- ታቦታቱን በእንግሊዝ ለሚገኘው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለመስጠት ሙዚየሙ አስቧል
ዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ ከ155 ዓመታት በፊት መቅደላ ላይ ከተሰዉ በኋላ ከአምባው የደረሰው በጄኔራል ናፒር የሚመራው የእንግሊዝ ጦር ወደ አገሩ ባዶ እጁን አልተመለሰም፡፡ በመቅደላ አምባ በንጉሠ ነገሥቱ ቴዎድሮስ (1847-1860) በተደራጀው ሙዚየም ውስጥ የሚገኙ የተለያዩ ውድ ቅርሶችን ዘርፎ እንጂ፡፡
በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ (1923-1967) ዘመንም ሆነ ከእሳቸው ንግሥና ቀጥለው በመጡት መንግሥታት ከፍተኛ ጥረት በተለያዩ ጊዜያት የተወሰኑ ቅርሶችና ንዋየ ቅድሳት (የቤተ ክርስቲያን ንዋዮች) መመለሳቸው ይታወሳል፡፡
በየዓረፍተ ዘመኑ እነዚህ የኢትዮጵያ ቅርሶች መነጋገርያ መሆናቸው አሁን እንደቀጠለ ነው፡፡ ወደ ትውልድ ቀያቸው ይመለሱ የሚለውም እያከራከረ ነው፡፡ ሰሞኑን በአውሮፓ የሚገኙ መገናኛ ብዙኃን በመቅደላ የተዘረፉት ቅርሶችን በተመለከተ አዳዲስ ዕይታዎችን ማቅረባቸው አልቀረም፡፡በእንግሊዝ ወታደሮች ከኢትዮጵያ የተወሰዱ በመቶዎች የሚቆጠሩ የባህል ቅርሶች በለንደን ከአዲስ ጥናት በኋላ ተለይተዋል የሚለውን ዘገባ ያቀረበው ኢቪኒንግ ስታንዳርድ ነው። ባለፈው ሳምንት በድረ ገጹ ባሠራጨው ዘገባው የአንድ ደራሲን ሥራ ተመልክቷል፡፡በኢትዮጵያ ውስጥ በጋዜጠኝነት ይሠሩ የነበሩት ደራሲ አንድሪው ሄቨንስ፡ ዘ ፕሪንስ ኤንድ ዘ ፕሉንደር የተባለው መጽሐፋቸው፣ እንግሊዛውያን እ.ኤ.አ. በ1868 በመቅደላ በፈጸሙት ወረራ ቅርሶቹን እንዴት እንደወሰዱት በዝርዝር የሚገልጽ ሆኖ፣ በዓይነት በዓይነት የተለዩ 538 ዕቃዎችን በለንደን ለይቷል፡፡ስብስቦቹ ብራናዎች፣ ከቁርጭራጭ የእጅ ጽሑፍ እስከ የንጉሣዊው ቤተሰብ የእጅ አምባርና አልባሳት፣ ንዋያተ ቅዱሳትንና ዘውድን ያካተቱ ናቸው፡፡ ቅርሶቹ በተለያዩ ቦታዎች ከዓበይት ተቋማት እስከ ምክር ቤት ስብስቦች ድረስ በሁሉም ቦታ ይገኛሉ፡፡ ደራሲው እንዲህም አሉ፣ ‹‹ወታደሮቹ ከዘረፏቸው መካከል ብዙዎቹ በቦርሳዎቻቸውና በኪሶቻቸው የያዟቸው ሁሉም ዕቃዎች ማለት ይቻላል በማሳያ ቦታዎች በዕይታ ላይ አይደሉም። የዝርፊያ ታሪኩን ለመንገር እነዚህን ነገሮች ተከታትዬአለሁ። መጽሐፌ ቅርሶቹ እንዲመለሱ የሚጠይቅ የቅስቀሳ መጽሐፍ አይደለም። ያ የኢትዮጵያ ጉዳይ ነውና››።በብዙኃኑ ከሚታወቁት አንዳንድ ዕቃዎች/ቅርሶች መካከል በዌስት ሚኒስተር አቢ እና በብሪቲሽ ሙዚየም ውስጥ የተቀመጡ ታቦቶች/ንዋየ ቅዱሳት፣ በቪክቶሪያና አልበርታ እጅ የሚገኙ ዘውድና ንጉሣዊ አልባሳት ይገኙበታል፡፡ ሌሎች ደግሞ በዌልኮም ስብስብ ውስጥ የእጅ ጽሑፎችን (ብራናዎች) የሚታወቁ ሲሆን፣ በሳውዝዋርክ ካውንስል እጅ የሚገኙት ከአንድ ሴንቲ ሜትር በታች የሚለኩ የክታብ ጥቅልሎች ከዚህ ቀደም ልብ ሳይባሉ ትኩረት ሳያገኙ ቆይተዋል።ቪክቶሪያና አልበርታ ቅርሶችን ለኢትዮጵያ በረዥም ጊዜ ትውስት ለመመለስን ፍላጎቱን ሲያሳይና ሲነጋገር፣ ዌልኮም ኮሌክሽን ምንም ዓይነት ቅርሶችን ስለመመለስ ጥያቄዎች እንዳልደረሱት፣ ነገር ግን ‹‹እንደ ሁኔታው በጉዳዩ ላይ ውሳኔዎችን እንደሚወስድ›› ተናግሯል። ዌስት ሚኒስተር አቤይ በበኩሉ፣ ‹‹የኢትዮጵያን ታቦት አስፈላጊነትና ጠቀሜታን ጠንቅቆ ያውቃል›› እና ‹‹በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ በጣም በተቀደሰ ቦታ ተጠብቆና ከዕይታ ተደብቆ›› መቀመጡን ገልጿል፡፡‹‹የእኛ ቀጣይ ምኞት እነዚህን ንዋየ ቅድሳት/ታቦታት በእንግሊዝ ለምትገኝ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በትውስት በመስጠት በትውፊታቸው መሠረት ቀሳውስት እንዲንከባከቧቸው ማድረግ ነው፤›› ያለው የብሪቲሽ ሙዚየም ነው።የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቅርስ አስመላሽ ኮሚቴ አባል አሉላ ፓንክረስት (ዶ/ር) ለኢቪኒንግ ስታንዳርድ በሰጡት ቃለ ምልልስ፣ የብሪታንያ ሙዚየሞች ‹‹እነዚህን ንዋዮች በመጠበቅ ለሰው ልጅ ትልቅ አገልግሎት ሰጥተዋል፤›› ያሉ ሲሆን፣ ነገር ግን እነዚህን ውድ ሀብቶችን የመመለስ ክርክርና ጥረት በሰፊው ይደገፋል ብለዋል፡፡የሕይወታቸውን የመጨረሻ ዓመታት ኢትዮጵያ ውስጥ የኖሩት የአሉላ አያት ሲልቪያ ፓንክረስት፣ በዘመናቸው ከመቅደላ ተዘርፈው የተወሰዱት ቅርሶች እንዲመለሱ ይወተውቱ ነበር፡፡ ‹‹አንዳንድ ነገሮች የበለጠ ጠቃሚ ስለሆኑ የመጀመሪያው ግልጽ የሆነው የሰው አካል/አፅም ነው መመለስ ያለበት፤ ከዚያም ንዋየ ቅዱሳት አሉ፤›› ማለታቸውን ዘገባው አስታውሷል።ይህም ሆኖ ሙዚየሞች ቅርሶችን ወደ መገኛ ትውልድ አገራቸው መመለስ አለባቸው የሚለው ክርክር እየጨመረ የመጣበት ጊዜ ነው፡፡ ለምሳሌ የብሪቲሽ ሙዚየም ከ200 ዓመታት በኋላ የኤልጂን እብነ በረድ ወደ ግሪክ ሊመለስ በሚችልበት ሁኔታ ላይ ‹‹ገንቢ ውይይቶችን›› ማድረጉን እንደቀጠለ፣ የካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲም የተዘረፈውን የቤኒን ነሐስ ሊመልስ እንደሆነ ማሳያዎች ናቸው።
በእንግሊዝ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ በዘመነ ቴዎድሮስ ከተዘረፉት ተንቀሳቃሽ ቅርሶች መካከል የተወሰኑትን ለማስመለስ በለንደን ከሚገኘው ከቪክቶሪያና አልበርት ሙዚየም ጋር ከዓመታት በፊት መነጋገር መጀመሩን በወቅቱ ዘግቧል፡፡
የቪክቶሪያና አልበርት ሙዚየም ካሉት ስብስቦች ውስጥ ለመመለስ ካሰባቸው መካከል የወርቅ ዘውድና ዘውዳዊ የሠርግ አልባሳት ይገኙበታል፡፡ የሙዚየሙ ምክትል ዳይሬክተር ቲም ሪቭ፣ “የዕደ ጥበብ ውጤቶቹን ወደ ኢትዮጵያ ስለሚመለሱበት መንገድ ከኢትዮጵያ ኤምባሲ ጋር በቅርበት እየተወያየን ነው፤” ማለታቸውን ዘጋርዲያን ጠቅሶ መዘገቡም ይታወሳል፡፡
ቀደም ሲል በለንደን ከተማ የሚገኘው ብሔራዊ የጦር ሙዚየም ለስድሳ ዓመታት በእጁ የነበረውን የአፄ ቴዎድሮስ ሁለት ቁንዳላዎች ለባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ማስረከቡ ይታወሳል፡፡
የአፄ ቴዎድሮስን መስዋዕትነት ተከትሎ በ1868 ዓ.ም. ከመቅደላ አምባ የተዘረፉት ቅርሶች በተለይ ከ500 በላይ የጽሑፍ ቅርሶች፣ የተለያዩ የፈጠራ ውጤቶች፣ የንጉሣውያን የወርቅ ዘውዶችና ጌጣጌጦች፣ እንዲሁም አሥር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታቦታት በእንግሊዝ የተለያዩ ሙዚየሞች ከመገኘታቸው በተጨማሪም በርካታ ቅርሶች በግለሰብ እጅ እንደሚገኙ ይታወቃል፡፡
የተዘረፉትን ቅርሶች ለማስመለስ ባለፉት መንግሥታት ከተደረጉት ጥረቶች ባሻገር “አፍሮሜት” የሚባለው የመቅደላ ቅርስ አስመላሽ ተቋም የበኩሉን ድርሻ በመወጣት ጥቂት ቅርሶች መመለሳቸው ይታወሳል፡፡
በአሁኑ ወቅትም የተለያዩ አካላትንና ታዋቂና አዋቂ ግለሰቦችን ያካተተ የኢትዮጵያ ቅርስ አስመላሽ ብሔራዊ ኮሚቴ መቋቋሙ ተነግሯል፡፡