- Advertisement -

አለመታደል ወይስ የለውጥ መጨንገፍ?

በተስፋዬ አባዶ

አገራችን

ኢትዮጵያ አኩሪ ታሪክ፣ መልካም ባህል፣ የሚያኖረን ያህል የኢኮኖሚ አቅም፣ የፖለቲካ አስተሳሰብ፣ አመለካከት፣ ጠንካራ ማኅበራዊ መስተጋብርና አብሮነት ያላት አገር ሆና እዚህ ደርሰናል። በአኅጉራዊው የአፍሪካ ኅብረትና ዓለምን ባሰባሰበው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) መሥራች ከመሆንም በላይ፣ ንቁ ተሳትፎ የምታደርግ ዋነኛ ባለድርሻ ናት።

በአክራሞታችን

የሰሜኑ የአገራችን ክፍል ግጭት በሰላም ስምምነት አስቆምነው ባልንበት ጊዜ፣ በአብዛኛው ምዕራብ ኢትዮጵያ ደግሞ ከአራት ዓመታት በፊት ወደ ጫካ የተለቀቀው የውንብድና ቡድን ጥቃትና ጥፋት እያደረሰ አለሁ ማለቱን ቀጥሏል። ብሔርና ማንነትን እየለየ። ቡድኑ የምዕራብ የአገሪቱን ክፍሎች ሰላምና ፀጥታ ከማደፍረስ ባለፈ ብሔርተኝነት መነሻውና መድረሻው ‘’ነፃነት’’ ሳይሆን፣ ግድያና ዘረፋ መሆኑን  ሲያሳየን ከረመ። በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የታየው አንፃራዊ ሰላም ዕፎይ ስላሰኘን ደስም አለን። ኢትዮጵያ የሚገባትም ይኸው ነውም አልን።

ማንነትን እያስከበሩ ኢትዮጵያዊነትን ለማለምለም በደቡብ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል አዲስ ክልል ለመፍጠር የተካሄደው ሕዝበ ውሳኔም የሚያስከፋ አይደለም። ሕዝቡ ለሕይወቱ የሚበጀውን ያውቅበታልና። በኢኮኖሚው ውስጥ በተለይ በግብርናው ዘርፍ ከስንዴ ተመፅዋችነት ወደ ላኪነት የሚደረገው ጥረት አኩሪ ነውም ብለን አደነቅን። የኢንዱስትሪውን ዘርፍ ለማነቃቃት ‘’ኢትዮጵያ ታምርት’’ ተብሎ ምርት ያቆሙትን ኢንዱስትሪዎች ጭምር ለማንቀሳቀስ የተያዘው ጥረትም አስመሥጋኝ ነው። ኢትዮጵያ በተለይ በኢኮኖሚው ወደ ክፍለ አኅጉራዊ፣ አኅጉራዊና ዓለም አቀፍ ለመቀላቀል የምታደርገው ጅምር ይበል የሚያሰኝና የሚመጥናት ነው። የድሬዳዋ ነፃ ንግድ ቀጣናን እያየን።

- Advertisement -

አዝማሚያዎቹ

በ1953 ዓ.ም. የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴን አገዛዝ ለመጣል የሞከረው የእነ ጄኔራል መንግሥቱ ንዋይ ሙከራ፣ በዘመናዊት ኢትዮጵያ ታሪክ የተመዘገበ የለውጥ እንቅስቃሴ ነበር። የ1966 ዓ.ም. ሕዝባዊ አመፅ የጠለፈውን ወታደራዊ አስተዳደር ደርግ አብዮት ከሽፎ መቅረት ያየችው አገር፣ ሁለተኛ የተባለውን የመንግሥት ለውጥ አስተናግዳለች። ለአሥራ ሰባት ዓመታት በሥልጣን ላይ የቆየውን ደርግ አውርዶ ሥልጣን ላይ የወጣው ለ27 ዓመታት ኢትዮጵያን የተቆጣጠረው የኢሕአዴግ አገዛዝ ኢትዮጵያን አጎሳቁሎ ወደ የሚሄድበት ሄዷል። ባለፉት አምስት ዓመታት ከኢሕአዴግ ጉያ የተወለደው የለውጥ ንቅናቄና መነቃቃት ዳግም የኢትዮጵያ ዳግም ውልደትን ያመለከተና ሕዝባዊ ድጋፍ ከአጥናፍ እስከ አጥናፍ አግኝቷል። ጉዞው ከየት ወዴት እንደሆነ ግን እየተመለከትን ነው።

ዘንድሮ

በትክክለኛው የአንድነትና የለውጥ መዘውር ገብታለች ያልናት አገር አንድነቷን ለማስጠበቅና በጋራ ለመኖር የጀመረችው ጉዞ መንገራገጭ አሳይቷል። የአብዮት ሾተላዮችን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ አምክናለች ብለን የምናስባት አገራችን፣ ዛሬም ከፈተና እንዳልወጣች ምልክቶችም ዓይተንባታል። በሁለንተናዊ መስኮች የተግባባች፣ የተባበረችና በጋራ የምትበለፅግና ሰላማዊ አገር አለችን የምንልም ዜጎች ነን ፈተናና ችግሮቿን እየተመለከትን ግራ መጋባት ውስጥ ብንገባ አይፈረድብንም። አለመታደል ነው ወይስ የለውጥ መጨንገፍ?

ጊዜ ወለድ ችግሮቻችን

ዓለም ወደ ሉላዊነት/ግሎባላይዜሽን ሲጓዝ፣ በእናቴ ቀሚስ አደናቀፈኝ ሰበብ ወደ መንደር አስተሳሰብ ወርደን እየተገኘን ችግር ውስጥ ነን። አንድ ዕርምጃ ወደፊት እንጓዝና ሁለት ዕርምጃዎች ወደኋላ መመለስ የተጠናወተን ይመስላል። ነገሮችን ሁሉ ወደ ሠፈሮቻችን እየወሰድን፣ ‹‹እኛ›› እና ‹‹እነሱ›› እያልን መፈራረጅ ባህል እያደረግነው መጥተናል። ‹‹እኛ›› እና ‹‹እነሱ›› እንልና መልካሙን፣ ስኬቱንና ድሉን የእኛ አድርገን  አሸናፊዎች እንሆናለን። በአንፃሩ መጥፎውን፣ ሽንፈትና ውጤት አልባነትን ደግሞ ለእነሱ እንሰጣለን። ኢትዮጵያን የጋራ ፕሮጀክታችን አድርገን በመገንባት ተጨባጭ ውጤት እያመጣን ባለንበት ወቅት በቅፅበት በሠፈር/መንደር አስተሳሰብ ተከልለን ሕዝብን ስናማርር እንገኛለን። መንደርተኝነታችን በአድሏዊነት፣ በሌብነትና በዘረፋም ይገለጻል።

ሰው ለይቶ አገልግሎት መስጠትና መጥቀም፣ ሰዎችን በማንነታቸው ለይቶ ማግለልና ያለ ማገልገልም ሁነኛ መገለጫዎች ናቸው። በኔትወርክና በቋንቋ የሚደረግ ትብብር መጠቃቀም ሌላው የዘመኑ በሽታ ሆኗል። እምነትን የፖለቲካ አስተሳሰብን ማራመጃ ማድረግም ሌላው መገለጫው ሆኖ በዘመናችን ተከስቷል። አንድ ታዋቂ ጋዜጠኛ ይል እንደ ነበረው፣ ‹‹በፖለቲካና በእምነት የሚነሱ ክርክሮች መቆሚያ የላቸውም››።

የኢትዮጵያዊነት ዋጋና ልክ የራስን ግፋ ቢል የቡድን ፍላጎትና ጥቅም ማሳኪያ አድርጎ መጠቀም የጊዜው ፋሽን መስሎ ብቅ ብሏል። በዚህ ሒደት የራስ ጥቅም ከተጓደለ “ኢትዮጵያ ትፍረስ” ከሚሉ ቡድኖች ጋር በሥውርና በግልጽ መጎዳኘት ጥሩ መንገድ ነው ብለው የተነሱ ወገኖች ተፈጥረዋል።

ኢትዮጵያን ብሎ በአገሩ ተማምኖና ኮርቶ የሚኖረውን ሕዝብ የአገሩ ባለቤት እንዳልሆነ አድርጎ ማሸማቀቅ፣ ኢትዮጵያዊነት የሚሰፈረውና የሚመዘነው በእንዲህ ዓይነት ኢትዮጵያዊነትን በቅጡ በማያውቁትና በማይኖሩት መሆኑ ሌላው ችግር ነው። ኢትዮጵያዊነት የዘመናት መስዋዕትነትና ጥረት ውጤት መሆኑን አውቆና ከመሥራት ይልቅ ማንነት እንደተካደ፣ ሰውነት እንዳልተከበረና እንደተጨፈለቀ አድርጎ ማላዘን ጎልቶ የሚሰማው ደግሞ ከእነዚሁ ሰዎች መሆኑ ደግሞ ዘመናችንን ድንቅ ያደርገዋል።

በተረኝነት ስሜት አገርን የግል ሀብትና ጥቅም ማግበስበሻ አድርጎ ለመኖር የሌሎችን ማንነት ክብርና ዜግነት ለመናድ መንቀሳቀስ፣ በማይነኩ የኅብረተሰቡ እሴቶች ደፍሮ በመግባት ጭምር ገብቶ አገርን ለማፍረስ መንቀሳቀስ የጊዜያችን ችግር ሆኖ ተከስቷል። በዘመናችን እየታዩ ያሉት አንዳንድ ሙከራዎች ኢትዮጵያን ወደ 1980ዎቹ አጋማሽ አልያም ወደ ዘመነ መሳፍንት ለመመለስ የሚደረጉ እንጂ፣ በ21ኛው ክፍለ ዘመን በምትኖር አገርና ዘመኑ ከደረሰበት የዕድገትና የቴክኖሎጂ ደረጃ የማይመጥኑ መሆኑን ማስተዋል ይገባል።

ዓለም፣ ዘመንና ቴክኖሎጂ በተለወጡበት የሚደረገው ነገር “ዱላው ወዲህ ቅዝምቅዝሙ ወዲያ’’ ዓይነት ነው። ኢትዮጵያዊነት ከ80 የማያንሱት ብሔረሰቦችና ከ100 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑት ዜጎች የጋራ ማንነት፣ ክብርና ሀብት መሆኑ ቀርቶ፣ የተወሰኑ ወገኖች ግፋ ቢል ለተወሰኑ ብሔረሰቦች የተሰጠ መለያና መጠቀሚያ ለማድረግ የሚያስበው ወገን ምን ዓይነት የህሊና ሰብዕና እንዳለው ራሱን ይጠይቅ ከማለት ውጪ ምን ማለት ይቻል ይሆን? ኢትዮጵያዊነት በአገሪቱ መልክዓ ምድር የሚገኙ ሁሉም ብሔረሰቦች መጠሪያና መለያ ያለ ማረጋገጥ ትልቅ እብለት ነው። ኢትዮጵያዊነት ከዚያም በላይ መሆኑን ማወቅም ይገባ ነበር። ኢትዮጵያዊነት ሲያመቸንና ደስ ሲለን መኩሪያችንና መመኪያችን፣ ሳያመቸን ደግሞ ገሸሽ አድርገን ብሔር/ብሔረሰብን መሸሸጊያ ማድረግም ያሳፍራል እንጂ አያኮራም።

ትልቋና ታላቋ ኢትዮጵያ     

ትልቋ ኢትዮጵያ በሕዝብ ብዛቷ፣ በኢኮኖሚ አቅሟ፣ በመድብለ ብዙኃን የፖለቲካ ሥርዓቷ፣ በብዝኃነትና በመቻቻል ሞዴል ሆና እንድትሆን የምትተጋ አገር ናት። ታላቋ ኢትዮጵያ ደግሞ በታሪኳ፣ በባህሏ፣ በነፃነቷና በፀረ ቅኝ አገዛዝና አፓርታይድ ትግል ባበረከተችው  አስተዋጽኦ የምትኮራ አገር ሆና ኖራለች። የረጅም ዘመናት ነፃነት ባለቤት መሆኗን ሳንዘነጋ። ትልቋና ታላቋ ኢትዮጵያ ለዜጎቿ የምትመችና መመኪያ አገር ትሆናለች እንጂ፣ የዜጎቿ መከፋፈልና አንድነት የሚያሳስባት አገር ልትሆን አይገባትም። ይልቁንም ዜጎቿ በአንድ ልብ፣ በአንድ ሐሳብ ለጋራ ልማቷና ዕድገቷ የሚተጉላት አገር ነው የምትሆነው።

የትልቋና ታላቋ ኢትዮጵያ ዜጎች ችግሮቻቸውን በሰላማዊና በሠለጠነ መንገድ ተነጋግረው ይፈታሉ እንጂ፣ ለዚህም አዋቂ ነን በሚሉ ትርክቶች፣ በታሪክና በሌሎችም መንገዶች ሊከፋፍሏቸው የሚሞክሩ ኃይሎችን ሴራ ያከሽፋሉ። ለችግሮቻቸው መፍትሔ በጋራ በማፈላለግ ይፈታሉ። በኢኮኖሚዋ የበለፀገች፣ በፖለቲካና በዴሞክራሲ ባህሏ ያደገች አገር በመሆን በዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ ተገቢና ተጠቃሽ አገር እንድትሆን ይሠራሉ። የትልቋና ታላቋ ኢትዮጵያ ዜጎች በአፍሪካና በዓለም አቀፍ መድረኮች ተገቢ ሚናዋን የምትወጣ አገር ባለቤቶች በመሆንም ማንነቷን ለማሳየት ተግተው የቀደመ ታሪካቸውን ያስመሰክራሉ እንጂ፣ በማይረባ እንቶ ፈንቶና በማንነት ስም ተደብቀው ማፈሪያ አይሆኑም። በትውልዶች ሽግግር የተገነባች አገር ባለቤት የሆኑት ኢትዮጵያውያን ዛሬም የታፈረች፣ የበለፀገችና ለዜጎቿ የምትመች፣ ለአፍሪካ የሆነች ሞዴል የሆነች ኢትዮጵያን ይገነባሉ።

የሚያዋጣው ብሎም የሚበጀው

በዛሬዋ  ኢትዮጵያ እንደ አገር ሊያስቀጥሉን የሚችሉ አማራጮች ሦስት ናቸው፡፡ አንደኛው ብሔረሰብንና አገርን አድርጎ ትንንሽ መንግሥታት ሆኖ መኖር ሲሆን፣ ሁለተኛው ኢትዮጵያዊነትን አስከብሮ በጋራ መኖር ነው። ሦስተኛውና ሁለቱንም አጣጥሞ አብሮ ለመቀጠል የሚያስችለን አማራጭ ደግሞ የብሔረሰብ ማንነት ያከበረ ኢትዮጵያዊነትን መገንባት ይሆናል። እንደ እኔ ያለፉት 30 ዓመታት የፖለቲካ መስመሮችና ከግማሽ ክፍለ ዘመን ያቀነቀነው የብሔር/ብሔረሰቦች ትግል በሦስተኛው በመንገድ እንድንቀጥል ያስገድዱናል ባይ ነኝ። ከዚህ የወጣና ማንነትን ባላስጠበቀ መንገድ የሚራመድ ኢትዮጵያዊነት በአሁኗ ፌዴራላዊና ብሔረሰባዊ፣ ክልላዊ  መንግሥታት በበዙባት አገር እምብዛም አያራምደንምና። ለሁላችንም የሚበጀው በዚህ መንገድ መጓዝ ነው ብዬ አምናለሁ።

በመከባበር፣ በመተባበርና በአንድነት የምንገነባት የዜጎቿ መኩሪያ የሆነች አገር የምትኖረንም፣ በዚህኛው አካታችነትን ባካተተው ሥርዓት ነው ብዬ አስባለሁ። የበዳይ ተበዳይ፣ የጨቋኝና ተጨቋኝ ትርክቶች የሚያከትሙት በዚህ ዓይነት የብሔረሰብ ማንነትን ባከበረና ኢትዮጵያዊነትን የጋራው ባደረገ መንገድ ነው ብዬ አምናለሁ። አለበለዚያ በትርክቶች ጭምር የተጨፈለቀና የተጎዳ የተባለው ማንነት አፈንግጦ ወደ ሌላ መስመር ወስዶን አገራዊ አንድነትን እንዳያፈርሰው ብሔረሰባዊ/ኢትዮጵያዊነትን አክብሮ መጓዝ ያስፈልጋል እላለሁ። ኢትዮጵያውያን በአንድነትና በጋራ ለመኖር፣ ለማደግና ለመመንደግ የምንችልበትን ዛሬም ለማበላሸት መሞከር ያለ መታደል ወይም ዛሬም አገራዊ ለውጡ መጨንገፍ? በፍጥነት ምላሽ ሊያገኝና መስተካከል የሚገባው አገራዊ የህልውና ጥያቄ ነው።

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡  

- Advertisement -

በማህበራዊ ሚዲያዎች ይከታተሉን

ከ ተመሳሳይ አምዶች

አሸናፊና ተሸናፊ የሌለበት ትንቅንቅ ማብቂያው መቼ ይሆን?

በናኦድ አባተ በአውሮፓውያን ዘንድ በስፋት የሚታወቀው “A House Divided Against Itself Cannot Stand.” (እርስ በርሱ የተከፋፈለ ቤት አይቆምም) አባባል ትልቅ መልዕክት አለው፡፡ ኢትዮጵያውያንም በታሪክ አጋጣሚ...

የሐረሪን ክልል በኦሮሚያ የመጠቅለል ዕሳቤ ፌዴራላዊ ሥርዓትን ማፍረስ ወይስ መገንባት?

በኑረዲን አብደላ በቅርቡ ለአገራዊ የምክክር ኮሚሽን የቀረበው የሐረሪን ክልል በኦሮሚያ የመጠቅለል አጀንዳ የነባር ሕዝቦችንና የብሔር ብሔረሰቦች የራስን ዕድል በራስ የማስተዳደር ሕገ መንግሥታዊ መብትን የሚፃረር፣ በምሥራቅ...

ለሰከነ የፖለቲካ ባህል ግንባታና መደማመጥ ለተላበሰ ድርድር ትኩረት ይሰጥ

በሳምሶን ተክለአብ ኢትዮጵያ የሁላችንም የጋራ ቤት ነች፡፡ ‹‹ጥያቄዬ ተመለሰልኝ››፣ ‹‹ጥያቄ አለኝ››፣ ወይም ‹‹እንዳደረጉ ያድርጓት›› ብሎ አንገቱን እንደ ሰጎን የቀበረውም ሁለተኛ ቤት እንደሌለው የታወቀ ነው፡፡ የአገሩን...

የብሔራዊ መሬት ፖሊሲ ይዘጋጅ ጥያቄና የውጭ ኃይል ፍላጎት

(ክፍል ሁለት) በደምስ ጫንያለው (ዶ/ር) በመሬት ፖስፕኢና የልማት እንቅስቃሴ ውስጥ የውጮቹ ጨዋታ ከ1940ዎቹ ወዲህ ከአፄ ኃይለ ሥላሴ ንግሥና፣ በተለይም በ1920ዎቹ መጨረሻ ከተቃጣብንና ከከሸፈው የኢጣሊያን ወረራ በኋላ፣ የውጭ...

ብሔራዊ የመሬት ፖሊሲ ይዘጋጅ ጥያቄና የውጭ ኃይል ፍላጎት

(ክፍል አንድ) በደምስ ጫንያለው (ዶ/ር) መንደርደሪያ ለኢትዮጵያ፣ ለበርካታ ዘመናት፣ የመሬት ባለቤትነት፣ ይዞታ፣ ውርስ፣ አጠቃቀም የመብትና ተዛማጅ ጉዳዮች ለአገር ደኅንነት ሆነ ለሉዓላዊነቷ ተከብሮ መቆየት የነበራቸው አስተዋፅኦ በቀላሉ የሚገለጽ...

ከምክክርና ከድርድር ውጪ ምን ዓይነት አማራጭ ይኑረን?

በዘውዳለም መንገሻ የዘመናዊት ኢትዮጵያ ፖለቲካ ውዝግብ በትንሹ የአንድ ምዕተ ዓመት ዕድሜ ያስቆጠረ ነው፡፡ በእነዚህ ወቅቶች በጨቋኝና ተጨቋኝ ትርክት፣ በአሸናፊና በተሸናፊ ፍልሚያ ውስጥ የኖሩ የአገሪቱ ሕዝብ...

አዳዲስ ጽሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ ቀኑን ሙሉ ከዋሉበት የሥራ አስፈጻሚ ስብሰባ ወደ መኖሪያ ቤታቸው ተመልሰው ከባለቤታቸው ጋር እያወጉ ነው]

የምን ስብሰባ ላይ ዋልኩ ነበር ያልከኝ? የሥራ አስፈጻሚ። የምን ሥራ አስፈጻሚ? የገዥው ሥራ አስፈጻሚ። ምን ገጥሟችሁ ነው የተሰበሰባችሁት? ለመረጠን ሕዝብ ቃል የገባናቸውን ተግባራት አፈጻጸም የምንገመግምበት የተለመደ ስብሰባ ነው። የገባችሁት ቃል...

ሕወሓትን አጣብቂኝ ውስጥ የከተተው መመርያ

በሁለት አንጃ ተከፍሎ የእርስ በርስ የቃላት ጦርነት ውስጥ የገባው ሕዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) ልዩነቱን ትቶ ወደቀድሞው አንድነቱ በመመለስ የሚጠበቅበትን ጠቅላላ ጉባዔ የማድረግ አልያም...

ባንኮች እየፈጸሙት ያለው አቅርቦትንና ፍላጎትን ያላገናዘበ የውጭ ምንዛሪ ግዥ

የውጭ ምንዛሪ ግብይት በገበያ ዋጋ እንዲገበይ የወጣው ሕግ ተግባራዊ መሆን ከጀመረ ከሰባት ወራት በላይ አስቆጥሯል፡፡ ሕጉ ተግባራዊ በተደረገበት የመጀመርያው ቀን የአንድ ዶላር የምንዛሪ ዋጋ...

አሳረኛው ኑሮ!

የዛሬው ጉዞ ከቦሌ ወደ ፒያሳ ይሆን ዘንድ ግድ ሆኗል፡፡ ለምን? በኑሮ  ምክንያት፡፡ የታክሲ መሠለፊያው ወሬ የነዳጅ ጭማሪውን ተከትሎ ስለሚመጣው ተጨማሪ ታሪፍ ነው፡፡ ‹‹የእኛ ኑሮ...

የግለሰቦች ለመብታቸው ኃላፊነት አለመውሰድ ለአገር ያለው አደጋ

በያሬድ ኃይለመስቀል አንድ የማከብረው ኢኮኖሚስት አንድ መጽሐፍ እንዳነብ መራኝና ማንበብ ጀመርኩኝ። ይህንን መጽሐፍ ሳነበው ከዋናው ሐሳብ ወጣ ብሎ ስለ “የነፃ ተጓዦች ሀተታ” (The Free Rider...

‹‹የብድርና ቁጠባ ኅብረት ሥራ ማኅበራትን ኢኮኖሚያዊ አስተዋጽኦ ማጠናከር ያስፈልጋል›› አቶ ፍፁም አብርሃ፣ የአሚጎስ ብድርና ቁጠባ ኅብረት ሥራ ማኅበር መሥራችና ሥራ አስኪያጅ

አሚጎስ የብድርና ቁጠባ ኅብረት ሥራ ማኅበር ከተመሠረተ አሥራ ሁለት ዓመታት ሆኖታል፡፡ በእነዚህ ዓመታት 8,500 አባላትን ማፍራት ችሏል፡፡ አሚጎስ ስለተመሠረተበት ዓላማ፣ እያከናወናቸው ስለሚገኙ ተግባራት፣ የብድርና...
[the_ad id="124766"]

በማህበራዊ ሚዲያዎች ይከታተሉን