በዳንኤል ንጉሴ
የፌዴራል መሬት ባንክና ልማት ኮርፖሬሽን ካለፈው ዓመት አንስቶ ሲያወዳድራቸው የቆዩ የመንግሥት ይዞታዎችን ለማልማት የተመረጡ ዲዛይኖችን ለዕይታ ቀረቡ፡፡
ኮርፖሬሽኑ በፌዴራል መንግሥት ሥር ያሉ ተቋማትን የማልማትና የማስተዳደር ሥልጣን የተሰጠው መሆኑ ይታወሳል፡፡ በአጠቃላይ በአገር ደረጃ 4.7 ሚሊዮን ሔክታር መሬቶችን የለየና የሰበሰበው ኮርፖሬሽኑ፣ ለጊዜው ዋነኛ ሥራው አድርጎ የተነሳው በአዲስ አበባ ባሉ ያልለሙ መሬቶችን ማልማት ሲሆን፣ ለዚህም በከተማዋ 3,700 ሔክታር መሬቶችን በመለየት እንዳዘጋጀ አስታውቆ እንደነበር አይዘነጋም፡፡
ኮርፖሬሽኑ የተለያዩ ዲዛይነሮችን በማወዳደር አንድ ከአገር ውስጥ፣ እንዲሁም አንድ ከውጭ አገር በመምረጥ ወደ ሥራ እንዲገቡ አቅጣጫ ሰጥቶ ነበር፡፡ ድርጅቶቹም ቢንያም ዓሊ አርክቴክትስና አርባኒስት የተባለ የአገር ውስጥ፣ እንዲሁም ዘ ድሪም ፋክትሪ የተባለ የውጭ አገር ድርጅት መርጦ እንደ ነበር ይታወሳል፡፡
በዚህም መሠረት ሐሙስ መጋቢት 14 ቀን 2015 ዓ.ም. በስካይላይት ሆቴል ባደረገው ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ዲዛይኖቹን ለዕይታ አቅርቧል፡፡ በሥነ ሥርዓቱ ላይ የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሮ ሌንሳ መኮንን ጨምሮ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡
በዝግጅቱም የተለያዩ ገለጻዎች የተደረጉ ሲሆን፣ የቢንያም ዓሊ አርክቴክትና አርባኒስት ባለቤትና ዋና ሥራ አስኪያጅ ቢንያም ዓሊ (ኢንጂነር) ስለዲዛይኖቹ ገለጻ አድርገዋል፡፡ በገለጻቸውም ዲዛይኖቹ ሥራ ላይ የሚውሉባቸው ቦታዎች፣ ሥራዎቹ ሲጠናቀቁ ስለሚሰጧቸው ጥቅሞች አብራርተዋል፡፡
የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሮ ሌንሳ ዲዛይኖቹ በታቀደላቸው ጊዜ ወደ ሥራ እንዲገቡ በማሳሰብ፣ ለድርጅቶቹ የማበረታቻ ሽልማት ሰጥተዋል፡፡
በዚህም መሠረት ለቢንያም ዓሊ አርክቴክትና አርባኒስት ባለቤትና ዋና ሥራ አስኪያጅ ቢንያም (ኢንጂነር) 340‚000 ሺሕ ብር ሽልማት ሲበረከትላቸው፣ ለ ዘ ድሪም ፋክትሪ ደግሞ 360‚000 ሺሕ ብር ሽልማት በመስጠት ዝግጅቱ ተጠናቋል፡፡