ተፎካካሪ ፓርቲዎች ጠቅላላ ጉባዔያቸውን ለማካሄድ የአዳራሽ ኪራይ ከከፈሉ፣ አባሎቻቸውን ከተለያዩ አካባቢዎች ከጠሩና ከፍተኛ ወጪ ካወጡ በኋላ፣ በማይታወቁና ማንነታቸውን በማይገልጹ የፀጥታ ኃይሎች ክልከላ እየተደረገ ያለበት ሒደት፣ የመድብለ ፓርቲ ሥርዓቱን አደጋ ላይ ሊጥለው እንደሚችል የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አሳሰበ፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለጠቅላይ ሚኒስቴር ጽሕፈት ቤት በጻፈው ደብዳቤ እንዳስታወቀው፣ ለጽሕፈት ቤቱ ተጠሪ የሆኑ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች፣ ኤጀንሲዎችና መሰል ተቋማት መሰብሰቢያ አዳራሾቻቸውን ለተፎካካሪ ፓርቲዎች መሰብሰቢያነት እንዲፈቀዱ ጠይቋል፡፡
‹‹ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ተፎካካሪ ፓርቲዎች ጠቅላላ ጉባዔያቸውን ሆቴል ተከራይተው እንኳን ማካሄድ አልቻሉም›› ያለው ቦርዱ፣ በዚህ የተነሳ የመንግሥት ተቋማት የስብሰባ አዳራሾቻቸውን ክፍት ሊያደርጉላቸው ይገባል ብሏል፡፡
መጋቢት 7 ቀን 2015 ዓ.ም. ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የተጻፈው የምርጫ ቦርድ ደብዳቤ፣ የተፎካካሪ ፓርቲዎች ሕጉ በሚያዘው መሠረት የጠቅላላ ጉባዔ ስብሰባ በሆቴሎች ለማካሄድ እንቅፋት እየገጠማቸው መሆኑን ይገልጻል፡፡ በተቃራኒው ግን ገዥው ፓርቲ (ብልፅግና) በመንግሥት ተቋማት የመሰብሰቢያ አዳራሾች የፓርቲ ክዋኔዎቹን ያደርጋል ይላል፡፡
ከመድበለ ፓርቲ የፖለቲካ ሥርዓት አኳያ ተፎካካሪ ፓርቲዎችም ሆኑ ገዥው ፓርቲ ያለ አድልኦ፣ በእኩልነትና በፍትሐዊነት የመጠቀም መብት እንዳላቸው የምርጫ ቦርድ ደብዳቤ ይጠቅሳል፡፡
ለዚህ ሲባልም የሚመለከታቸው የመንግሥት ተቋማት ለተፎካካሪ ፓርቲዎች የስብሰባ አዳራሾቻቸውን ክፍት ማድረግ እንዳለባቸው ያሳስባል፡፡
ረቡዕ መጋቢት 6 ቀን 2015 ዓ.ም. ቦርዱ አሳሳቢ ሆኗል በማለት ስለገለጸው የተፎካካሪ ፓርቲዎች የጠቅላላ ጉባዔ መከልከል በተመለከተ በሰጠው መግለጫ፣ የቦርዱ ሰብሳቢ ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ይህንኑ ጉዳይ አንስተውት ነበር፡፡
‹‹የተቃዋሚ ፓርቲዎች ያለ ክፍያ በነፃ በመንግሥት የስብሰባ አዳራሾች መሰብሰብ ይችላሉ፡፡ ይሁን እንጂ ይህን ለማድረግ ችግር ይገጥማቸዋል፡፡ በእኛ በኩል ችግሩ ከግንዛቤ እጥረት የሚፈጠር ነው ብለን ለሁሉም የመንግሥት ተቋማት ደብዳቤ ጽፈናል፡፡ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮ ጀምሮ የፌዴራል ተቋማት አዳራሾች ለተቃዋሚዎች መሰብሰቢያነት ክፍት እንዲሆኑ መመርያ እንዲተላለፍ በደብዳቤ አስታውቀናቸዋል፤›› በማለት አብራርተዋል፡፡
ቦርዱ በሰጠው መግለጫ ከሰሞኑ በተቃዋሚ ፓርቲዎች ላይ እየደረሰ ያለው የጠቅላላ ጉባዔ መሰናከል አሳሳቢና ተቀባይነት የሌለው መሆኑን አስታውቋል፡፡
የጉራጌ አንድነትና ፍትሕ ፓርቲ (ጎጎት) ጠቅላላ ጉባዔ ማድረግ ቢችልም፣ አመራሮቹና የጠቅላላ ጉባዔ ሰነዶቹ በፌዴራል ፖሊስ ተይዘው ለደቡብ ክልል ፖሊስ መተላለፋቸውን ቦርዱ በመግለጫው ጠቅሷል፡፡
እናት ፓርቲና ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ) በጥቂት ቀናት ልዩነት ሊያደርጉዋቸው የነበሩ ጠቅላላ ጉባዔዎች ደግሞ፣ ስማቸው ተለይቶ ባልታወቀ የፀጥታ ኃላፊዎች መስተጓጎሉን ቦርዱ ገልጿል፡፡
ፓርቲዎቹ በሕግ የተጣለባቸውን ግዴታ እንዳይወጡ የሚያደርግ ብቻ ሳይሆን፣ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓቱንም አደጋ ላይ የሚጥል ነው ብሎታል፡፡
ይህ አካሄድ ተቀባይነት የሌለው ከመሆኑም በላይ ምርጫ ቦርድ በሕግ የተሰጠውን ኃላፊነት እንዳይወጣና ሥራውን እንዳያከናውን ከፍተኛ ጫና የሚያመጣበት ነው ሲል፣ የቦርዱ መግለጫ በአፅንኦት አስታውቋል፡፡