በአበበ ፍቅር
ከአፄ ኃይለ ሥላሴ ንግሥና (1923-1967) አሥር ዓመት ቀደም ብሎ የጃማይካውያን የመብት ተሟጋች ማርከስ ጋርቬይ ተከታዮቹን ‹‹ወደ አፍሪካ ተመልከቱ ጥቁር ንጉሥ ይነግሣል የመስጠት ዓመትም ይመጣል፤›› ሲል ነገራቸው፡፡
ከትንቢቱ አሥር ዓመት በኋላ ራስ ተፈሪ መኰንን በኢትዮጵያ ሲነግሡ በርካቶች ትንቢቱ ዕውን የመሆን ምልክት ነው አሉ፡፡ ከአሥር ሺሕ ኪሎ ሜትር በላይ ርቀው የሚገኙት ጃማይካውያን አፄ ኃይለ ሥላሴ ‹‹እንደ ፈጣሪ›› ኢትዮጵያንም የቃል ኪዳኑ ምድር አድርገው እንደወሰዱ ይነገራል፡፡
በዚህም አፄ ኃይለ ሥላሴ በ1950ዎቹ መጀመሪያ ላይ ጃማይካን በጎበኙበት ወቅት በሺዎች የሚቆጠሩ ጃማይካውያን የደመቀ አቀባበል አደረጉላቸው፡፡ የጃንሆይ ጉብኝት ተከትሎ ወደ ኢትዮጵያ የሚመጡ ጃማይካውያን ቁጥር መጨመሩ ይነገራል፡፡
የሬጌ ሙዚቃ ንጉሥ ቦብ ማርሌም በሙዚቃው አፍሪካንና ኢትዮጵያን እንዲሁም ንጉሡን የመፃኢ ዘመን ተስፋና መጠጊያ አድርጎ ይሥላቸው እንደነበር በቦብ ማርሌ የሕይወት ታሪክ ላይ ተጽፎ ይገኛል፡፡
ከዚያ ዘመን ጀምሮ ጃማይካውያን የሬጌ አቀንቃኞች ኢትዮጵያን ለዓለም ለማስተዋወቅ ብዙ ሥራዎችን እንደሠሩ ይነገራል፡፡
ይህንን ታሪካዊና የቀደመ ቁርኝታቸውን የበለጠ ለማጠናከር እየተቀዛቀዘ የመጣውን ግንኙነት ለማነቃቃት ያለመ የሙዚቃ ዝግጅት በጃማይካ ሞንቲጎ ቤይ ሊካሄድ ነው ተብሏል፡፡
ይህ የሙዚቃ ድግስ ከመጪው ግንቦት 18 እስከ 20 ቀን 2015 ዓ.ም. እንደሚካሄድ አዘጋጆቹ ንጉሥ ኢንተርቴይመንትና አቢሲኒያ ኢንተርቴይመንት አስታውቀዋል፡፡
በዚህ ዓለም አቀፍ የሙዚቃ ሮያል ፌስቲቫል ላይ የጃማይካ ተወዳጅ የሆኑት የሬጌ ሙዚቃ አቀንቃኞች ጆሲ ሮያል፣ ሲዝላ ኮሎንጅ፣ ጆሶን ፓንቶን፣ ሚኪ ግንራል የተካተቱበት ሲሆን፣ ከኢትዮጵያ ተወዳጆቹ ወጣት ድምፃውያን ዳዊት ጽጌ፣ ልጅ ሚካኤል፣ ካስማስ፣ ዮሐና፣ ኒና ግርማ፣ ያሬድ ነጉና ሳሚ ዳን ሥራዎቻቸውን እንደሚያቀርቡ ተመልክቷል፡፡
‹‹ኢትዮጵያ የተባረከች ገነት አገር›› ናት ያለው ጆሲ ሮያል፣ የዓለም ቋንቋ የሆነውን ሙዚቃ ተጠቅመን በኢትዮጵያና በጃማይካ ምናባዊ ድልድይ መሥራት ይኖርብናል ሲል ተናግሯል፡፡
በዚህ ታላቅ የሙዚቃ ድግስ ከአሜሪካና ከአውሮፓ የሚመጡ ከሁለት ሺሕ በላይ ኢትዮጵያውያን ይሳተፉበታል የሚል ግምት እንዳላቸው አዘጋጆቹ ተናግረዋል፡፡
በዚህ የሙዚቃ ድግስ መሳተፍ የሚፈልጉ ኢትዮጵያውያን አዘጋጆቹን በማነጋገር መሳተፍ ይችላሉ ተብሏል፡፡
ዝግጅቱ ኢትዮጵያን ለዓለም ለማስተዋወቅና የዓለም አቀፍ ጎብኚዎችን ትኩረት ለመሳብ እንዳለመ ተጠቁሟል፡፡