Tuesday, March 28, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

አዝማሪው ተገኘ ታደሰ

በተሾመ ብርሃኑ ከማል

ተገኘ ታደሰ ምናልባት በ1910ሮቹ ተወልዶ ሊሆን እንደሚችል የሚገመት ሲሆን፣ አብዛኛው የሕይወት  ዘመኑን ያሳለፈው በዋግ ነው፡፡ ሆኖም አንዳንድ ሰዎች ልጃቸውን ሲድሩ ወደ ደሴም፣ አዲስ አበባም ሊመጣ ይችላል፡፡ ተገኘ ታደሰ የተገኘው ከአዝማሪ ቤተሰብ ሲሆን አባቱ አባ መላ ታደሰም ሆኑ አያቱ (የእናቱ አባት) ሊቀ መኳስ ቢያድግልኝ ደስታ በዋግ የታወቁ አዝማሪ እንደነበሩ ትልቅ ወንድሜ ሐጅ ዓብዱራሕማን ብርሃኑ ከማል ነግሮኛል፡፡ ወንድሜ እንደሚለው የተገኘ ታደሰ አያት የሆኑት ሊቀ መኳስ ቢያድግልኝ በወቅቱ ለነበሩት ዋግ ሹሞች ማሲንቆ በመምታት፣ በማመስገን፣ በማወደስ፣ እነርሱን አጅበው በተለያዩ በዓላት ተገኝተው ያደምቁ ነበር፡፡ የወቅቱ አዝማሪዎች፣ የመኳንንቱና የመሳፍንቱ ለቅሶን ለማድመቅም ታሪካቸውን አጥንተው፣ ወይም ፈጥረው ያወድሱ ነበር፡፡ በተለይም እንደ የዘውድ በዓል፣ የድል በዓል፣ የሃይማኖት በዓላት ሲኖሩ እስከ አሥር የሚደርሱ አዝማሪዎች ዋግ ሹሞችንና አብረዋቸው የሚገኙ ባለሥልጣኖችን ከፊት በሁለት ረድፍ ሆነው ሕዝብ ወደ ተሰበሰበበት አደባባይ ይመሩ ነበር፡፡ ወንድሜ ዓብዱራሕማን ብርሃኑ ከማል ጨምሮ እንዳስረዳኝ፣ በተለይም ትውልዱ ወለህ፣ ጀርባ፣ በአባቱ ቡግና አያቱ ሊቀ መኳስ ቢያድግልኝ ደስታ ናቸው፡፡ ወንድሜ እንደሚለው የተገኘ ታደሰ አያት ሊቀመኳስ ቢያድግልኝ ደስታ፡ ብላታ ወልደ ሳሙኤል ቢያድግልኝ፣ አብርሃ ቢያድግልኝ፣ በላይ ቢያድግልኝ፣ አሰገደች ቢድግልኝ (የተገኘ ታደሰ እናት) ተብለው የሚጠሩ ልጆች ሲኖሯቸው ሁሉም አዝማሪዎች ነበሩ፡፡

የተጠቀሱት የሙዚቃ ባለሙያዎች ልጆቻቸው ጭምር አዝማሪነት አስተምረዋቸዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ የወ/ሮ አሰገደች ቢያድግልኝ ልጆች የሆኑት እነ ዓለሙ ወዳጆ፣ መለሰ ወዳጆ፣ ጌታወይ ወዳጆ በጣም የታወቁ አዝማሪዎች ናቸው፡፡ አባታቸው አቶ ወዳጆም የታወቁ አዝማሪ ነበሩ፡፡ የአዝማሪ ልጅ አዝማሪ የሚሆንበት መሠረታዊ ምክንያት ከዘር ወደ ዘር እንደባህርይ፣ ወይም እንደ ንጉሣዊ ቤተሰብ የሚተላለፍ ሲሆን፣ እነሱም ለምን ሌላ ሥራ አትሠሩም ሲባሉ ‹‹አንሠራም፡፡ የአባቶቻችን ነው፡፡ ካልሠራን በቁምጥና እናልቃለን›› የሚል አስተሳሰብ አላቸው፡፡

ተገኘ ታደሰን እንዴት መግለጽ ይቻላል?

ተገኜ ታደሰ ካለፈ ብዙ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ምናልባት 40 ዓመታት ሊያልፉ ይችላሉ፡፡ ስለዚህም እኛ በ60ዎቹና በ70ዎቹ ዕድሜ ከምንገኘው በስተቀር ብዙ የሚያስታውሰው የለም፡፡ እኔም ይህን ጽሑፍ ለማዘጋጀት ብፈልግም ዘፈኑን ለማግኘት ባለመቻሌ እስካሁን ለመጻፍ አልቻልኩም ነበር፡፡ በመሆኑም ብዙ ጊዜ ጨርሶብኛል፡፡ በቅርቡ በጥቁርና ነጭ የተሠራጨ ፊልም ሳገኝ የመጻፍ ፍላጎቴ እንደገና ተነሳሳ፡፡ በዚህ እንቅስቃሴ ላይ እያለሁ መዝሙር ፈንቴ፣ አሸናፊ ፈንቴ፣ ዮሴፍ በላይ፣ መሳይ ጸጋው (የዋግ ኽምራ ዞን ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ) የየራሳቸውን ዕገዛ በማድረግ ታሪኩን እጽፈው ዘንድ ገፋፉኝ፡፡ ሆኖም ጽሑፉን አዘጋጅቼ ሳጠናቅቅ ፎቶግራፉን የሚሰጠኝ ላገኝ አልቻልኩም፡፡

በልጅነት ዕድሜዬ እንደማስታውሰው፣ የቀይ ዳማ፣ ፊተ ክብ፣ ጸጉረ ሉጫ፣ ቀጭን ሲሆን ከተማ ሲሆን ሳሪያን ኮትና ተፈሪ ቅድ የተሰኘውን ሱሪ መልበስ ያዘወትራል፡፡ ከከተማ ውጭ ሲሄድ ግን ቁምጣ ሱሪና ሸሚዝ ይለብሳል፡፡ ከዚያ ላይ ነጠላ ወይም ቀጭን ኩታ ይደርባል፡፡ ጥርሶቹ ያምራሉ፡፡ ተገኘ ታደሰ ከጀርባው የማይለይ ማሲንቆ ቢኖረውም አጭርና ረዥም ምንሽር፣ አልቤን በኋላ ላይም ቤልጅግ ታጣቂ ነው። በሰጋር በቅሎ አሽከር አስከትሎ የሚሄድ ነበር። ሰፊ እርሻ፣ ብዙ ከብት በሺሕ የሚቆጠር ፍየል ነበረው ይባላል። ቤቱም ከሀብታሞች እኩል ትልቅ ነበር። የብዙ ሰዎች ሚዜ ነበር። የአጎቴም ሚዜ የነበረ ይመስለኛል።

ተገኘ ታደሰ በዘለሰኛ ዜማ

በሰላም ያዋልኸኝ፣ ሰላም አሳድረኝ፣

ሒሳቡ ነው እንጅ የሚቸግረኝ

እመጣለሁ ኋላ ሌላም ቤት የለኝ፡፡

በዘፈን መካከል አስገብቶ ያለ እንደሆን የነበረው ደስታ ሁሉ ወደ ትካዜ ይለወጣል፡፡ ከዚያ አውጥቶ

ሸሞንሟና ቀሚስ አሠርቼልሽ

የማንን ድሪቶ ትጎትቻለሽ

ሳምሳም አድርገሽ ቶሎ ልቀቂኝ

የዋግሹም አጫዋች ቅምጥሉ ነኝ፡፡

ያገሬን ልጅ ትቼ የሰው አገር ሳድን፣

ቀረሁ እንዳከሳሁ ጐኔም ሳይደነድን፡፡

አገሩ ጉራንጉር ስፍራው የወንበዴ፣

ስንቱን አገር አልፎ አንቺን አለ ሆዴ፡፡

እኔ አንቺን አልኩ እንጅ የልጅነቴን፣

የፍቅርን ሀ ሁ ያስተማርሽኝን፡፡

አሚተኛ ይማ ይቆረጥ አንጀቱ

አያጠፋ የለም ሰው በልጅነቱ፡፡

የቸገረ ነገር የጠፋ ለመላ

እንዴት ይለያያል ሰው ሳይጠላላ፡፡

ጤነኛ ይመስላል ይኼ ሁሉ ሰው፣

ሌሊት ሌሊት ያብዳል በየመኝታው፡፡

በማለት ወደ ፍቅር ዓለም ጎትቶ ያስገባል፡፡

ተገኘ ታደሰ የሌለበት በዓል፣ ሠርግና ለቅሶ አይደምቅም። የተለያዩ ምቶችና ዜማዎች ስለነበሩት ሲዘፍን ያስጨፍራል፡፡ ሲያንጎራጉርም አንጀት አንሰፍስፎ ያስለቅሳል። ለበዓል እግሩ ወዳደረሰው ቤት እየዞረ ለጥቂት ደቂቃዎችም ቢሆን ሲጫወት ለሠርግ የሚጠራው ግን አስቀድሞ ነው። ታዲያ ደሃ ሀብታም አይለይም። ሲበዛ ጥንቁቅ ነው። በየቦታው የሚሄደው ታዲያ ሳንቲም ለመልቀም ሳይሆን ስለቱን ለማድረስ ነው።

ተገኘ ታደሰ በግል ሕይወቱ ተጫዋች ነው። ይህን ዘፈን ዘፍኖ በሬዲዮ በተላለፈ ሰሞን (1958) በሰቆጣ፣ በኮረምና በደሴ ከተማ ሳሪያን ኮቱንና ተፈሪ ቅድ ሱሪውን ለብሶ በዚያ ላይ የሚያምር ቀጠን ያለ ጥበብ ያለው ነጠላ ደርቦ ሲንጎማለል ልዩ ክብረ ሞገስ ነበረው።

አገሬ ጥራሪ ኧረ ወንዛ ወንዙ

አገሬ ዛምራ ኧረ ወንዛወንዙ

አገሬ ተከዜ ኧረ ወንዛወንዙ

ውኃው ይጣፍጣል ማር እንደበረዙ

የዘጠኝ ዋግሺም ልጅ አሥረኛው እሱ

ሰጥ አርጎ ይገዛል ዋግሥዩም አድማሱ ይለዋል፡፡

ይህ ድምፃዊ በ1950ዎቹና 60ዎቹ የታወቀና ስመ ገናና ነበር። ስለሆነም ፊልም አንሽዎች ኮረም ድረስ መጥተው ዘፈኑ በዘመኑ ውድ በሆነ ፊልም ቀርጸውታል። በቴሌቪዥንና በሬዲዮ ሲተላለፍም የጉድ ጉድ ተብሎለታል። ዘፈኑን በሬዲዮ ወይም በቴሌቪዥን በድንገት የሰማና ያየ የዋግና የላስታ ሰው ሥራውን ወይም ጉዞውን አቋርጦ ሰምቷል ወይም አዳምጧል።

ከዚያ ወዲህ፣ አንዳንድ ጊዜ፣ በታወቁ የሰቆጣና የኮረም፣ የደሴም ጠጅ ቤቶች ወይም ሌሎች ድግሶች ሲዘፍን ድምፁን ጎርነን ሲልበት ‹‹ኧረ ወዲያ፣ ይኼ ራዲዮን ድምፄን ሰልቦት አይደል?›› የሚል ምክንያት ይሰጥ ነበር። በዚያን ጊዜ ‹‹ሬዲዮን የሚያናግረው ሰይጣን ነው›› የሚል አስተሳሰብ ነበር። ይኸው በዋግና ላስታ ተወዳጅ የነበረ ድምፃዊ ወደ አዲስ አበባ መጥቶ ብዙ ሰቆጦችና ላስቶች በሚኖሩበት ቂርቆስ ቀበሌ የነበረ ሲሆን ምናልባት በ1970ዎቹ የሞተ ይመስለኛል።

አገሬ ጻግብጅ ያግድም ያግድም፣

አገሬ ዝቋላ ያግድም ያግድም፣

ወይ አገሬ ስሜን ያግድም ያግድም፣

አገሬ ደሃና ያግድም ያግድም፣

አገሬ ጋዝጊብላ ያግድም ያግድም፣

አንጋዳው ክፉ ነው አያረማምድም፡፡

ኧረ በለው በለው ኧረ በለው በለው

በለው በለውና ጠብቄ ልበለው

ቅል ቋንቁራም የለኝ የማንጠለጥለው፡፡

የተገኘ ታደሰ ዜማ ጨዋታ

ዜማ ማለት ስልት፣ ውበት፣ ሥርዓት፣ ምት ያለው ድምፅ ነው፡፡ ድምፁ፣ የማህሌት፣ የውዳሴ፣ የቅዳሴ፣ የሙጋሴ ሊሆን ይችላል፡፡ ዜማን ድምፀ መረዋ ሲያቀርበው ተደማጭ፣ ተናፋቂና ከልቦና የማይጠፋ ሲሆን ሸካራ ድምፅ ያለው ሲያቀርበው ደግሞ በተቃራኒው ይሆናል፡፡ የተገኘ ታደሰ መዲና፣ ዘለሰኛ፣ ሰንጎ መገን፣ ቀረርቶና ሽለላ ቢጫወት ለሁሉም ዜማዎች የታደለ ነበር፡፡

አንዳንዱ ግጥም ምክንያቱ ይታወቃል፣ አንዳንዱ ደግሞ አይታወቅም፡፡ ሆኖም አንድ ግጥም ዝም ብሎ አይገጠምም፡፡ ምክንያት ይኖረዋል፡፡ ከዚህ በታች የተያያዘው ተገኘ ታደሰ ከ1953 መፈንቅለ መንግሥት ጋር በተያያዘ ሲዘፍነው የነበረ ነው፡፡

ሲወዱት የጠላ ሲያምኑት የከዳ ሰው፣

በዚያው በሣልስቱ ብድሩ ደረሰው

ላፍ ይመራል እንጅ ሆድ ያጠራል ኮሶ

ይርጋ ብሎ ቀረ፣ የትግሬው ምሰሶ

በግሩ ተተካለት ልጁ ተመልሶ

ባባት ስም የላቸው በናት ስም የላቸው፣

አፈቀርኩኝ ብለው ጃንሆይ ቢያቀርቧቸው

እንዲህ በማታለል ጉባዔ አለ ብለው

እነርሱ ታርደዋል ታላቁን አጉለው፡፡

በአንድ በዓል ወይም ዝግጅት፣ ወይም ሠርግ ብዙ አዝማሪዎች ሊኖሩ ሲችሉ አንዱ ጨዋታውን ካረዘመው፣ ወይም ታዳሚው ካልወደደው፣ ወይም መሰላቸት ካሳየ ተገኘ ታደሰ በማሃል ገብቶ በዚያው ምት፡-

ሸሞንሟና ቀሚስ አሠርቸልሽ

የማንን ድሪቶ ትጎትቻለሽ

ሳምሳም አድርገሽ ቶሎ ልቀቂኝ

የዋክሽም አጫዋች ቅምጥሉ ነኝ

በማለት በመጀመር ወደ ራሱ ዜማ ሲቀይረው ይታይ ነበር፡፡

ተገኘ ታደሰ፣ አንዳንድ ጊዜ በጣም ድንቅ የሆኑ ግጥሞች ይመጡለትና አንድም ስለሚረሳቸው ወይም የስንኙን መድፊያ ወዲያው መፍጠር ስለሚቸግረው አንዱን ሲጀምር ሲደጋግም ወይም ሲያድበሰብስ ይታያል፡፡ ለምሳሌ፡-

እኔስ እፈራለሁ ቆሜ ሰው መግደሉን

ባንቺ እጀምራለሁይልና ቆም በማለት ወይም በማድበስበስ

እስቲ ላነሳሳው ተገኘ አባመላን

የዋክሽሞች አሽከር ሰርክ አመስጋኙን

እንደምን ላድርገው በላይ ደበበን

ተገኘ አባመላ ኮረም ያለውን፡፡

ተገኘ ታደሰ ብዙ ጊዜና በብዙ ቦታዎች ከሚያወሳቸው ታሪኮች አንዱ በጣሊያን ወረራ ጊዜ (1928-1933) ደጃዝማች ኃይሉ ከበደ ያሳዩትን ጀብዱና ወለህ በተባለ ስፍራ መሰዋታቸውን የሚመለከተው ነበር፡፡

አንድም በየዳ ላይ ሰባ ሰው ታረደ፣

አንድም ከርቦ ዳነ ሰባ ሰው ታረደ

ያንን ሰምቶ ሰምቶ ተነሳ ከበደ፣

ጣሊያን ጋር ጌታውን ሮማ ሰደደ፣

አይቻልም ብሏል እንግዳ ከበደ፣

እርባማና ሆኖ ወለህ ሲቀድስ፣

አጨደው ከመረው ወለህ ላይ ሲደርስ፣

ባስቻለው መትረየስ፣ ባስቻለው እርሳስ፣

መረብ ወደቀ አሉኝ ውድብ ሳይጨርስ፡፡

አንገትህ በኮረም ተሰቅሎ ነበረ፣

አንገትህ ባስማራ ተሰቅሎ ነበረ፣

አምስት ዓመት ሙሉ ሲጸልይ የኖረ፣

ዕድሜ ላባጠቅል ደምሽ ተከበረ፡፡

ቀረርቶ፣ ሽለላና ፉከራ

አዝማሪዎች ባማረና በሚስብ ላህይና ቃና በማሲንቆ ግርፋቸው ቀረርቶ፣ ሽለላና ፉከራቸው የታዳሚውን ልቦና ይስባሉ፡፡ ፉከራ፣ ሽለላና ቀረርቶ ብዙ ጊዜ የሚቀርበው እንደ ዓድዋ በዓል፣ እንደ ሚያዝያ 27 እና የካቲት 12 ባሉ ብሔራዊ በዓላት ቢሆንም በሠርግም ጊዜ መሽራው ሙሽሪትን ከመውሰዱ በፊት ሊቀርብ ይችላል፡፡ ቀረርቶው፣ ሽለላውና ፉከራው በአርበኞች ወይም በባለሥልጣኖች ቤት ሲሆን ሊበረታ ሙሽራውና ሚዜዎቹ ብቻ ሳይሆኑ አርበኛ የሙሽሪትና የሙሽራ አባቶች እንዲሁም ወዳጅ ዘመዶች ከመሃል ገብተው ሊካፈሉ ይችላሉ፡፡ ተገኘ ታደሰ በዚህ ረገድ የታደለ ድምሰፅ የነበረው ሲሆን ማሲንቆው ራሱ ወኔ የሚያነሳሳ ድምፅ ነበረው፡፡ ቀረርቶ፣ ሽለላና ፉከራ ቀስ ብሎ ወደ ዘፈን የሚወስድ ሆኖ ዘፈኑ ይቀጥላል፡፡ ተገኘ ታደሰ በዚህ ረገድ በእጅጉ የታወቀና ወኔን የሚቀሰቅስ አዝማሪ ነበር፡፡ ከዚህ በታች ያለው ግጥም ስለ ጀኔራል ኃይሉ ከበደ ተጋድሎ የሚወሳበት ዘፈን ነው፡፡

አባ መረብ ኃይል ኃይሌ አባ ይባስ፣

አንገቱን የሰጠው እንደ ዮሐንስ፡፡

ወለህ ከሜዳው ላይ ገብቶ ሲቀድስ፣

ቄሱ ታፈረ ነው ዲያቆኑ ሞገስ፡፡

አባ መረብ ኃይል ኃይሌ ሀንስ አባ ይባስ፣

አጨደው ከመረው ወቃው እንደ ገብስ፣

ሳያዘራው ቀረ ካልታጣው አድማስ፡፡

አንቺ ወለህ ማርያም ተቃጠልሽ ወይ፣

ዐምደ ወርቅ ጨርቆስ ተቃጠለ ወይ፣

እናቴ ወይብላ ተቃጥለሽ ነወይ

እያወቅሽ ጠላትሽን ልትሰጅው ነወይ፡፡

አንቺ ወለህ ማርያም፣ አንቺ ምንድን ሆንሺ

ዓርብ ተሰቀለ፣ ኃይሉ ከደጅሽ፡፡

ቀይ በርቤ መስለው ጥሊያኖች ሲዘልቁ፣

መድፉ ተቀየደ መትረየሱ ትጥቁ፣

ያንን ሁሉ ጠቅጥቆ የመጣው አድማሱ፣

የማይቀር ተሆነ ያጦር መጠንሰሱ፣

ምጥዋ በመለስ መስጠት ነው ላድማሱ፡፡

ዋግ ሥዩም አድማሱ ጨዋታ ያውቃሉ

ሰርክ ዓይና ቡግና ይደባደባሉ፡፡

እነዚህ ጥሊያኖች ባተ መልካም ናቸው፣

በኋላ ቀርቸ ሲሄዱ ባያቸው፡፡

ዘብጥያ ነዳው ከነጂኒናር ጋር

ወርዶ አገናኛቸው ቁስላቸው ሳይሽር

ለባንዴራ ታማኝ አድማሱ ወሰን፡፡

ልማታዊ ግጥሞች

ተገኘ ታደሰ በርካታ ልማታዊ ግጥሞችና ከግጥሞቹ ጋር የሚሄዱ ዜማዎች ነበሩት፡፡ ከእነዚህም የልማት ግጥሞች መካከል ለብዙ ጊዜ ሲጓተት የነበረው የኮረም ሰቆጣና የሰቆጣ መቀሌ መንገድ ይገኝበታል፡፡ መንገዱ ተደልድሎ መኪና ሲገባም እንዲህ ሲል ተጫውቷል፡፡

መኪና ሰቆጣ አይገባም እያሉ፣

የታባቱ ገባ አባይ ጠንቋይ ሁሉ

ጉብኝት ሲገባ ሲመጣ ሰው ሁሉ

ለምን ወጣት ሁሉ አጉል ይጨነቃል

መኪናና ሰቆጣ ያመጣ አምላክ ያውቃል

መኪናን በሳምሬ ያገባ አምላክ ያውቃል፡፡

ከተወለደ አይቀር፣ ከፈረሰም አይቀር፣ ከተሰጠ መርሻ

መውለድ እንደኛ ልጅ ልክ እንደ መንገሻ

ጌታችን ተወልዶ ደረሰ ለጋሻ

አስገራሚ የተገኘ ታደሰ ዘፈኖች

ተገኘ ታደሰ ብዙ አስገራሚና አስደናቂ እንዲሁም አመራማሪ ዘፈኖች ነበሩት ከእነዚህም አንዱን ‹‹ዓለም ክብረት ዓለም›› በሚል የሚዘፍነው ሲሆን እርሱንም እንደሚከተለው እንመልከት፡፡

‹‹እስቲ ወዲያሂደሽ ወዲህ ተመለሽ

እንደቀይ ዳንግሌ መድኃኒቴ ነሽ፡፡››

ይህ ምን ማለት ነው?

በዚህ ግጥም ሁለት መሠረታዊ ነገሮች አሉ፡፡ አንደኛ ወዲያ ሂዶ ወዲህ መመለስ ሲሆን፣ ሁለተኛው ቀይ ዳንግሌ ነው፡፡ በመሠረቱ ዳንግሌ የሚለው ቃል ደንከሌ፣ የደንከል፣ የዓፋር በግ ማለት ሲሆን ቀይ ዳንግሌ ማለትም ላቱ የሚጎተት የደንከል በግ በደብተራ፣ በጠንቋይ፣ በመተተኛ ለበሽተኛ  የሚታዘዝ መድኃኒት ነው፡፡ በጉ እምጥም ይሁን ስምጥ ተገብቶ መገኘትና ወደ በሽተኛው መምጣት፣ ከመጣ በኋላም በበሽተኛው ፊት ወዲያ ወዲህ መመላለስና በበሽተኛው ላይ ፈውስ ማምጣት አለበት፡፡ ለምሳሌ በሽተኛው ደሃና፣ ዝቋላ፣ ቡግና ወይም ምዕራብ በለሳ ቢሆን ቀይ ዳግሌ በግ ለማግኘት ቢያንስ ቢያንስ እስከ አላማጣ፣ ኩኩፍቶ፣ መኾኒ እዚያም ከጠፋ እስከ ማሐል ዓፋር መምጣት ያስፈልጋል፡፡ ከደሃና አላማጣ ለመድረስ ሦስት ቀን በግ እየነዱ ለመመለስ ደግሞ ያን ያህል ቢሆን የሳምንት መንገድ መጓዝ ያስፈልጋል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን ቀይ ዳንግሌ በግ 20 እና 30 ብር ቢሆን፣ ላም ወይም በሬ ሸጦ መሄድ ይጠይቃል፡፡ በዚህም መሠረት የሚወዳትን፣ የታመመባትን፣ የሚናፍቃትን ለማግኘት፣ ወይም ከመንፈስ ሕመሙ ለመፈወስ ‹‹ከወዲያ ወዲህ ወዲህ መመለስ ምሱ ነው›› ማለት እንችላለን፡፡

የባህር ማሽላ የለውም ወይ ነዶ

አገሯ ሰቆጣ በለስ ወዲያ ማዶ

አገሯ ደሃና ገበያው ዐምደ ወርቅ

ምነው በቀረብኝ ሳንተዋወቅ፡፡

ለምን ቢቀርበት መረጠ? እንግዲህ ለሆነ ምክንያት፣ ማለትም ለገበያ፣ ለሠርግ፣ ለለቅሶ ሄዶ ይሆናል እንበል፡፡ የአጋጣሚ ነገር ግን ዐምደ ወርቅ ገበያ አግኝቷት ይሆንና ይተዋወቃታል፡፡ በሁለቱ መካከል ፍቅር ይመሠረታል፡፡ ሆኖም ከዚያ በኋላ እየተመላለሰ ሊያያት ቢፈልግ ይቸግረዋል፡፡ አይተዋት ነገር አፍቅሯል፡፡ እንደፈለገ አያገኛት ነገር አገሯ ሩቅ ነው፡፡ በመሠረቱ ወጣቶች ከአጎራባች መንደሮች ካሉ ጋር ፍቅር ሲይዛቸው እርሻቸውን ሲያርሱ ከዋሉ በኋላ ሞፈር ቀንበራቸውን ተሸክመው ከብቶቻቸውን በረት ውስጥ ያስገቡና በጨረቃም ሆነ በጨለማ ከፍቅረኞቻቸው ጋር ተያይተው ይመለሱ ነበር፡፡ ዐምደ ወርቅ ገበያ የተገኘችው ሴት ግን የሩቅ ሩቅ መሆኗ ነው፡፡ ስለዚህም አይተዋት ነገር አፍቅሮ፣ እንደፈለገ አያገኛት ሩቅ ሆኖበት ሲወዘወዝ ኖሯል ማለት ነው፡፡ ይህም ማለት ትቷታል አይሄድም ማለት አይደለም፡፡ ይሄድና ያያታል ግን መመላለሱ አድካሚ ነው፡፡

ሰቆጣ ከዋርካው ከጥላው አርፌ፣

ልቤን ትቸው መጣሁ ሳንባዬን ታቅፌ

በዚህ ዘፈን የምናገኘው ሰቆጣው ዋርካው ስር ተቀምጦ የነበረው ሰው ልቡን ትቶ ሳንባውን ታቅፎ መምጣቱ ነው፡፡ ነገር ግን ሰቆጣ ዋርካው ጥላ ሥር ምን ነበር? ምሥጢሩ ያለው እዚህ ነው፡፡ ሰቆጣ ዋርካ ጥላ ሥር በሳምንት ማክሰኞና ረቡዕ ቅቤ፣ ዶሮ፣ እንቁላል፣ ጀበና ይዘው ከቆላው አካባቢ የሚመጡ እጅግ ውብ ሴቶች ነበሩ፡፡ ከዚህ ላይ በቅቤ ወዝተው ሲመጡ ውበታቸው በጣም ይስባል፡፡ ሰውየው ሳንባውን አትርፎ ልቡን ብቻ ትቶ መሄዱ ዕድለኛ ነው ማለት ይቻላል፡፡

መቋጫ

የተገኘ ታደሰ ዘፈን ብዙ ነው፡፡ ከስድሳ እስከ ሰባ ዓመት ያህል በሙዚቃው ዓለም የቆየ ስለሆነ ዘፈኑ ብዙ ነው፡፡ እኔ ብቻዬን ከየዘፈኑ 300 ያህል ስንኞችን ሰብስቤያለሁ፡፡ ወደፊት በመልክ በመልካቸው እተነትናቸዋለሁ ብዬ አስባለሁ፡፡ ለጊዜው ግን፡-

ዓለም ወይ ለዎ ዓለም ወይ ለዎ

እፈይ አው ግሪሩ ለዎ

እፈይ አወይጭሩ

ምንም አዲስ ሆነሽ ቋንቋየን ባታውቂ፣

ጥርስሽ ደስ ይለኛል በይ አንድ ጊዜ ሳቂ፡፡

በጥራሬ አቀበት፣ በብርብር ፀሐይ፣

ዓለም ጥላ ይዤ ልከተልሽ ወይ

ዓለም ወይ ለዎ ለዎ፣ ዓለም ወይ ለዎ

ይኻግር ሳልጽበ፣ ያም …ሳበ

ቀዱ ቢሊሲግደ ለዎ ያለም ተጡን ትግረ

ይኻግር ጻግብጂ አውከሱድ እንጎጂ ለዎ

በማለት በአማርኛና በአገውኛ ህብር ዜማው እሰናበታለሁ፡፡ ይህን ጽሑፍ እንዳዘጋጅ የተባበሩኝን ሁሉ አመሰግናለሁ፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው አንጋፋ ጋዜጠኛ፣ ደራሲ፣ የእስልምና ጉዳዮች ተመራማሪ፣ እንዲሁም የታሪክ አጥኚ ሲሆኑ፣ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን፣ በኢሜይል አድራሻቸው [email protected] ማግኘት ይቻላል፡፡

spot_imgspot_img
- Advertisment -

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

Related Articles