ኢትዮጵያ በመጭው ዓመት ልትተገብረው ላቀደችው የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ውስጥ የተጎጂዎችን ቅሬታ ሊያዳምጥ የሚችል የተጎጂዎች ማዕከልና ጥቃቅን የሆኑ ቅሬታዎችን ሊያዳምጡ የሚችሉ ባለሙዎች እንደሚያስፈልጉት ተገለጸ፡፡
በኢትዮጵያ ባለፉት ጊዜያት ተፈጠሩ የተባሉ በደሎችና የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች የተፈጠረውን ቁርሾና ቁስል ለማከምና ለማድረቅ ያስችላል የተባለለት የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ተሰንዶ ውይይት ተጀምሯል፡፡
መጋቢት 7 ቀን 2015 ዓ.ም. በሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ አማራጭ ሰነድ ላይ ከመላው ዓለም የተውጣጡና በተለያየ ደረጃ በሽግግር ፍትሕ ዙሪያ የሚሠሩ ዓለም አቀፍ ተቋማት፣ ጥናትና ምርምር ያደረጉ እንዲሁም መጽሐፍ የጻፉ ታላላቅ ባለሙያዎች በአዲስ አበባ ምክክር አድርገዋል፡፡
በምክክሩ ከተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ጽሕፈት ቤት የመጡ ተወካይ በውይይቱ እንደተናገሩት፣ የተጎጂዎች ማዕከል አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የዚህን ማዕከል አስፈላጊነት ሲያብራሩ ተጎጂዎች በበቂ መልኩ ሊሳተፉና ሊደመጡ እንዲችሉ የሚያደርግና በቀጣይ መንግሥት በቀጣይ ለሚያወጣቸው የፖሊሲ ግብዓቶች እንደ አንድ ምንጭነት ሊያገልግሉ ይችላሉ ብለዋል፡፡
በሌላ በኩል በውይይቱ የተገኙ አንድ ሌላ ተሳታፊ የተጎጂዎችን ጥቃቅን ቅሬታ ሊያዳምጡ የሚችሉ ገለልተኛ የሆኑና በዘርፉ የተሻለ እውቀትና መረጃ ያላቸው ዓቃቤ ሕጎች ሊኖሩ እንደሚገባ አስረድተዋል፡፡ በተመሳሳይ በአገር አቀፍ ደራጃ ይህን የሚያስፈጽም ኮሚሽን የሚቋቋም ከሆነ፣ በተመሳሳይ በተዋረድ በክልሎችም ራሱን ችሎ እንዲቋቋምና የታችኛው መዋቅር ድረስ ተንቀሳቅሶ ትክክለኛ ፍትሕ እንዲተገበር በማድረግ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲውን ተዓማኒ ማድረግ እንደሚያሰፈልግ ተናግረዋል፡፡
ኢትዮጵያ ካላት የረዥም ጊዜ ታሪክ የተነሳ በሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ችግሩን ለመለየት ወደ ሥራ ሲገባ ከሕዝቡ ሰፋ ያሉ ቅሬታዎች ሊነሱ ስለሚችሉ፣ ለዚህ በበቂ ሁኔታ መዘጋጀት እንደሚያስፈልግ የጠቀሱት ደግሞ ከደቡብ አፍሪካ የሰላምና ፍትሕ የተሰኘ ተቋም የመጡ ተሳታፊ ናቸው፡፡ ተሳታፊው አክለው የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ዘላቂና አስተማማኝ ሰላም ለመገንባት እንጂ እንዲያው ዝም ብሎ የሽግግር ፍትሕ ለማካሄድ በሚል ትልም መሆን የለበትም ብለዋል፡፡
ከአውሮፓ ኅብረት የፍትሕና የሽግግር ፍትሕ ተቋም የመጡ ተሳታፊ እንደተናገሩት፣ የሚዘጋጀው የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲና ወደ ሥራ ሲገባ በሚሰማው የሕዝብ ቅሬታ መካከል ልዩነት ሊፈጠር እንደሚችለ በመግለጽ የሕዝቡ ቅሬታ የተወሳሰበ ሊሆን ስለሚችል ተጎጂዎቹን ማዕከል ያደረገ ዘዴ እንደሚያስፈልግ አስረድተዋል፡፡
የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ አማራጭ ሐሳብ የያዘው ሰነድ ወደ ፖሊስ ከመቀየሩ በፊት በሰነዱ ላይ በቀጣይ በመላ አገሪቱ ወደ 59 መድረኮች እንደሚካሄዱበት ተገልጿል፡፡
በዚሁ ውይይት ሌሎች ተሳታፊዎች በሽግግር ፍትሕ ፖሊሲው ትግበራ ላይ ምን ዓይነት እርቅ እንደሚተገበርና የሚተገበረው የዕርቅ ዓይነት እንዴት አስፈላጊ እንደሚሆን መብራራት እንዳለበት ተነስቷል፡፡ በመሆኑም የፖለቲካ፣ የሃይማኖት፣ የወታጣቶች፣ የአገር ሽማግሌዎች ወይስ የሲቪክ ማኅበራት የእርቅ ዓይነት ተብሎ መለየት እንዳለበት ተጠይቋል፡፡
በሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ አፈጻጸም ተቋማዊ ለውጦች የሚያስፈልጉ ከሆነ ሊደረግ የታሰበው ተቋማዊ ለውጥ ከሰብዓዊ መብት ጥሰቶች መሻሻል ጋር አብሮ ሊሄድ የሚችል ሊሆን እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡ በዚህ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ውስጥ ሙስና ላይ የተገናኙ ጉዳዮችም እንዲታዩ ሐሳባቸውን የሰነዘሩ ነበሩ፡፡
ከናይጄሪያ የመጡ ተሳታፊ ሲናገሩ የተጎጂዎችን ፍላጎት ሊመጥን የሚችል ሥራ ካልተሠራ ነገ መልሶ ሌላ በደል እንዲፈጸም ዕድል ይፈጥራል ያሉ ሲሆን በዚህ ሒደት ውስጥ የሕግ እውቀት ያላቸው የሰብዓዊ መብት ባለሙያዎች መኖር ቀጣይነቱን ያሳምረዋል ብለዋል፡፡
በኢትዮጵያ ያለው ፍላጎት መብዛት፣ ያለው ሁኔታ የተወሳሰበ በመሆኑ የሽግግር ፖሊሲው ሊመልሰው ያሰበውን ጥያቄ በሚመልስ መልክ መሆን እንዳለበትም ተጠቅሷል፡፡