ሶማሊያ መፍረክረኳን ተከትሎ እ.ኤ.አ. በ1991 ራሷን ነፃ አገር አድርጋ በሰየመችው ሶማሌላንድ ሰላም ደፍርሶ ውጥረት መንገሥ ከጀመረ ወር ተቆጥሯል፡፡ ሶማሌላንድ ነፃ አገር ስለመሆኗ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት ባታገኝም፣ በሶማሌና በቀጣናው ካለው አለመረጋጋት አንጻር ሰላሟ ተጠብቆ ከ30 ዓመታት በላይ ዘልቃለች፡፡
ከቅርብ ሳምንታት ወዲህ ግን ፖለቲካዊ ውጥረት የነገሠባት ሶማሌላንድ፣ ውጥረቱ በመንግሥት ኃይሎችና ለሶማሊያ መንግሥት ታማኝ በሆኑ ሚሊሻዎች መካከል ግጭት እንዲፈጠር አድርጓል፡፡
ግጭቱ ነዋሪዎች እንዲፈናቀሉ፣ እንዲሰደዱና እንዲሞቱ ከማድረጉ በተጨማሪ በሶማሌላንድና በሰሜን ሶማሊያ ከፊል ራስ ገዝ አስተዳደር ባላት ፑንትላንድ መካከል የይገባኛል ጥያቄ ያለበትን የሳስ አኖድ ዋና የንግድ መስመር አስተጓጉሏል፡፡
ግጭቱ ከ185 ሺሕ በላይ ሰዎች እንዲፈናቀሉ ማድረጉን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሲገልጽ፣ በሥፍራው ከፍተኛ ግጭት መኖሩንም የአካባቢው ጎሳ መሪዎች መግለጻቸውን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
በሶማሌላንድ የነገሠውን ውጥረትና ጥቃት ለማስቆም ሶማሊያ እየሠራች መሆኑን ደግሞ የሶማሊያ ፕሬዚዳንት ሐሰን ሼኪ ሞሐመድ በዚህ ሳምንት ለአልጀዚራ ተናግረዋል፡፡
በሶማሌላንድ፣ በአልሸባብና በአገሪቱ የወደፊት ዕጣ ፈንታ ዙሪያ ለአልጀዚራ ማብራሪያ የሰጡት ፕሬዚዳንት ሞሐመድ፣ ከሶማሊያ ተገንጥላ በምትገኘው ሶማሌላንድ ሰላም ተመልሶ እንዲሰፍን በቅርበት እየሠሩ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በሶማሌላንድ ባለሥልጣናትና በአካባቢው ጎሳ ኃይሎች መካከል የተፈጠረውን ግጭት በማንሳትም ‹‹አንድነት ብቸኛው የሰላም አማራጭ እንደሆነ እናምናለን፡፡ ሆኖም ይህ አንድነት በግጭት እንዲመጣ አንፈልግም፡፡ ግጭት ሁኔታዎችን ያባብሳል፤›› ብለዋል፡፡
ግጭቱ የተነሳው በሶማሌላንድ ያሉ የጎሳ መሪዎች ሳስ አኖድ፣ ሳናግ እና ካይን የተባሉ ቀጣናዎችን ከሶማሊያ ጋር መልሰው ለመዋሃድ ያላቸውን ፍላጎት ከገለጹና ሕዝቡ ድጋፍ እንዲሰጣቸው ከጠየቁ በኋላ ነው፡፡
ፕሬዚዳንት ሞሐመድ እንደሚሉት፣ ይህንን የመዋሃድ ሐሳብ ከማየት በፊት በሶማሌላንድ እንዴት ግጭት ማስቆም ይቻላል በሚለው ላይ እየተሠራ ሲሆን፣ ግጭቱ ሲቆም የውይይት መድረክ ይኖራል፡፡
ፕሬዚዳንት ሞሐመድ ይህንን ከማለታቸው አስቀድሞ የሶማሌላንድ ባለሥልጣናት ግጭቱን ለማስቆም የተኩስ አቁም ማድረጋቸውን ካስታወቁ ከጥቂት ቀናት በኋላ ሶማሊያ የሶማሌላንድ ኃይሎችን ማጥቃት መጀመሯን ይፋ ማድረጋቸው ይታወሳል፡፡
በግጭቱ ሳቢያ ከቀያቸው ከተፈናቀሉት ከ185 ሺሕ በላይ ሶማሌያውያን፣ 89 በመቶ ያህሉ ሴቶችና ሕፃናት መሆናቸውን ተመድ ሲያስታውቅ፣ በግጭቱ የሆስፒታል የኤሌክትሪክ፣ የኦክስጅን፣ የደም ባንክና ሌሎች አገልግሎቶች የወደሙ በመሆኑ ጉዳት የደረሰባቸውን ከ500 በላይ ሰዎችን ለማከም ፈተና መሆኑን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
በርካቶች በዛፍ ስር ወይም በተዘጉ ትምህርት ቤቶች ውስጥ ለመጠለል ተገደዋል፡፡ ሲሆን፣ በሶማሌላንድ ውስጥ ተፈናቅለው ከተቀመጡት በተጨማሪ 60 ሺሕ ያህል ሰዎች ወደ ኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል መግባታቸውንም ተመድ መግለጹ ይታወቃል፡፡ ከ100 በላይ ሰዎችም በግጭቱ ተገድለዋል፡፡
4.5 ሚሊዮን ዜጎች ያሏት ሶማሌላንድ የራሷን ገንዘብ አትማለች፡፡ የራሷ ፓስፖርት ያላት ሲሆን፣ የራሷን መንግሥትም ባለፉት 30 ዓመታት ስትመርጥ ቆይታለች፡፡ ሆኖም አገር መሆኗን ለዓለም አቀፍ መንግሥታት እንዲያውቁላት ብትጠይቅም ተቀባይነት አላገኘችም፡፡ ይህም ደሃና የተገለለች አገር እንድትሆን አድርጓታል፡፡
ሶማሌላንድ ያለፉትን 30 ዓመታት በሰላም ብታሳልፍም፣ ሰሞኑን የገጠማት ግጭት በተለይም ከሦስቱ ቀጣናዎች የተነሳው ‹‹ከሶማሊያ ጋር እንዋሃዳለን›› ጥያቄ ወደ ግጭት መርቷታል፡፡
የሶማሊያ መንግሥት ደግሞ ግጭቱን ለማርገብ እየሠራ መሆኑን አስታውቋል፡፡ ዓምና ሶማሌላንድ በዓለም አቀፍ መንግሥታት ተቀባይነት በምታገኝበት ዙሪያ የሶማሌላንድ የሕዝብ ምክር ቤት ተወካዮች ባዘጋጁት መድረክ፣ ሶማሌላንድ ከሶማሊያ ጋር እንደማትቀላቀል መንፀባረቁ ይታወሳል፡፡
በርካታ ፖለቲከኞችና ተማሪዎችም ሐሳቡን በመደገፍ በሃርጌሳ ሠልፍ መውጣታቸው አይዘነጋም፡፡