Friday, June 9, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ኪንና ባህል‹‹ንቃቃት›› ድራማ - ፆታዊ ጥቃቶችን ለመከላከል  የሄደበት መንገድ

‹‹ንቃቃት›› ድራማ – ፆታዊ ጥቃቶችን ለመከላከል  የሄደበት መንገድ

ቀን:

በአበበ ፍቅር

በኢትዮጵያ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች ተብለው ከሚፈረጁት ውስጥ የሴት ልጅ ግርዛትና የልጅነት ጋብቻ ተጠቃሽ ናቸው፡፡ በተጨማሪም አስገድዶ መድፈርና ጠለፋ ሴት ልጆችን ካለ ዕድሜያቸውና ፍላጎታቸው ለከፋ ጉዳት ከሚያጋልጡ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች ይመደባሉ፡፡

ለእነዚህ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች እንደ መሠረታዊ ምክንያቶች ተደርገው ከሚወሰዱት ውስጥ የማኅበረሰቡ አኗኗር ዝቅተኛ መሆን፣ የግንዛቤ እጥረትና  ማኅበረሰቡ ለሴቶች ያለው ግምት ዝቅተኛ መሆን የሚሉት ይጠቀሳሉ፡፡

የተባበሩት መንግሥታት ሕዝብ ፈንድ እ.ኤ.አ. የ2022 የሥርዓተ ፆታ ግንኙነት ሚዛኑን አለመጠበቅ፣ የውሳኔ ሰጪነት ድርሻዎች መዛባት፣ የሴት ልጆች ሰብዓዊ መብት መጣስ፣ የግል ምርጫቸው አለመከበር ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ አኗኗራቸው ዝቅተኛና የተጎሳቆለ መሆን በማኅበረሰቡ ዘንድ ሴት ልጆችን ለጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች እንደሚዳርግ ያስቀምጣል፡፡

በኢትዮጵያ በተለይም በገጠራማው አካባቢ ፆታን መሠረት አድርገው በሴቶች ላይ የሚደርሱ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችን ለመከላከል፣ ሴቶች በትዳር አጋራቸው የሚደረስባቸውን ጭቆና እንዲሁም የሴት ልጅ ግርዛትና የመሳሰሉትን ችግሮች ለመፍታት መንግሥትና የተለያዩ ግብረ ሰናይ ድርጅቶች እየሠሩ ይገኛል፡፡

ከእነዚህ ድርጅቶች መካከል ፖፕሌሽን ሚዲያ ሴንተር ኢትዮጵያ የተሰኘው ዓለም ዓቀፍ ድርጅት አንዱ ነው፡፡ ድርጅቱ የሴቶችንና ሕፃናትን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ችግሮች ለማቃለል ላለፉት 20 ዓመታት የተለያዩ የመገናኛ ብዙኃንን በመጠቀም በጥናት ላይ ተመሥርቶ በተለያዩ አካባቢዎች ላይ ከፍተኛ የሆነ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት ሲያስተላልፍ መቆየቱን ተናግሯል፡፡

ፖፕሌሽን ሚዲያ ሴንተር ኢትዮጵያ ከተባበሩት መንግሥታት የሥነ ሕዝብ ፈንድ ጋር በመተባበር ከካናዳ መንግሥት በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ ‹‹ንቃቃት›› የሚል ተከታታይ የሬድዮ ድራማ በማዘጋጀት ለሕዝብ ጆሮ ሲያደርስም ቆይቷል፡፡

ድራማው በዋናነት በፆታዊ ጥቃት፣ በታዳጊነት ዕድሜ የሚፈጸም ጋብቻ የሴቶች ግርዛትና የእርግዝና መከላከያ ተጠቃሚነትን በማሳደግ ላይ ትኩረት አድርጎ ለ18 ወራት ሲተላለፍ ቆይቷል የድራማውን መጠናቀቅ ምክንያት በማድረግም ጥር 17 ቀን 2015 ዓ.ም. የማጠቃለያ ፕሮግራም ተካሂዷል፡፡

ፖፕሌሽን ሚዲያ ሴንተር ኢትዮጵያ ከተመሠረተበት እ.ኤ.አ. ከ2001  ጀምሮ፣  ከተባበሩት መንግሥታት የሕፃናት መርጃ ድርጅት፣ ከዓለም ዓቀፉ የሕፃናት አድር ድርጅት፣ ከጤና ሚኒስቴርና ከመሳሰሉት መንግሥታዊና መንግሥታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች ጋር በመተባበር አሳሳቢ በሆኑ ጉዳዮች በተለይም የጤናና ማኅበራዊ ችግሮችን ለመቅረፍ ሲሠራ መቆየቱ በፕሮግራሙ ላይ ተነስቷል፡፡

ፕሮጀክቱ በዋናነት ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችና ኅብረተሰብ ተኮር ችግሮች ላይ በማተኮር በቤተሰብ ምጣኔ፣ ያለዕድሜ ጋብቻ፣ የወጣቶች የሥነ ተዋልዶ ጤና፣ ኤች አይቪ ኤድስ፣ በሕፃናት ጉልበት ብዝበዛ፣ የሴት ልጅ ግርዛትን ጨምሮ በፆታ እኩልነትና የሴቶችን አቅም በመገንባት ላይ ያተኮሩ ሥራዎችን ሲያከናውን እንደነበር የፕሮጀክቱ የኢትዮጵያ ዋና ዳይሬክተር ኃይለኛው እሸቴ (ዶ/ር) አስታውቀዋል፡፡

ድርጅቱ ምርምርን መሠረት ያደረጉ ጤናና ማኅበራዊ ይዘት ያላቸውና እያንዳንዳቸው ከአንድ ዓመት ተኩል እስከ ሁለት ዓመት ተኩል የወሰዱ ድራማዎችን አዘጋጅቶ ለሕዝብ ማድረሱ ተገግሯል፡፡

ከተላለፉት ድራማዎች መካከል የቀን ቅኝት፣ ዲንቢባ፣ ማለዳ፣ መንታ መንገድ፣ ስብራት፣ ምዕራፍ፣ የረገቡ ፈትሎች፣ የብርሃን አጽናፋትና ንቃቃት ይገኙበታል፡፡ ድራማዎቹ በቤተሰብ ምጣኔ፣ በታዳጊነት የሚፈጸም ጋብቻ፣ በኤችአይቪ፣ በሴት ልጅ ግርዛት፣ ወጣቶችን ለልማት በማነሳሳት እንዲሁም በጤናና ኤክስቴሽን በመሳሰሉ ጉዳዮች ዙሪያ የግንዛቤ ማስጨበጫ መልዕክቶችን ሲያስተላልፉ መቆየቱን ዋና ተጠሪው አብራርተዋል፡፡

ድራማው በብዙዎቹ ዘንድ ተደራሽ እንዲሆን በአማርኛ፣ በኦሮሚኛ፣ በአፋርኛና በሱማሊኛ ቋንቋዎች ተዘጋጅተው እንደቀረቡ፣ በአማራ፣ በኦሮሚያ፣ በትግራይና በደቡብ ብሔር ብሔረሰብ ክልሎች ለ18 ወራት ሲተላለፍ የነበረው ‹‹ንቃቃት›› ድራማም በተመረጡ 24 ወረዳዎች 669 ሺሕ ለሚልቁ ጉዳዩ በቀጥታ ለሚመለከታቸው የኅብረተሰብ ክፍሎች መተላለፉን የፕሮግራሙ ማናጀር ትዕግሥት ሞገስ አብራርተዋል፡፡ እነዚህ ወረዳዎች በፕሮጀክቱ የታቀፉ ይሁኑ እንጂ ፕሮግራሙ በመላው አገሪቱ ሲደመጥ መቆየቱን ተናግረዋል፡፡

የድራማውን መጠናቀቅ ተከትሎ በተደረገ የግምገማ ጥናት ፕሮግራሙን ያዳመጡት ሰዎች ካላዳመጡ ሰዎች የተሻለ ግንዛቤ እንዳሳዩ ትዕግሥት ተናግረዋል፡፡

ይሁን እንጂ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት በኢትዮጵያ በገጠርም ሆነ በከተማ በሴቶች ላይ የሚፈጸሙ ፆታዊ ጥቃቶችን ለመከላከል ሁሉም ኅብረተሰብ ኃላፊነት ሊወስድ ይገባል ብለዋል፡፡

ፖፕሌሽን ሚዲያ ሴንተር ኢትዮጵያ በኅትመት ውጤቶችም ተደራሾችን ለማግኘት በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ የተጻፉ መጻሕፍትን፣ መጽሔቶችን፣ በራሪ ጽሑፎችን ፖስተሮችን አሳትሞ ለንባብ እንዳበቃ ተነግሯል፡፡

በዕለቱም ‹‹የዓይን እማኝ›› እና ‹‹ሥነ ሕዝብ›› የተሰኙ መጻሕፍት ተመርቀዋል፡፡ የ‹‹ዓይን እማኝ›› የተሰኘው መጽሐፍ አሥር አጫጭር እውነተኛ ታሪኮችን የያዘ ሲሆን፣ በአገሪቱ በሴቶች ላይ የሚፈጸሙ ፆታዊ ትንኮሳዎችና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥን ነው፡፡

ታሪኮቹ የተጻፉት በመጽሐፍ ዝግጅት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲና ከኢትዮጵያ ደራሲያን ማኅበር በተውጣጡ ደራሲያን ሲሆን፣ ከመጻፋቸው በፊት ቦታው ድረስ በመሄድ በፕሮጀክቱ የታቀፉ ወረዳዎች ላይ ቅኝት በማድረግና ባለታሪኮችን በአካል በማነጋገር የተዘጋጀ እንደሆነ የፖፕሌሽን ሚዲያ ሴንተር የኢትዮጵያ ተጠሪ ኃይለኛው (ዶ/ር) ተናግረዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ የሥነ ሕዝብና ተያያዥ ጉዳዮች በሚል ርዕስ በጉዳዩ ላይ የሥራ ልምድ ባካበቱ የዩኒቨርሲቲ ምሑራን ጋር በመተባበር ያሳተመውን መጽሐፍ ለንባብ አብቅቷል፡፡

መጽሐፉ ለአካባቢ ጥበቃ፣ ለተመጣጠነ ሕዝብ ዕድገት፣ ልማትና ከዚሁ ጋር ተያያዥነት ላላቸው የአየርና ሥነ ምኅዳር መዛባት በአጠቃላይም ተፈጥሮ ሚዛኗን ጠብቃ እንድትቆይ ሁሉም ሰው የየራሱን ድርሻ መወጣት እንዳለበት በስፋት የሚዳስስ መሆኑን ለማየት ችለናል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ