የተለያዩ የተፎካካሪ ፓርቲዎች ከሰሞኑ ጠቅላላ ጉባዔ እንዳያደርጉ መከልከላቸው ተቀባይነት የሌላውና በአስቸኳይ ሊቆም እንደሚገባ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አስታወቀ፡፡ ከሰሞኑ እናት ፓርቲና ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ) ጠቅላላ ጉባዔያቸው በፀጥታ ኃይሎች መከልከሉ፣ የአገሪቱን ፖለቲካ ዕድገት የሚያቀጭጭ መሆኑን የጋራ ምክር ቤቱ ገልጿል፡፡
የጋራ ምክር ቤቱ ዋና ሰብሳቢ መብራቱ ዓለሙ (ዶ/ር) ድርጊቱ የተከለከሉት ፓርቲዎች ጉዳይ ብቻ ሳይሆን፣ ‹‹እንደ አገር የሁላችንም ነው፤›› ብለዋል፡፡ ‹‹ለምርጫ ቦርድ፣ ለፌዴራል ፖሊስ፣ ለብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ደብዳቤ ጽፈናል፡፡ ድርጊቱን የፈጸሙትን ማን እንደሆኑ አናውቅም ነው የሚሉት፤›› በማለት ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
በዋናነት ፓርቲዎችን ጠቅላላ ጉባዔ አድርጉ የሚለው ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ መሆኑን የገለጹት መብራቱ (ዶ/ር)፣ ጉባዔ ለማካሄድ የተከለከሉ ፓርቲዎችን ችግር ለመፍታት ቦርዱ የበኩሉን ጥረት ማድረጉንና በተፈጠረው ችግርም ማዘኑን እንደሚያውቁ አስረድተዋል፡፡
ከከልካዮቹ መካከል የኦሮሚያ ክልል ፖሊሶች ይገኙበታል መባሉን በተመለከተ፣ ‹‹የኦሮሚያ ፖሊስ በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ምን ሥልጣን አለው? የአዲስ አበባ ከተማ ፖሊስ እያለ ይህ ተደርጎ ከሆነ እናጣራለን፤›› ሲሉ ነው መብራቱ (ዶ/ር) ምላሽ የሰጡት፡፡ ‹‹ይሁን እንጂ ከልካዩ ማንም ይሁን የሁለቱ ፓርቲዎች ጠቅላላ ጉባዔ እንዳይካሄድ መከልከል እንደ አገር ወዴት እየሄድን ነው የሚል ጥያቄ የሚያስነሳ ነው፤›› ብለዋል፡፡
የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ በቃሉ አጥናፉ፣ እሑድ መጋቢት 3 ቀን 2015 ዓ.ም. ፓርቲያቸው በጋምቤላ ሆቴል ጠርቶት የነበረው ጠቅላላ ጉባዔ የተከለከለው በፖሊሶችና ደኅንነቶች መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ፓርቲያቸው ከምርጫ ቦርድና ከሰላምና ፀጥታ ቢሮ ሕጋዊ ደብዳቤ ይዞ ስብሰባውን ቢጠራም፣ በጎን የፀጥታ ኃይሎች ባለሆቴሎችን በማስፈራራት ጉባዔውን እንዳሳገዱባቸው ገልጸዋል፡፡
‹‹በአንድ በኩል ጉባዔ ማድረግ ትችላለህ ትባላለህ፡፡ በሌላ በኩል ግን በሴራ እንዳትሰበሰብ ትከለከላለህ፡፡ የተያዘው የማፍያ ሥራ ዓይነት ነው፤›› በማለት አቶ በቃሉ ወቀሳ ሰንዝረዋል፡፡
ለምርጫ ቦርድ የተፈጠረውን ችግር በተመለከተ በሁለት ቀናት ውስጥ የጽሑፍ ሪፖርት እንደሚያቀርቡ የተናገሩት አቶ መብራቱ፣ ምርጫ ቦርድ ከመንግሥትም ሆነ ከሚመለከተው ጋር ተነጋግሮ መፍትሔ እንዲፈልግ ጠይቀዋል፡፡
‹‹ያለበለዚያ ግን ከዚህ ሁሉ ጭቅጭቅ ምርጫ ቦርዱ የራሱን አዳራሽ አዘጋጅቶ እዚያ ጠቅላላ ጉባዔያችንን ብናደርግ ይሻላል፤›› ብለዋል፡፡
ይህን ሐሳብ የተጋሩት የፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢ መብራቱ (ዶ/ር)፣ ምርጫ ቦርድ በራሱ ጽሕፈት ቤትም ሆነ በራሱ አዳራሽ ማዘጋጀትን ሊያስብበት ይገባል ብለዋል፡፡
የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ዋና ጸሐፊ የሆኑትና እንደ አንድ ፖለቲከኛ የግል ሐሳባቸውን ለሪፖርተር የተናገሩት ራሔል ባፌ (ዶ/ር)፣ የፓርቲዎች ጉባዔ መከልከል ብዙ ዓይነት ጉዳት አለው ብለዋል፡፡
‹‹በመጨረሻ ሰዓት የሚታገድ ስብሰባ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠር ሀብት ኪሳራ የሚያስከትል ነው፡፡ በተለይ አገራዊ የሆኑ ፓርቲዎች ከመላ አገሪቱ አባላትን ለመሰብሰብ ብዙ ወጪ ያወጣሉ፡፡ ይህን መሰሉ ክልከላ ከዚያም በላይ የሚኖረው ሥነ ልቦናዊ ተፅዕኖ ቀላል አይሆንም፤›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡
ምርጫ ቦርድ ችግሩ እንዲፈታ ብዙ እየሞከረ መሆኑን እንደሚያውቁ የጠቀሱት ራሔል (ዶ/ር)፣ ‹‹የፀጥታ ኃይሎች ዩኒፎርም የለበሱ ሰዎች ናቸውና ስብሰባዎቹን እያስቆሙ ያሉት ለዚህ ኃላፊነት ወስዶ ተጠያቂ ሊሆን የሚገባ አካል መኖር አለበት፤›› ብለዋል፡፡