በዓለም አቀፍ ደረጃ ከሚከናወኑ ዓመታዊ የጎዳና ውድድሮች መካከል አንዱ የሆነው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ አሥር ኪሎ ሜትር የጎዳና ሩጫ ለሁለተኛ ጊዜ የዓለም ምርጥ ሁለተኛ ሆኖ ተመረጠ፡፡
በዓለም አቀፍ ደረጃ ከሚታወቁ የስፖርት ጋዜጦች አንዱ የሆነው ራነር ወርልድ (Runner World) ባወጣው መረጃ መሠረት፣ በዓለም ላይ ከሚከናወኑ የ10 ኪሎ ሜትር ውድድሮች አንዱ የሆነው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ በምርጥነት ተመርጧል፡፡
ጋዜጣው የኢትዮጵያን ውድድር አንደኛ አድርጎ ሲመርጥ የለንደኑን ቪታሊታ 10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ሩጫ ሁለተኛ፣ እንዲሁም የፓሪሱን 10 ኪሎ ሜትር ውድድር ሦስተኛ በማድረግ መምረጡን ይፋ አድርጓል፡፡
የታላቁ ሩጫ ዓመታዊ ውድድር መከናወን ከጀመረ 22 ዓመታትን የተሻገረ ሲሆን፣ ደማቅ ሕዝባዊ ውድድር ከመሆኑም በላይ፣ ለበርካታ አትሌቶች የውድድር ዕድል በመፍጠር በዓለም አቀፍ ደረጃ መድረክ ደምቀው እንዲታዩ የራሱን አስተዋጽኦ ማበርከት ችሏል፡፡
ከዚህም ባሻገር በየዓመቱ የተለያዩ ውድድር ዓይነቶችን እያበዛ፣ በርካታ የውድድር ዕድሎችን ከመፍጠር ባሻገር፣ ማኅበረሰቡ ስፖርትን የዘወትር እንቅስቃሴው አንዱ አካል እንዲያደርግ የራሱን አሻራ ማኖር ችሏል፡፡
ከዚህም ባሻገር በአዲስ አበባ ከተማ ከሚያሰናዳቸው ውድድሮች ባሻገር በተለያዩ የክልል ከተሞች ውድድሮችን እያከናወነ ይገኛል፡፡