ችግር ሲያጋጥም በሕጋዊና በሰላማዊ መንገድ መፍታት ከአላስፈላጊ ግብግቦች ይታደጋል፡፡ ሰሞኑን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተፈጠረው ችግር በሰላማዊ መንገድ መፈታት ሲገባው፣ ልዩነቱ ከሚገባው በላይ ተለጥጦ አደገኛ ሁኔታ ውስጥ እየተገባ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ለሁለት ዓመታት ያህል የገባችበት አውዳሚ ጦርነት ቁስሉ ሳይጠግ፣ ድንገት እንደዚህ ያለ አደገኛ ሁኔታ ውስጥ ሲገባ ያስፈራል፡፡ አሁን ያለው አማራጭ አንድ ብቻ ነው፡፡ እሱም ሕግ ተከብሮ የተፈጠረውን ውጥረት ማርገብ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያኗ ውስጣዊ ችግር በውስጥ አሠራርና ሕግ ፈር ይዞ ሰላማዊ ድባብ እንዲፈጠር፣ መንግሥትም ሆነ ሌሎች ባለድርሻ አካላት የሚፈለግባቸውን ኃላፊነት ይወጡ፡፡ አሁን በስፋት እንደሚስተዋለው የማይመለከታቸው አካላት ጭምር ችግሩን እያባባሱት ነው፡፡ ፖለቲካና ሃይማኖታዊ ጉዳይን በመደበላለቅ በሕጋዊና በሰላማዊ መንገድ መፈታት ያለበትን ችግር እያወሳሰቡት ነው፡፡ ነገሮች ከቁጥጥር ውጪ ወጥተው የከፋ ጥፋት ከመድረሱ በፊት ውጥረቱ ይርገብ፡፡ እልህ መፍትሔ አያስገኝም፡፡ ከእልህ በመላቀቅ ሁሉንም ወገኖች የሚያግባባ መፍትሔ ላይ ይደረስ፡፡
አማኞች ሰላማዊ ሆነው ጽንፈኛ ፖለቲከኞች አገር ሲረብሹ ማስቆም የመንግሥት ኃላፊነት ነው፡፡ አገርን መቀመቅ ሊከትና ሕዝብን ለተጨማሪ ሥቃይና መከራ የሚዳርግ ችግር ሲከሰት፣ ከማንም በፊት ቀድሞ አደጋን መከላከልና ማስቆም ያለበት መንግሥት ነው፡፡ በዚህ ረገድ የፌዴራል መንግሥትና የክልል ብሔራዊ መንግሥታት በመጀመሪያ ራሳቸው ሕግ አክብረው የማስከበር ኃላፊነት አለባቸው፡፡ በሕግና በሥርዓት የማይመራ አገር የወንበዴዎች መጫወቻ ስለሚሆን፣ የሚመለከታችሁ የመንግሥት አካላትና አመራሮች ሕግ እንዲከበር ኃላፊነታችሁን ተወጡ፡፡ ሰሞኑን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያጋጠመው ችግር ተፈቶ ሰላም ይስፈን፡፡ በሕጋዊና በሰላማዊ መንገድ መነጋገርና ችግሩን መፍታት እየተቻለ፣ ከመጠን በላይ ተለጥጦ አድማሱን ሲያሰፋ በእልህና በግትርነት ስሜት ችላ ማለት ዋጋ ያስከፍላል፡፡ የፖለቲካ ተዋንያን ያለ ምንም ከልካይ እየተንደረደሩ እየገቡበት ያለው እሰጥ አገባ ማቆሚያ ካላገኘ፣ ሕዝብና አገርን ከባድ ቀውስ ውስጥ እንደሚከት ለማንም ግልጽ መሆን አለበት፡፡ ስለዚህም እጃቸውን እያስረዘሙ ያሉ ፖለቲከኞች ከድርጊታቸው ይቆጠቡ፡፡ ሃይማኖትና ፖለቲካን መቀላቀል አያዋጣም፡፡
መንግሥት የአገርን ሉዓላዊነትና የግዛት አንድነት ማስከበር የሚችለው የሕዝብን ሰላምና ደኅንነት ሲያስከብር ነው፡፡ ሕዝብ ከኢኮኖሚያዊ፣ ከፖለቲካዊና ከማኅበራዊ ጉዳዩ ባልተናነሰ ሃይማኖታዊ ችግር ሲያጋጥመው፣ መንግሥት በሕግ በተሰጠው ሥልጣን መሠረት ተገቢውን ምላሽ መስጠት ይጠበቅበታል፡፡ በመንግሥትም ሆነ በፓርቲ መዋቅር ውስጥ ሆነው ሕግን የሚያፋልሱና አላስፈላጊ ድርጊቶችን የሚፈጽሙ ሲኖሩም፣ በሕጉ መሠረት ተገቢውን ዕርምጃ በመውሰድ ግዴታውን መወጣት ይኖርበታል፡፡ የዜጎች ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ሲጣሱ ከማንም በላይ ለምን ብሎ መነሳት ያለበት መንግሥት ነው፡፡ ሕገወጦች ዜጎችን ሲበድሉም ሆነ ሕግ ሲጥሱ የማስታገስ ግዴታ ያለበት መንግሥት ነው፡፡ የአገርን ሰላምና ደኅንነት የሚያናጋ ሕገወጥ ድርጊት ሲፈጸም ፈጥኖ ዕርምጃ የመውሰድ ኃላፊነት ያለበት መንግሥት ስለመሆኑ ለማንም ግልጽ ነው፡፡ በአሁኑ የኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ግን መንግሥት በርካታ ሕገወጥ ድርጊቶችን ዓይቶ እንዳላየ እያለፈ ብዙዎችን እያሳዘነ ነው፡፡ በተለያዩ አካባቢዎች ዜጎች በማንነታቸው ተለይተው ሲጨፈጨፉና ጽንፈኞች እንዳሻቸው ሲፈነጩ፣ ተቆጪና ገሳጭ በመጥፋቱ እዚህ ደረጃ ላይ ተደርሷል፡፡
አሁን ጊዜው በጣም እየረፈደ ስለሆነ ሰሞነኛውን የአገር ትኩሳት ማብረድ ከምንም ነገር በላይ የሚቀድም ተግባር ነው፡፡ ከዚህ ቀደም በብሔርም ሆነ በሌሎች ጉዳዮች ከአጋጠሙ ቀውሶች የባሰ አደገኛ ሥጋት ተደቅኗል፡፡ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጀምሮ በየደረጃው ያሉ ከፍተኛ የመንግሥት ተሿሚዎችም ሆኑ ሌሎች አካላት፣ በአገር ላይ እያንዣበበ ያለውን አደጋ ለመቀልበስ በቀና መንፈስ መነሳት ይጠበቅባቸዋል፡፡ አሁን ያጋጠመው ችግር በአግባቡ ተፈቶ አንፃራዊ ሰላም እንዲፈጠር ማድረግ ይቻላል፡፡ ነገር ግን ከዚህ በተቃራኒ የሚታሰብ ከሆነ ግን፣ አገር በታሪኳ ዓይታው የማታውቀው ግጭት ሊቀሰቀስ ይችላል፡፡ ስለዚህ በቅንነትና በስክነት ችግሩን በመፍታት አደጋውን ማስቆም ይገባል፡፡ ለስክነት፣ ለትዕግሥት፣ ለመነጋገር፣ ለመግባባትና በጋራ አብሮ ለመሥራት ፍላጎት ማሳየት ጠቃሚ ነው፡፡ ከጉዳዩ ባለቤቶች በላይ በመሆን ችግሩን አላስፈላጊ ገጽታ በማላበስ ጥላቻ የሚያስፋፉ አካላትን ወደ ጎን በማለት፣ ከዋነኞቹ የጉዳዩ ባለቤቶች ጋር መነጋገርና ልዩነትን ማጥበብ ያስፈልጋል፡፡ ሃይማኖታዊ ጉዳይ ውስጥ ብሔርና ፖለቲካን እየቀየጡ ችግር የሚፈጥሩ አካላትን በሕግ መጠየቅም ተገቢ ነው፡፡
የቤተ እምነቶች ጉዳይ ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚያስፈልገው፣ ከዚህ ቀደም በፖለቲካው አለመግባባት ውስጥ በሰፊው የታየው የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ተጠናክሮ ስለሚቀጥል ነው፡፡ የእምነት ጉዳይን ለባለቤቶቹ መተው ችግር ሲያጋጥመው በውስጣቸው እንዲፈቱት ስለሚያግዝ ነው፡፡ ነገር ግን ከጉዳዩ ባለቤቶች እጅ ወጥቶ ጽንፈኛ ፖለቲከኞች ሲረባረቡበት፣ በግራና በቀኝ እንደ ሰደድ እሳት የሚስፋፋው ፕሮፓጋንዳ የሰላም አማራጮችን በማጥበብ ግጭት ያስከትላል፡፡ መንግሥታዊ መዋቅሮች፣ የፀጥታ አካላት፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የተለያዩ ፍላጎቶችን የሚወክሉ ማኅበራትና ድርጅቶች ገለልተኝነትን ማሳየት አለባቸው፡፡ ልዩነትን ካጋጋሉ ግን ገላጋይ ጠፍቶ ዕልቂትና ውድመት ይከተላል፡፡ ለስክነትና ለትዕግሥት ቦታ የማይሰጡ አካላት ሰላማዊ አማራጮችን እያደፈረሱ ተገቢ ያልሆኑ ድርጊቶችን ሲፈጽሙ፣ በተለይ በማኅበራዊ የትስስር ገጾች ከአፅናፍ እስከ አፅናፍ እየተሰራጩ ቁርሾውን ያባብሳሉ፡፡ አሁንም በምሥልና በድምፅ የሚሰራጩ መረጃዎች የብዙዎችን ስሜት እያጎሹ ነው፡፡ በጉዳዩ ዙሪያ የሚሰሙ ትንታኔዎችና የሚነበቡ ጽሑፎች በአብዛኛው ከገንቢነት ይልቅ አፍራሽነት ላይ ያተኮሩ በመሆናቸው፣ በዚህ አሳሳቢ ወቅት ስክነትና መረጋጋት እንዲኖር ለአገር አሳቢ ወገኖች ድምፃቸውን ማሰማት ይጠበቅባቸዋል፡፡
ከዚህ ቀደም ጽንፈኛ ፖለቲከኞች በቀሰቀሱት ግጭት ዜጎች በማንነታቸው እየተሳደዱ ሲገደሉ፣ ንብረታቸው እየተዘረፈ ሲፈናቁሉና ሜዳ ላይ ሲጣሉ ከጊዜያዊ ዋይታ በስተቀር ለአገር የተረፈ ነገር የለም፡፡ አሁንም ሃይማኖትን ከፖለቲካ ጋር መቀየጥ የሚፈልጉ በግራም ሆነ በቀኝ ያሉ ኃይሎች፣ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻውን በስፋት ተያይዘውታል፡፡ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻው ዓላማ አንዱን ወገን አስቆጥቶ ስህተት እንዲሠራ ማደፋፈር ነው፡፡ ከሴራው በስተጀርባ ያሉ ደግሞ ድምፃቸውን አጥፍተው የማኅበራዊ ትስስር ገጾችን በማንቀሳቀስ፣ የሚፈልጉትን ዓላማ ለማሳካት ማባሪያ የሌለለው የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ውስጥ ተሰማርተዋል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ መረን የለቀቀ ድርጊት ካልተገታ፣ ‹‹የማን ቤት ጠፍቶ የማን ሊበጅ፣ የአውሬ መፈንጫ ይሆናል እንጂ›› በመባባል የጥፋት አዘቅት ውስጥ ዘው ተብሎ ይገባል፡፡ ያኔ ግን ማጣፊያው ስለሚያጥር ከሚታሰበው በላይ ዕልቂትና ውድመት ሊከተል ይችላል፡፡ ይህ ማስፈራሪያ ሳይሆን አፍጦና አግጦ የሚታይ ሥጋት የተላበሰ እውነት ነው፡፡ ጊዜው ሳይረፍድ ውጥረቱ ይርገብ!