ካሮላይን ራየን (ዶ/ር)፣ የአሜሪካ የበሽታዎች መቆጣጠሪያና መከላከያ ማዕከል የኢትዮጵያ ዳይሬክተርና ሾን ጆንስ፣ የዩኤስኤ አይዲ ኢትዮጵያ ዳይሬክተር፣
የቲቢ በሽታ በቀላሉ ልንከላከለውና ልናድነው የምንችለው ቢሆንም፣ በኢትዮጵያ በእያንዳንዷ ሰዓት የሁለት ሰዎችን ሕይወት ይቀጥፋል።
የቲቢ በሽታ አምጪ የሆነው ባክቴሪያም በዓለማችንም ሆነ በኢትዮጵያ ከፍተኛ ጉዳት አድራሽ ተህዋስ ሲሆን፣ በየዓመቱ በወባና በኤችአይቪ ከሚሞቱት ሰዎች በላይ ይገድላል።
መጋቢት 15 ቀን 2015 ዓ.ም. የሚከበረውን የዓለም የቲቢ ቀን አስመልክቶ፣ በአዲስ አበባ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ በላከው መግለጫ፣ ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. በ2030 የቲቢ በሽታን በመላ አገሪቱ ለማጥፋት ያስቀመጠችውን ግብ እንድታሳካ በዩኤስኤ አይዲና በሲዲሲ አማካይነት ድጋፉን እንደሚቀጥል አስታውቋል፡፡
ለዓመታት ተዘንግቶ የቆየውን የቲቢ በሽታና መድኃኒት የተላመደ የቲቢ ዝርያን ለመከላከል የሳይንሱ ማኅበረሰብ የተለያዩ መሣሪያዎችን፣ መድኃኒቶችንና ዘዴዎችን አበርክቷል።
በአሁኑ ወቅትም የቲቢን በሽታ ለማከም ፈጣንና ትክክለኛ ውጤትን የሚያሳዩ መሣሪያዎች፣ ፈዋሽና ውጤታማነታቸው የተረጋገጠ መድኃኒቶች እንዲሁም በመላ አገሪቱ የቲቢ በሽታን ለመለየት፣ ለመመርመርና ለማከም የሚያግዙ በርካታ አዳዲስ ግኝቶች መኖራቸውን መግለጫው ጠቁሟል፡፡
ዳይሬክተሮቹ እንዳሉት፣ በእነዚህ የፈጠራ ውጤቶች በመታገዝ በኢትዮጵያ እ.ኤ.አ 2022 በቲቢ ምክንያት የተከሰተውን 19 ሺሕ ሞት ማስቀረትና የቲቢ በሽታን በመከላከል ረገድ ዋነኛው ተግዳሮት የሆነውን በሽታው ሥር ሳይሰድ አስቀድሞ ማወቅ ወሳኝ ነው።
የቲቢ በሽታ አምጪ ባክቴሪያ በቀላሉ ሊታይና ሊለይ በማይችል የሰውነት ክፍል ውስጥ ለወራት አንዳንዴም ለዓመታት ራሱን ደብቆ መቆየት የሚችል በመሆኑ፣ አሁን ባለው የጤና ሥርዓት 30 በመቶ የሚሆነውን የቲቢ በሽታ አስቀድሞ ለማወቅ እንደሚያስቸግርና ይህም ችግሩ ደጋግሞ እንዲከሰት ማድረጉንም አክሏል፡፡
ዓምና ብቻ 145 ሺሕ የሚጠጉ ኢትዮጵያውያን በቲቢ በሽታ መያዛቸውን ያስታወሰው መግለጫው፣ የአሜሪካ መንግሥት ክፍለ ዘመናትን ያስቆጠረውን በሽታ መከላከል ድጋፍ ማድረግ ከጀመረ ወዲህ፣ ከጤና ሚኒስቴር ጋር በጋራ በመሆን የቲቢ በሽታን ለመከላከል በተቀየሰው ዘዴ የ2.3 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን ሕይወት ለመታደግ መቻሉን ጠቁሟል። በዚህም ባለፉት 20 ዓመታት የቲቢ በሽታ በኢትዮጵያ 70 በመቶ መቀነስ መቻሉንና ሥራውን አጠናክሮ መሄድ እንደሚያስፈልግም ገልጿል።
የአሜሪካ ሕዝብ ቲቢን በኢትዮጵያ ለመከላከል ዳግም ቁርጠኝነቱን የሚያረጋግጠው፣ በሽታውን ለማግኘት ድጋፋን በማጠናከርና እ.ኤ.አ. በ2030 በመላ ኢትዮጵያ በበሽታው የሚያዙ ሰዎችን ቁጥር በ35 ከመቶ ለመቀነስ፣ ፍቱን መድኃኒቶችንና ሕክምናዎችን በማቅረብ በበሽታው ከሚሞተው ሕዝብ የ50 በመቶውን ሕይወት ማትረፍና በ2030 በመላ አገሪቱ 90 በመቶ የቲቢ በሽታን ሙሉ በሙሉ መለየት፣ ማከምና ማዳን የሚሉትን ሦስት መሠረታዊ ግቦች አስቀምጦ በመንቀሳቀስ መሆኑንም ራየን (ዶ/ር) እና ሚስተር ጆንስ ተናግረዋል፡፡
እነዚህን ግቦች ለማሳካትና ያለ ምንም የውጭ ዕርዳታ በሽታውን ለመከላከል የሚያስችል አገር አቀፍ የቲቢ መርሐ ግብር ለመዘርጋት ቆርጦ በመነሳት፣ ከለጋሽ ድርጅቶችና የረዥም ጊዜ አጋር ከሆነው ጤና ሚኒስቴር ጋር በጋራ በመተባበርና በመቀናጀት በኢትዮጵያ የቲቢ በሽታን ማስወገድ እንደሚቻል እምነታቸው መሆኑንም የሁለቱ ተቋማት ዳይሬክተሮች ገልጸዋል።