በሪፖርተር ጋዜጣ ረቡዕ ጥር 24 ቀን 2015 ዓ.ም. ዕትም ‹‹የፌዴራል ፕሮጀክቶች የካሳ ክፍያ ለከፍተኛ የወንጀል ድርጊት ምንጭ እየሆነ ነው›› በሚል ርዕስ የወጣው ጽሑፍ ሐሳብ በተለይም ‹‹ፍትሕ ሚኒስቴር አለ›› ተብሎ የተገለጸው በወቅቱ በመድረኩ ከተሰጠው አስተያየት ጋር የማይገናኝ ነው በማለት በፍትሕ ሚኒስቴር ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ዘርፍ በወንጀል የተገኘ ሀብት ማስመለስ ዳይሬክተር ጄኔራል ወ/ሮ ፀጋ ዋቅጅራ እንዲስተካከል ጠይቀዋል፡፡ እሳቸው ለማለት የፈለጉትም ‹‹የካሳ አከፋፈል ኢትዮጵያ ውስጥ እየተፈጸመ የመጣ ትልቅ ወንጀል ነው፡፡ በመሆኑም የካሳ አከፋፈል ሥርዓት ያልተበጀለት በሕግና በመመሪያ ያልተደገፈ ከሆነ የሙስና ወንጀል ነው፡፡ በመሆኑም የካሳ አከፋፈል ሥርዓት ያልተበጀለት በሕግና በመመሪያ ያልተደገፈ ከሆነ የሙስና ወንጀል እንዲፈጽም ዕድል የሚከፍት በመሆኑ ትኩረት ሊሰጥበት ይገባል፤›› እንጂ፣ በጋዜጣው ላይ እንደተገለጸው የፌዴራል ፕሮጀክቶች የካሳ ክፍያ ለከፍተኛ የወንጀል ድርጊት ምንጭ እየሆነ ነው፤›› የሚል መደምደሚያ ተሰጥቶ እንዳልተገለጸ አሳውቀዋል፡፡ በመሆኑም ከላይ በተገለጸው ሁኔታ የካሳ አከፋፈል ሥርዓት ለወንጀል የተጋለጠ እንዳይሆን ትኩረት ሊደረግለት ይገባል ተብሎ እንዲነበብ እንጠይቃለን፡፡