ኢትዮጵያ ስንዴን ለዓለም ገበያ ለማቅረብ የሚያስችላት ደረጃ ላይ መድረሷ ተነግሯል፡፡ ለመጀመርያ ጊዜ ስንዴን ለውጭ ገበያ ለማቅረብ መቻሏን የሚያረጋግጥ መርሐ ግብር ባለፈው ሳምንት ተበስሯል፡፡ ‹‹ኢትዮጵያ ከራሷ ፍላጎት አልፋ ለውጭ ገበያ የሚተርፍ ስንዴ ማቅረብ ችላለች›› መባሉ በራሱ መልካም ዜና ነው፡፡
በእርግጥም ባለፉት ሦስት ዓመታት እዚህ ደረጃ ላይ ለመድረስ ብዙ ሲሠራ ቆይቷል፡፡ ተነሳሽነቱና በተግባር የታየው ክዋኔ የበለጠ ውጤታማ የሚሆነው ግን ጅምሩን በአግባቡ ማስቀጠል ሲቻል ነው፡፡ በአንድ በስንዴ ብቻ ሳይሆን ሌሎች ምርቶችንም እንዲህ ባለው አሠራር ምርታማነትን ማጎልበት ቢቻል ደግሞ በአጭር ጊዜ ለውጥ ሊመጣ ይችላል ተብሎ ይታመናል፡፡
‹‹ኢትዮጵያ በስንዴ ምርት ራሷን ችላ ለውጭ ገበያ የሚቀርብ ትርፍ ምርት አምርታለች፣ ማምረት ብቻ ሳይሆን ለመላክ በቅታለች›› የሚለውን ዜናም በሌሎች ምርቶች ላይ እንሰማ ዘንድ ብርቱ ምኞታችን ነው፡፡
ከሰሞኑ የስንዴ የወጪ ንግድ ጋር በተያያዘ ግን አንድ በእጅጉ ሊታሰብበት የሚገባ ጉዳይ አለ፡፡ ይህም ኢትዮጵያ በምርት ዘመኑ ከራሷ ፍላጎት በላይ የሆነ የስንዴ ምርት ካመረተች የስንዴ ገበያም መረጋጋት አለበት፡፡ በአገር ውስጥ ያለውን የስንዴ ገበያ ማረጋጋት ካልተቻለ ለውጭ ገበያ ብቻ ማቅረባችን የመጨረሻ ስኬት አይሆንም፡፡ ትርፍ ምርት ተመርቶ የተረጋጋ ገበያ ከሌለ፣ ስንዴን ግብዓት በማድረግ የሚመረቱ ምርቶች የዋጋ ላይ ለውጥ ካላሳዩም አንድ የተጓደለ ነገር እንዳለ ሊያመላክተን ይገባል፡፡
ትርፍ ማምረት መቻላችን ዳቦ ላይ የዋጋ ለውጥ ማምጣት አለበት፡፡ የዱቄት ዋጋ ቅናሽ ማሳየት ይኖርበታል፡፡ የስንዴ ግብይት ያለ ችግር በነፃ ገበያ ሥርዓት እንዲጓዝ ዕድል የሚሰጥም ነውና ይህንን አጋጣሚ ዋጋ ለማረጋጋት መጠቀም ያስፈልጋል፡፡
ኢትዮጵያ ስንዴን ለውጭ ገበያ ማቅረብ መጀመሯ በተበሰረበት ሰሞን ግን፣ የስንዴ ግብይት ችግር ውስጥ እየገባ ስለመሆኑ መነገሩ በራሱ የሚነግረን ነገር አለ፡፡ ለዚህም ነው ትርፍ ማምረትና ለውጭ ገበያ ማቅረብ ብቻ ሳይሆን፣ የአገር ውስጥ የግብይት ሥርዓቱን በሚገባ ማስፈጸም ይገባል የምንለው፡፡ ስንዴ ለውጭ ገበያ ማቅረብ መቻላችንን እንደ ትልቅ ስኬት እንደተቀበልነው ሁሉ፣ የአገር ውስጥ ግብይቱንም በአግባቡ በማስተዳደር ገበያውን ማረጋጋት ልክ ለውጭ ገበያ የተሰጠውን ትኩረት ያህል ሊሰጠው ይገባል፡፡
ከሰሞኑ የዱቄት ፋብሪካዎች የሚፈጩት ስንዴ አጥተው ተቸግረናል ማለታቸው ስንዴ ለውጭ ገበያ ማቅረብ መቻላችን እንጂ፣ የአገር ውስጥ ግብይቱ ዙሪያ ብዙ የታሰበበት እንዳልሆነ ያሳየናል፡፡ ስለዚህ ስንዴን ለውጭ ገበያ ለማቅረብ የተደከመውንና የተገኘውን ውጤት በኩራት እንደተቀበልነው ሁሉ፣ የአገር ውስጥ ግብይቱም ፈር እንዲይዝ ያስፈልጋል፡፡
ቁልፍ ጉዳይ እንደተነገረንም ትርፍ ምርት ተገኝቷል፡፡ ይህ ማለት ከፍላጎት በላይ ስንዴ አለ ማለት ነው፡፡ ከፍላጎት በላይ ምርት ካለ ደግሞ ዋጋ መረጋጋት ይችላል ማለት ነው፡፡ እውነታው ይህ ከሆነ ጥሬ ስንዴውንም ሆነ ስንዴን ግብዓት በማድረግ የሚመረቱ ምርቶች ሁሉ ዋጋቸው ሊረጋጋ መቻል አለበት፡፡ አሁን የምናየው ግን ይህንን አይደለም፡፡ ጭራሽ ዋጋቸው ከፍ ብሎ ከመታየቱም በላይ ገበያ ላይ እጥረት እየታየ ነው፡፡ ይህ ጉዳይ ሊያሳስብ ይገባል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየጨመረ ያለው የዳቦ ዋጋ፣ ምርት ተትረፈረፈ በተባለበት ወቅት ዋጋው መጨመሩ ለምን? የሚል ጥያቄ እንድናነሳ ያስገድደናል፡፡
አንዳንድ ዳቦ ቤቶች የዱቄት አቅርቦት አንሶብናል ዋጋም ጨምሮብናል በሚል ሰበብ እያደረጉ ያሉትን የዋጋ ጭማሪ እንዲያቆሙ ብቻ ሳይሆን፣ የጨመሩትንም ዋጋ እንዲቀንሱ ከተፈለገ የስንዴ የግብይት ሒደቱን በአግባቡ ማስኬድና በቂ ምርት ማቅረብ ያስፈልጋል፡፡ ስንዴን ወደ ውጭ እየላክን ነው በሚል ሰበብ አገሬው መጎዳት የለበትም፡፡ መንግሥት ከበቂ በላይ ምርት መመረቱን ባወጀበት አገር፣ ‹‹የምንፈጨው ስንዴ አጣን›› የሚሉ ዱቄት አምራቾችና ‹‹ለዳቦ የምንጠቀምበት ዱቄት አጣን›› የሚሉ ዳቦ ቤቶች ሊኖሩን አይገባም፡፡
በነገራችን ላይ መንግሥት ቁጥጥር ያደርግባቸዋል የተባሉ ዳቦ ቤቶች አሁን የሚሸጡት የዳቦ መጠንና እየጠየቁ ያሉት ዋጋ አስደንጋጭ ለመሆኑ አንዱ ምክንያት በቂ ግብዓት እጦት መሆኑም ሊሰመርበት ይገባል፡፡ ከዚህ ቀደም ዳቦ ቤቶች ምን ያህል ግራም በምን ያህል ዋጋ መሸጥ እንደሚኖርባቸው ተጠቅሶ ሲሠራበት የነበረው አሠራር ዛሬ እየታየ አይደለም፡፡ ከመንግሥት ቁጥጥር ውጪ ሆነው እንዲሠሩ የተፈቀደላቸውም ዳቦ ቤቶችማ ዋጋቸው አልቀመስ እያለ ነው፡፡
በአጭሩ ኢትዮጵያ በተለይ በዚህ የምርት ዘመን ከአገር ውስጥ ፍላጎቷ በላይ ማምረት መቻሏን በተለያየ መንገዶች ማረጋገጥ የተቻለ ሲሆን፣ ይህ ምርት ገበያውን ማረጋጋት አለበት፡፡ ከፍላጎት በላይ ምርት ባለበት አገር እጥረት ሊሰማ አይገባም፡፡ የዋጋ ጭማሪም መታየትም የለበትም፡፡ መንግሥት ከአገር ውስጥ ፍላጎት ተሟልቶ የተረፈውን ምርት ለውጭ ገበያ ለማቅረብ መወሰኑ መልካም ቢሆንም፣ የአገር ውስጥ ፍላጎት ተሟልቷል የሚባለው መቼና ምን ሲሆን ነው? የአገር ውስጥ ገበያውስ ምን ይመስላል? ብሎ ማየት ይኖርበታል፡፡ ቢያንስ በበቂ ሁኔታ ምርቱ ቀርቦ ዳቦ ላይ በዋጋም ሆነ በመጠን የመጣውን ለውጥ እንዲያሳየን እንፈልጋለን፡፡ በተለይ በተለይ የስንዴ ግብይትን ነፃ ማድረግ የመንግሥት ወቅታዊ ሥራ መሆን አለበት፡፡ ግብይቱ በተመረጡ ሰዎች ብቻ እንዲካሄድ ማድረግ አጠቃላይ የግብይት ሥርዓቱን ከማባባስ በላይ ለዋጋ ንረትም ምክንያት ስለሚሆን የስንዴ ዋጋ በገበያ የሚወሰንበት አሠራር ይዘርጋ!