_ቀሪዎቹ ሦስት ህገወጥ ተሿሚዎች የመጨረሻ እድል ተሰጥቷቸዋል
ጥር 14 ቀን 2015 ዓም በህገወጥ መንገድ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የምትመራበትን ቀኖና በመጣስ እነ አቡነ ሳዊሮስ(ሦስት ጳጳሳት) 26 ኤጲስ ቆጶሳት በመሾማቸው ምክንያት ጥር 18 ቀን 2015 ዓም አስተላልፎት የነበረውን ውግዘት ከአምስቱ ኤጲስ ቆጶሳት በስተቀር ማንሳቱን አስታወቀ።
ዛሬ መጋቢት 21 ቀን 2015 ዓም ጀምሮ ውግዘቱ መነሳቱን ያስታወቀው ቅዱስ ሲኖዶስ እንደገለጸው፣ ቀኖና ሕገ ቤተ ክርስቲያንን መሠረት አድርጎ ከቀረበው ምክረ ሐሳብና በቤተ ክርስቲያኒቱና በምዕመናን ላይ ከደረሰው ሞት፣ የአካልና የሞራል ጉዳት፣ እስራትና እንግልት አንጻር ውግዘቱ ሊነሣ የማይገባውና በሕግም የሚያስጠይቅ ሕገወጥ አድራጎት ቢሆንም አሁን በተከሰተው ድርጊት በአጭር ጊዜ ውስጥ በእናት ቤተ ክርስቲያን ላይ እና በተከታዮቿ ምዕመናንና አገልጋዮቿ ላይ ከደረሰው ከፍተኛ ጉዳት አንጻር ችግሩን በሆደ ሰፊነትና በይቅርባይነት መፍታት ካልተቻለ አሁን ያለው መከራና ችግር ይቀጥል ቢባል በቀጣይ በቤተ ክርስቲያኒቱ አንድነትና ሐዋርያዊ ተልዕኮ እንዲሁም በምዕመናንና አገልጋዮቿ ሰላማዊ ጉሮ ላይ የሚያደርሰውን ከፍተኛ የሆነ አደጋ ከግምት ውስጥ በማስገባት እና ካሁን ቀደም ክቡር የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ በተገኙበትና በመቀጠልም ክቡር አቶ ሽመልስ አብዲሳ የኦሮምያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ፕሬዝዳንት በተገኙበት በተደረገው ውይይት በተደረሰው 10ሩ የስምምነት ነጥቦች መሠረት ቅዱስ ሲኖዶስ በስፋት ከተወያየ በኋላ የሚከተሉትን ውሳኔዎች አሳልፏል፡፡
የካቲት 8 ቀን 2015 ዓ.ም. በክቡር የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚ/ር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ መሪነት ወደ ጽርሐ መንበረ ፓትርያርክ በመምጣት እስካሁን ድረስ በበዓታቸው ጸንተው የቆዩት 3ቱም የቀድሞ ሊቃነ ጳጳሳት ማለትም ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ፣ ብፁዕ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ እና ብፁዕ አቡነ ዜናማርቆስ ላይ አስቀድሞ ጥር 18 ቀን 2015 ዓ.ም. በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተላለፈው ውግዘት ከዛሬ መጋቢት 21 ቀን 2015ዓ.ም. ጀምሮ ተነስቷል፡፡
ውግዘቱ የተነሣላቸው 3ቱም ሊቃነ ጳጳሳት ከዛሬ መጋቢት 21 ቀነ 2015ዓ.ም. ጀምሮ በቀድሞ የሊቀ ጳጳስነት ማዕረጋቸውና ስማቸው ማለትም ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ሊቀጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ሊቀጳጳስ እና ብፁዕ አቡነ ዜናማርቆስ ሊቀጳጳስ ተብለው እንዲጠሩና አስቀድሞ ተመድበው ይሰሩበት በነበረው የሥራ ኃላፊነታቸው ሥራቸውን እንዲቀጥሉ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተገኙበት በተደረገው ውይይት በተደረሰው ስምምነት መሠረት ጥሪውን ተቀብለው ለስምምነቱ ተገዥ በመሆን በጽሑፍ ጥያቄያቸውን ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ያቀረቡት 20ዎቹ የቀድሞ መነኮሳት ጥር 18 ቀን 2015 ዓ.ም. በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ውሳኔ የተላለፈው ውግዘት ከዛሬ መጋቢት 21 ቀን 2015 ዓ.ም. ጀምሮ ተነስቷል፡፡ ቀሪዎቹ 5ቱ ባለው ጊዜ ተጠቅመው ወደቤተ ክርስቲያናቸው እንዲመለሱ ቅዱስ ሲኖዶስ በድጋሚ እያሳሰበ ውግዘቱን በሚመለከት በቋሚ ሲኖዶስ በኩል ታይቶ እንዲፈጸም ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
ውግዘቱ የተነሣላቸው 20ዎቹም የቀድሞ መነኮሳት አስቀድሞ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት ከዲቁና እስከ ቁምስና ባለው ማዕረገ ክህነታቸው እንዲያገለግሉ እና በምንኩስና ስማቸውም እንዲጠሩ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
20ዎቹ የቀድሞ መነኮሳት የሥራ ምደባን በተመለከተ በተደረሰው ስምምነት መሠረት በቀድሞው የሥራ መደብ ደረጃቸው እንዲመደቡ ቅዱስ ሲኖዶስ በመወሰን ዝርዝር ጉዳዩ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በኩል እንዲፈጸም ቅዱስ ሲኖዶስ አዟል፡
በተከሰተው ሕገወጥ ድርጊት መነሻነት ለቤተ ክርስቲያናችን ክብርና ልዕልና ሲሉ ለሞት፣ ለአካልና የሞራል ጉዳት፣ ለእስራትና እንግልት እንዲሁም ለስደት የተዳረጉትን ምዕመናን፣ ወጣቶች፣ አገልጋይ ካህትና ከሀገረ ስብከት እስከ አጥቢያ ያሉ የሥራ ኃላፊዎችን ጉዳትና መከራ እንዲሁም ችግሩን በሕግ አግባብ እንዲፈታና የቤተ ክርስቲያኒቱ መብትና ጥቅም እንዲከበር ሌሊት ከቀን በማገልገል ላይ የሚገኙትን የሕግ ባለሙያዎች ማህበር የሰጡትን ሙያዊ አገልግሎት ቅዱስ ሲኖዶስ ዘወትር በከባድ ሐዘንና ጸሎት ሲያስታውሰው የሚኖርና በቀጣይ በቤተ ክርስቲያኒቱ የታሪክ መዛግብት ተመዘግቦ ለቀጣዩ ትውልድ መማሪያነት እንዲውል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
ውግዘቱ የተነሣላችሁ የቤተ ክርስቲያኒቱ አገልጋይ አባቶችም በቀጣይ በፈጸማችሁት ድርጊት የተጎዳውን መላው ሕዝበ ክርስቲያን እና ክብሯ የተደፈረውን እናት ቤተ ክርስቲያናችሁን ሊክስ በሚችል የትሕትና መንፈስ በማገልገልና ዳግመኛ ከእንዲህ ዓይነቱ ሕገወጥ አድራጎት በመራቅ የተጣለባችሁን ከፍተኛ ኃላፊነት በታማኝነት እንድትወጡ ቅዱስ ሲኖዶስ በጥብቅ ያሳስባል፡፡
በቤተ ክርስቲያናችን ላይ የደረሰውን ፈተና እንዲወገድና የቤተ ክርስቲያኒቱ መብትና ክብር እንዲጠበቅ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወክላችሁ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመሩት የውይይት መድረክ ላይ በመሳተፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከታችሁ ሦስቱ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ብፁዕ አቡነ ናትናኤል፣ ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ እና ብፁዕ አቡነ ሩፋኤል እና አቀራራቢ የሀገር ሽማግሌዎች እንዲሁም በፍትሕ አደባባይ ክስ በመመስረት የደከማችሁ የሕግ ባለሙያዎች ማህበር እና ችግሩን ለመላው ዓለም በማዳረስ ሰፊ ሥራ የሠራችሁ የሚዲያ ተቋማትን ቅዱስ ሲኖዶስ ለሰጣችሁት ታሪክ የማይረሳው አገልግሎት በእጅጉ ያመሰግናል፡፡
ምንም እንኳን አስቀድሞ ከክቡር የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስቴር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ እና ክቡር አቶ ሽመልስ አብዲሳ የኦሮምያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ፕሬዝዳንት ጋር በተደረገው ውይይትና ስምምነት መሠረት የታሰሩት ግለሰቦች በሙሉ እንደሚፈቱ ቃል የተገባ ቢሆንም እስካሁን ድረስ በርካታ ሰዎች በእስር ላይ የሚገኙ ስለሆነ መንግስት አስቀድሞ በገባው ቃል መሠረት ሁሉንም እስረኞች እንዲፈታልን ቅዱስ ሲኖዶስ በጥብቅ ያሳስባል፡፡
በተከሰተው ችግር ከሀገረ ስብከት እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ባሉት የቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር ላይ በኃላፊነት ተመድበው ሲሰሩ ቆይተው በችግሩ ምክንያት ተፈናቅለው የቆዩት ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የሀገረ ስብከትና የወረዳ ቤተ ክህነት ሠራተኞች ያለምንም የፀጥታ ስጋት በምድብ ሥራቸው ላይ እንዲቀጥሉ ከፌዴራል ጀምሮ በየደረጃው ያሉ የመንግስት አካላት ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ቅዱስ ሲኖዶስ ማሳሰቢያ ሰጥቷል፡፡