Thursday, June 1, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -

የተመረጡ ፅሑፎች

መንግሥት ለመኖሪያ ቤቶች ችግር ቀዳሚ ትኩረት ይስጥ!

አዲስ አበባን ጨምሮ ትልልቅ በምንላቸው የኢትዮጵያ ከተሞች ካሉባቸው በርካታ ችግሮች መካከል የመኖሪያ ቤት ዕጦት በቀዳሚነት ሊጠቀስ ይችላል፡፡ በተለይ በአሁኑ ወቅት ጎጆ ቀልሶ ለመኖር ከማይቻልበት ደረጃ ላይ ተደርሷል፡፡ በጋራም ሆነ በተናጠል ቤት ለመገንባት የሚቻልበት ዕድል እጅግ የጠበበና እንደ አማራጭ የሚቀርብ አሠራር እየጠፋ ነው፡፡ ዜጎች መሠረታዊ የሚባለውን የመኖሪያ ቤት ችግራቸውን ለመቅረፍ የሚያስችሉ አማራጮች ከመነፈጋቸውም በላይ ቤት ለማግኘት የሚያስችሉ አሠራሮች ጭምር እንዲቋረጡ መደረጋቸው ተስፋ እያስቆረጠ ነው፡፡ ጥቂት የሪል ስቴት አልሚዎች የሚያቀርቡት የመኖሪያ ቤቶች ቢኖሩም እንኳን፣ ለባለገንዘቦች ብቻ የሚደርሱና ዋጋቸውም የማይቀመስ ሆኖ የመገኘቱ ጉዳይ በእጅጉ ያሳስባል፡፡ 

በዚህ ላይ በግል የሪል ስቴት አልሚዎች የሚያቀርቡት የመኖሪያ ቤቶች ዋጋቸው ብቻ ሳይሆን በርካታ የአሠራር ችግር ያለባቸው ናቸው፡፡ ስለዚህ የግል ሪል ስቴት አልሚዎች የአዲስ አበባ የመኖሪያ ቤት ችግርን ከመቅረፍ አንፃር ያላቸው ፋይዳ እዚህ ግባ የማይባል ነው፡፡ ይበልጡኑ ደግሞ የሚጠየቅባቸው ዋጋ በመኖሪያ ቤት ዕጦት የሚሰቃየውን አብዛኛውን ነዋሪ አቅም ያላገናዘበ በመሆኑ ጥሩ አማራጭ ይሆናሉ ተብሎ አይታሰብም፡፡ በእርግጥ አሠራራቸውን እንዲያስተካክሉ የሚደረግበት አሠራር ቢዘረጋ እንደ አንድ አማራጭ ሊወሰዱ የሚችልበት ዕድል ቢኖሩም፣ ጉዳዩን ነገሬ ብሎ የሚከታተል ባለመኖሩ እነሱ ላይ ተስፋ ማድረግ የሚቻል አይሆንም፡፡  

ስለዚህ ብዙዎች እንደ አማራጭ የሚያዩትና ተስፋም ተደርጎበት የነበረው የጋራ መኖሪያ ቤቶች ግንባታ ነው፡፡ ነገር ግን ይህንን መልካም ጅምር በቅጡ ማስተዳደር ባለመቻሉ፣ እስካሁን ለተመዘገቡ ቤት ጠባቂዎች እንኳን በአግባቡ ለማድረስ አልተቻለም፡፡ ጭራሽ ከዚህ በኋላ የጋራ መኖሪያ ቤቶችን መገንባት ውስጥ መንግሥት እጁን እንደማያስገባ መግለጹ በራሱ የከተማዋን የቤት ችግር የበለጠ አወሳስቦታል፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ መንግሥት የጋራ መኖሪያ ቤት ታገኛላችሁ ብሎ የመዘገባቸውና በዚሁ መሠረት የቆጠቡ ዜጎች በተገባላቸው ቃል መሠረት የተባለው የጋራ መኖሪያ ቤት ሊደርሳቸው ሲገባ የፍትሕ ያለ የሚለውን ድምፃቸውን የሚሰማ ጠፍቷል፡፡ ይህ የሚያሳየን ለዚህ አንገብጋቢ ጉዳይ ሰሚ መታጣቱን ብቻ ሳይሆን፣ ቤት ቀልሶ ለመኖር የተሻለ አማራጭ የተባለው አሠራር መዳፈኑን ነው፡፡ 

መንግሥት አሁን ካለው ችግር አንፃር የጋራ መኖሪያ ቤቶችን በማስገንባት እያደገ የሚሄደውን ፍላጎት ከሥር ከሥር ለማቃለል እስከ ብዙ ችግሮቹም ቢሆን በጋራ መኖሪያ ቤት ግንባታ ውስጥ መኖር ይገባው ነበር፡፡ ሆኖም ከዚህ ሥራ ወጥቻለሁ ካለ ቢያንስ ለእስካሁኖቹ ተመዝጋቢዎች በአግባቡ ማስተናገድ ግዴታው ሊሆን ይገባል፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፣ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ግንባታን ማስተናገድ አልችልም ካለ ሌላ አማራጭ ይዞ መቅረብና ዜጎች እንደ አቅማቸውና ወረፋቸው የቤት ባለቤት የሚሆኑበት አሠራር መዘርጋት ግዴታው ነው፡፡

ምክንያቱም አንድ ዜጋ ቢያንስ በአቅሙ የራሱ መጠለያ የሚያገኝበት ዕድል ሳይመቻች፣ ሁሉ ነገር ተዘጋግቶ መቀመጥ ተገቢ ስለማይሆን ነው፡፡ ዛሬ ላይ በሊዝ (እሱም የለም) መሬት ተጫርቶ ገዝቶ መኖሪያ ቤት ለመቀለስ የሚችል የከተማም ነዋሪ ይኖራል ተብሎ አይታሰብም፡፡ ለመኖሪያ ቤት ግንባታ ተብሎ የተከለለ መሬት በሌለበት ከሁሉም በላይ የዜጎችን የመኖሪያ ቤት ችግር ለማቃለል የአጭር፣ የመካከለኛና የረዥም ጊዜ ዕቅድ ባልተያዘበት ሁኔታ የጋራ መኖሪያ ቤት ግንባታን ላለመቀጠል መወሰን ፈፅሞ ተቀባይነት የለውም፡፡

በእርግጥ በፌዴራል በቤቶች ኮርፖሬሽን በኩል እየተሠሩ ናቸው የሚባሉ ሥራዎች ያሉ ቢሆንም፣ እነዚህን ቤቶች ለማግኘት የሚችልበት መንገድ ጠባብ ነው፡፡ የሚተላለፉበት መንገድ አይታወቅም ወይም ሲገለጽ አይሰማም፡፡ 

ስለዚህ የቤቶች ኮርፖሬሽን የመኖሪያ ቤት ችግር ለመቅረፍ በአሥር ዓመት እሠራለሁ ብሎ ያቀደውን ቤት መገንባት ቢቻል እንኳን ዜጎች ይህንን ቤት እንዴት እንደሚያገኙ በግልጽ የተቀመጠ ነገር አለመኖሩ በራሱ ብዥታ ይፈጥራል፡፡

ከጋራ መኖሪያ ቤቶች ልምድ እንዳየነው ቢያንስ የተመዘገቡና የቆጠበው ሰዎች ጊዜው ቢረዝምም፣ በተፈለገው የጥራት ደረጃ የተገነባና ያለቀ ቤት ባይረከቡም ከብዙ ድካም በኋላ ቤት ማግኘት መቻላቸውን በራሱ መልካም ነበር፡፡ አሁን ግን ዓመታት ጠብቆ ቤት ለማግኘት የሚቻልበት ዕድል እየተዳፈነ መምጣቱ በገዛ አገራችን አንገታችንን የምናስገባበት አጥተን እንደኖርን እየተፈረደብን ይሆን? ግራ ያጋባል፡፡

 በቤቶች ኮርፖሬሽን በኩል እየተገነቡ ያሉ ቤቶች (ያለቁ መኖራቸውም ይታወቃል) ለዜጎች የሚተላለፉበት መንገድ እስካልታወቀ ድረስ ፍትሐዊ አሠራር ይኖራል ተብሎ አይታሰብም፡፡ 

ስለዚህ የተለያዩ አማራጮችን ማፈላለግ የመንግሥት ቁልፍ ተግባር መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ፣ በትክክል የቤት ፈላጊዎችን ቁጥር በሥርዓት አደራጅቶ ቤቱ መቼም ይድረሰው ሁሉም ዜጋ በእኩል የሚስተናገድበት አሠራር ሊኖር ይገባል፡፡ ዛሬ የብዙዎች ችግር የሆንን የመኖሪያ ቤት ችግር ለመቅረፍ አማራጭ የሚሆነው የጋራ መኖሪያ ቤቶችን በመገንባት ኅብረተሰቡ በቆጠበውና በተመዘገበበት ቅደም ተከተል እንዲስተናገድ ማድረግ አንድ አማራጭ ተደርጎ መወሰድ አለበት፡፡ ሁለተኛ መንግሥት በትክክል ቤት የሌላቸውን ዜጎች በመለየት በጋራ ረዣዥም የጋራ መኖሪያ ቤቶችን እንዲገነቡ ዕድል ሊሰጥ ይገባል፡፡ የመንግሥት ቤቶች ኮርፖሬሽንም ከኮንዶሚኒየሞች ግንባታ በተሻለ እየገነባቸው ያሉ መኖሪያ ቤቶችን ግንባታ እያሰፋ ከሄደ ለኅብረተሰቡ እንዴት እንደሚደርሱ በግልፅ አሳውቆ በአማራጭነት የቀረበ ጥሩ ዕድል መሆኑን ማሳየት አለበት፡፡ የሪል ስቴት አልሚዎችም ቢሆኑ ችግሩን ለማቃለል እንደ አንድ አማራጭ ተወስደው ብዙኃኑን ሊደርሱ የሚችሉ የጋራ መኖሪያ ቤት እንዲገነቡ የሚያስገድድ ሕግ መውጣትም ከብዙ አማራጮች አንዱ ሊሆን ስለሚችል በዚህ ላይ መትጋት ያስፈልጋል፡፡ 

ሥር እየሰደዱ በመሆኑ ልዩ ትኩረት የሚያስፈልገው ነው፡፡ የችግሩ መባባስ የሚፈጥረውንም ማኅበራዊ ቀውስ ልብ ማለትም ያሻል፡፡ አሁን እያየን ያለነው ነገር ችግር ለማቃለል ይተገበራሉ ተብለው በተለያዩ ወቅቶች ሲነገሩ የነበሩ አንዳንድ ዕቅዶች እንኳን መሬት ላይ እየወረዱ አለመሆኑም ጉዳዩ ትኩረት እንደተነፈገው ያሳያል፡፡ በመሆኑም የመኖሪያ ቤት ችግርን ለመቅረፍ ከወሬ ያለፈ ተግባር የሚያሻ ሲሆን፣ መንግሥት ያሉትን አማራጮች በሙሉ መጠቀም ግድ ይለዋል፡፡ ችግሩን ለመቅረፍ እስካሁን ከታዩ አማራጮች ሁሉ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ግንባታ ግን የተሻለው አማራጭ ሊሆን ይገባል፡፡

Latest Posts

- Advertisement -

ወቅታዊ ፅሑፎች

ትኩስ ዜናዎች ለማግኘት