገር ውስጥ ከተመረቱ የምግብ ምርቶች በተጨማሪ ከውጭ ገዝቶም ቢሆን ጉድለቱን መሸፈን ይጠበቅበታል፡፡ የስንዴ ምርት ከማሳ ተነስቶ ለሸማቾችም ሆነ ለዱቄት ፋብሪካዎች በአግባቡ መቅረብ ባልቻለበት ሁኔታ ውስጥ፣ ለውጭ ገበያ ለማቅረብ የሚደረገው ጥድፊያ መገታት አለበት፡፡ ምክንያቱም አሁን ምግብ ትልቁ የሥጋት አጀንዳ ስለሆነ፡፡ አብዛኛው ሕዝብ የኑሮ ውድነቱን መቋቋም ተስኖት ሕይወቱ ሲኦል እየሆነበት ባለበት በዚህ አስከፊ ጊዜ፣ ከመንግሥት በላይ ማንም አጣዳፊ ዕርምጃ ለመውሰድ የሚችል ኃይል የለም፡፡ በቀን አንዴ ምግብ ለማግኘት ሚሊዮኖች በሚጨነቁባት ኢትዮጵያ ውስጥ ፈጣን ዕርምጃ መውሰድ አለመቻል፣ ከሚታሰበው በላይ አደገኛ ሰብዓዊ ቀውስ ሊያስከትል እንደሚችል ግንዛቤ ይኑር፡፡ በአገር ደረጃ ከዚህ በላይ አጣዳፊ ጉዳይ እንደሌለ ይታመን፡፡

ኢትዮጵያ ውስጥ ምግብ መቼም ቢሆን ውድ ያልሆነበት ጊዜ የለም፡፡ አንድ ኩንታል ነጭ ጤፍ 40 ብር ይሸጥ ነበር የሚባልበት ጊዜም ቢሆን፣ አቤት ደጉ ዘመን እየተባለ ከበሮ የሚያስደልቅ ታሪክ የለውም፡፡ በወቅቱ የ40 ብር ደመወዝተኛ ወይም የወር ገቢ የሚያመነጭ ሥራ ያላቸው በጣም ጥቂት ነበሩ፡፡ የተቀረው ሕዝብ ግን ከእጅ ወደ አፍ የሆነ ኑሮ ነበር የሚገፋው፡፡ ጤፍ፣ ስንዴ፣ ገብስ፣ ማሽላ፣ በቆሎና ሌሎች የጥራጥሬ ሰብሎችን የሚያመርተው አርሶ አደርም ቢሆን፣ በዓመት ውስጥ የረባ ምግብ የሚያገኘው ግፋ ቢል ለሁለት ወራት ብቻ ነበር፡፡ የምግብ ዋስትና ጉዳይ ሁሌም ጭንቅና መከራ ነበር፡፡ በዚህ ላይ ደግሞ በየአሥር ዓመቱ ሳይዛነፍ ከተፍ የሚለው ድርቅና ረሃብ፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ኢትዮጵያን ደጋግሞ ስሟን አስጠርቷታል፡፡ ለንጉሠ ነገሥቱ ሥርዓት መገርሰስ ምክንያት ከሆኑት አንደኛው የ1965 ዓ.ም. ረሃብ ነበር፡፡ በ1977 ዓ.ም. በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎችን አርግፏል የሚባለው ዘግናኝ ረሃብ ጦሱ አይረሳም፡፡ መንግሥታት በተቀያየሩ ቁጥር አጀንዳ ከመሆን ዘሎ የማያውቀው የምግብ ችግር፣ በጥናት ላይ የተመሠረተ ምላሽ ባለማግኘቱ አሁንም ትልቅ ሥጋት ደቅኗል፡፡

ከዕለት ጉርስ በተጨማሪም አልባሳት፣ መጫሚያዎች፣ የቤት ኪራይ፣ የትምህርት ቤት፣ የጤና፣ የትራንስፖርት፣ የውኃ፣ የኤሌክትሪክና ሌሎች ለኑሮ የሚያስፈልጉ መሠረታዊ ምርቶችና አገልግሎቶች ዋጋቸው አልቀመስ እያለ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት በአጭር፣ በመካከለኛና በረጅም ጊዜ ዕቅድ መፍትሔ ለማግኘት ርብርብ እየተደረገ ለኑሮ ውድነት ምክንያት የሆኑ ጉዳዮች ግን በጥልቀትና በስፋት መጠናት አለባቸው፡፡ ኢትዮጵያን የመሰለች ከፍተኛ መጠን ያለው ለም መሬት፣ ክረምት ከበጋ የሚፈስ ትልቅ የውኃ ፀጋ፣ በአፍሪካ አንደኛ የሆነ የእንስሳት ሀብት፣ ለቁጥር የሚያዳግቱ ማዕድናት፣ በርካታ የቱሪስት መስህቦችና ከምንም ነገር በላይ ከፍተኛ የሰው ኃይል ያላት አገር ምግብ ብሔራዊ ሥጋት ደቀነባት ሲባል መደንገጥ ይገባል፡፡ ለዘመናት እነዚህን የተፈጥሮ በረከቶች መጠቀም አቅቶ በዓለም አቀፍ ደረጃ ኢትዮጵያ ለምን የረሃብ ተምሳሌት ሆነች የሚለው፣ ከምንም ነገር በላይ የአገራዊ ምክክሩ መነጋገሪያ አጀንዳ መሆን አለበት፡፡ ከዚያ በፊት ግን ክቡር የሆነው የሰው ልጅ በቂና ተመጣጣኝ ምግብ እንዲያገኝ ፈጣን ዕርምጃ ይወሰድ!  

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

የኦሮሞን ሕዝብ ታሪክ አልባ በማድረግ ታሪክ አይሠራም

በኢተፋ ቀጀላ​​  ከዛሬ ሃምሳ ዓመት ወዲህ ከተፈጠሩት የኦሮሞ ድርጅቶች መካከል ከኢጭአት በስተቀር፣...

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንና የመንግሥት ውዝግብ

የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) መንግሥት ባለፉት አራት ዓመታት...

በኦሮሚያ ክልል በስድስት ከተሞች የተዋቀረውን ሸገር ከተማን የማደራጀት ሥራ ተጀመረ

በአዲስ አበባ ዙሪያ በሚገኙ ስድስት ከተሞች የተዋቀረው ሸገር ከተማን...
- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

[የምክር ቤቱ አባል ላቀረቡት ጥያቄ በተሰጣቸው ምላሽ አቤቱታቸውን ለክቡር ሚኒስትሩ እያቀረቡ ነው]

ክቡር ሚኒስትር እየሆነ ያለው ነገር ትክክል ነው? ምነው? ምክር ቤቱም ሆነ...

የጉራጌ የክልልነት ጥያቄ ትኩሳት

ቅዳሜ መጋቢት 16 ቀን 2015 ዓ.ም. በጉራጌ ዞን ወልቂጤ...

አይ የእኛ ነገር!

የዛሬው ጉዞ ከጀሞ ወደ ፒያሳ ነው፡፡ መንገዱ ለሥራ በሚጣደፉ፣...

የዓለም ኢኮኖሚ መናጋት ለወቅታዊው የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ችግር ምክንያት ነው?

ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ባለፈው ማክሰኞ መጋቢት 16...

የተዘነጋው የከተሞች ሥራ የመፍጠር ተልዕኮ

በንጉሥ ወዳጅነው አሁን አሁን የአገራችን የሥራ ዕድል ፈጠራ ጉዳይ አንገብጋቢና...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

የሰላም ዕጦትና የኑሮ ውድነት አሁንም የአገር ፈተና ናቸው!

ማክሰኞ መጋቢት 19 ቀን 2015 ዓ.ም. የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ለጠቅላይ ሚኒስትሩ በርካታ ጥያቄዎች አቅርበዋል፡፡ ጥያቄዎቹ በአመዛኙ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ያጠነጠኑ...

ግልጽነትና ተጠያቂነት የጎደለው አሠራር ለአገር አይበጅም!

ሰሞኑን የአሜሪካና የኢትዮጵያ መንግሥታት በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ተፈጽመዋል በተባሉ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችና የጦር ወንጀሎች መግለጫ ላይ አልተግባቡም፡፡ አለመግባባታቸው የሚጠበቅ በመሆኑ ሊደንቅ አይገባም፡፡ ነገር ግን...

የምግብ ችግር ድህነቱን ይበልጥ እያባባሰው ነው!

በአገር ውስጥና በውጭ የተለያዩ ተቋማት የሚወጡ መረጃዎች እንደሚያሳዩት፣ በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ከ22 ሚሊዮን በላይ ዜጎች አስቸኳይ የምግብ ዕርዳታ ያስፈልጋቸዋል፡፡ እነዚህ ወገኖች በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት፣...