አፄ ልብነ ድንግል በ16ኛው ምዕት ዓመት የኢትዮጵያን ንጉሠ ነገሥት ነበሩ፡፡ በ1520ዎቹ አጋማሽ ለፖርቱጋል ንጉሥ አማኑኤል ከጻፉላቸው ደብዳቤ ውስጥ የሚከተለው ይገኝበታል፡፡ የታሪክ ጸሐፊው አቶ ተክለ ጻድቅ መኩርያ፣ ከአፄ ልብነ ድንግል እስከ አፄ ቴዎድሮስ በተሰኘው መጽሐፋቸው እንዲህ ጽፈውታል፡፡ ደብዳቤው የኢትዮጵያን መልክአ ምድር ዘርዘር አድርጎ አመልክቶታል፡፡
‹‹ስሜ ዕጣነ ድንግል፣ በኢትዮጵያ ቋንቋ ድንግል ያበራችለት፣ ይኸው ስም የተሰጠኝ ቅድስት ጥምቀትን በተቀበልሁበት ቀን ነው፡፡ በነገሥሁ ጊዜ ዳዊት ተባልሁ፡፡ ዳዊት ፍቁረ እግዚእ ዘእምነገድ ይሁዳ፣ የዳዊት ልጅ የሰሎሞን ልጅ፣ … የዘርዓ ያዕቆብ ልጅ በሥጋ የናሁ (ናዖድ) ልጅ፡፡ የላይኛውና የታችኛው ኢትዮጵያ የትልልቆቹም የነጋሢ ግዛቶች የክሶአ ንጉሥ የካፋታ (ከፋ)፣ የፈጠጋር፣ የአንጎት፣ የባሩ፣ የበአሊንግዝ፣ የአድአ የሻንግ (ወንጅ)፣ ዓባይ የሚፈልቅበት የጐዣም የአማራ የባጋሚድሪ (ቤጌምድር)፣ የአምቢያ (ደምቢያ)፣ የዋኝ የትግሬ መሆም (ትግሬ መኰንን ወይም ትግሬ መሆኔ)፣ ንግሥተ ሳባ የወጣችበት የሳበይም (ሳባ)፣ የባርናጋስ፣ ንጉሠ ነገሥት በመጨረሻ እስከ ኑብያ ያለው ግዛት ጌታ እርሱም ከግብጽ የሚዋሰን . . .
ደጉ ንጉሥ አማኑኤል ሆይ ሰላም ላንተ ይሁን፡፡
አሁንም ሰላም ላንተ ይሁን፤ ለንግሥቲቱም ለውዲቱ ጓደኛህ ክርስቶስ ጸጋውን የሰጣት የድንግል ማርያም አገልጋይ ለወንዶች ልጆችህም ሁሉ ሰላም ይሁን፤ ከነርሱም ጋር መዓዛው በሚጣፍጥ የጽጌረዳ አበባ በሞላበት አትክልት እንደተቀመጥህ ሁሉ፣ ደስታህን የምታይ፣ ለሴቶች ልጆችህም ሰላም ይሁን፤ ሥጋጃው በተነጠፈበት የመሳፍንቶችና ያለቆች አዳራሽ በጥሩ ልብስ አጊጠው ለሚታዩት … ለዳኞችህና ለአማካሪዎችህ ለጦር አለቆችህም ሰላም ይሁን፡፡››
– ሔኖክ መደብር