“ደሞዝ የምትወጣ በልደታ
የምታልቀው ጀንበር ስ’ጠልቅ ወደ ማታ” አሉ።
ደመወዙ እጁ የገባች ደመወዝተኛ መሠረታዊ ነገሮችን ሸማምቶ እንጥፍጣፊ እንኳ ሳይተርፈው የሚቀጥለውን የደመወዝ መክፈያ ቀን ማስላት ይጀምራል። ‹‹ደመወዝ ሃያ ዘጠኝ ቀን ቀረው›› የሚለው ደመወዝተኛ ቁጥሩ የትየለሌ ነው።
የሸቀጦች ዋጋ ከዕለት ዕለት እየናረ መሄድ ኗሪውን ግራ ከማጋባት ዘሎ በሐሳብ ካሰበው ወደ አላሰበው መንገድ መሄድ ብቻም ሳይሆን አጠገቡ የሚያደምጠው ያለ ይመስል እጁን እያወናጨፈ ለብቻው እያወራ የሚሄደውም በዝቷል።
የአገራችን የንግድ ሥርዓት መልክ የሌለውና ካሻቀበ የማይመለስ መሆኑ ነገን አስፈርቶታል። እኛ አገር የወጣ የሚወርደው ባለሥልጣን ብቻ ነው ብለው ማሾመራቸው ቅጂው ኑሮ ነው። የምግብ ዘይት ተምዘግዝጋ የነዳጅ ዘይትን ማስከንዳቷን ለአብነት ማንሳቱ ይበቃል።
በየ ዘመናቱ ኑሮ መልኩን ሲያጠቁርና ችግር ሲበረታ ኗሪው ዘመኑን መልክ ሰጥቶ የሚያልፍባቸው ጥበቦች ብዙ ናቸው። በ1977 በአገራችን ተከስቶ በነበረው ድርቅ እንዲህ እንደ ዛሬው የጤፍ ዋጋ ሰማይ ሲነካና ችግር ጉልበቱ ሲፈረጥምበት በዚያን ወቅት ለጆሮ ደርሶ የነበረውን የኤፍሬም ታምሩን ልመደው ሆዴን ዜማውን ተውሰው ግጥሙን የያኔውን መልክ አሲዘው ለኑሮ አጎራጉረውለት ነበር አሉ።
ልመደው ልመደው ሆዴ
ተወዷል ጤፍና ስንዴ
እሩዝን ብላው በዘዴ።
ያኔ እሩዝ ከአብዛኛው ማኅበረሰብ ጋር የተዋወቀበት ዘመንም ነበር አሉ። አንዳዴም እጥረት ሳይኖር ምርቱን በመሸሸግና እጥረት እንዲፈጠር በማድረግ በሰው ስቃይ ትርፍ የሚያሰላውም ነጋዴ ቁጥሩ ቀላል አይደለም። ዋጋዎች የሚጠለዙበት የጊዜ ገደብ በቀናት ሳይሆን በደቂቃዎች ልዩነት እየሆነ ነው። አንድ ወዳጄ የገጠመውን እንዲህ አወጋኝ። የፀሐይዋን ንዳድ ያበረደልን የሰሞኑ ዝናብ ለቆርቆሮ ነጋዴዎች ገበያው ፌሽታ ደርቶለታል አሉ።
አንድ በዕድሜ ገፋ ያሉ አዛውንት ጥቂት የቤት ክዳን ቆርቆሮዋችን ለመቀየር ይበቃል ብለው የገመቱትን የቆርቆሮ ሚስማር ኪሎውን በቆርቆሮ መግዣ ብር ገዝተው ለፈጣሪያቸው በምሬት ማመልከቻቸውን እያደረሱ ይዘው ይሄዳሉ። ጥቂት ቆይተው የገዙበት ቤት ተመልሰው መጡ። የወሰዷት ሚስማር ስላልበቃቻቸው እንዲጨምርላቸው ነጋዴውን ጠየቁት። ነጋዴውም መለሰ ‹‹አባቴ ቅድም በሸጥኩልዎት ዋጋ አልሸጥልዎትም። አሁን ጨምሯል አላቸው። ሽማግሌውም ‹‹ምነው ልጄ አናፂው ከቆርቆሮ ላይ ሳይወረድ፣ መሬት ሳይነካ›› አሉ አሉ። በምሬት። ገበያው እንዲህ ነው በብርሃን ፍጥነት እየተምዘገዘገ መያዣ መጨበጫው የጠፋው። ሀይ ባይ ያጣው።
አሁን በተያያዝነው የኑሮ አቀበት ኗሪው አሁናዊ የኑሮውን መልክ መልክ እየሰጠ ውሎ ያነጋል። ነጭ ጤፍ በፍላሽ እንጭናለን ከሚለው ጀምሮ ኑሮን በተለያየ መንገድ በዘመን ሰሌዳ ላይ አስቀምጠው እያለፉ ነው።
በቆምንበት አሁናዊ መልካችን የተወነጨፈች ነች። ሽማግሌዎች ለትዳር ልጅዎን ለልጃችን ለማለት ሽምግልና ሄዱ አሉ። ተቀባይ ሽማግሌዎች ለመሆኑ ምን አለው ብለው ጠየቁ። መላሾች፣
‹‹ነጭ ጤፍ !!!!!!!!!!!!!››
(ዳንኤል ነገዎ)