ኢትዮጵያ ውስጥ ዜጎችን በእጅጉ የሚያሳስቡ በርካታ ችግሮች አሉ፡፡ ከችግሮቹ መካከል ዋነኛ የሚባሉት በኢኮኖሚው፣ በፖለቲካውና በማኅበራዊው ዘርፍ በስፋት የሚስተዋሉ ተግዳሮቶች ይጠቀሳሉ፡፡ ኢኮኖሚው ለ120 ሚሊዮን ሕዝብ የሚሆን በቂ ምግብ፣ መጠለያ፣ አልባሳትና የመሳሰሉትን ማቅረብ ተስኖታል፡፡ በከፍተኛ የዕዳ ጫና ውስጥ ያለው ኢኮኖሚ የኢንዱስትሪና የግብርና ምርቶችን በሚፈለገው መጠን ማቅረብ አቅቶታል፡፡ ከኤክስፖርት የሚገኘው የውጭ ምንዛሪ በጣም ዝቅተኛ ሲሆን፣ በአንፃሩ ነዳጅን ጨምሮ ከውጭ የሚገቡ ምርቶች የአገሪቱን መጠባበቂያ አድቅቀውታል፡፡ የንግድ ሚዛኑ ከበፊት ጀምሮም ቢሆን የተዛባ መሆኑ ቢታወቅም፣ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በአገር ውስጥ ለመተካት የሚደረገው ጥረት ፍሬ ማፍራት አልቻለም፡፡ የአገሪቱ የመገበያያ ገንዘብ አቅም በጣም ከመኮስመኑ የተነሳ፣ በይፋዊውና በጥቁር ገበያው መካከል ያለው ሰፊ ልዩነት የችግሩን መጠን ያስገነዝባል፡፡ የሁሉም የምግብ ምርቶችና የፍጆታ ዕቃዎች ዋጋ በየቀኑ እየጨመረ የሚሊዮኖች ሕይወት እየተመሰቃቀለ ነው፡፡ የኑሮ ውድነቱ ብዙዎችን ከመካከለኛ ኑሮ ወደ ዝቅተኛ፣ ከዝቅተኛ ደግሞ ወደ ለየለት የድህነት አዘቅት ውስጥ እየከተታቸው ነው፡፡ የኢኮኖሚው ችግር መላ ካልተፈለገለት መጪው ጊዜ ያሳስባል፡፡
በአሁኑ ጊዜ በጣም እያስፈሩ ካሉ የኢኮኖሚው ተግዳሮቶች መካከል በስፋት እየተጠቀሰ ያለው፣ መንግሥት ከዓለም ባንክና ከአይኤምኤፍ ጋር እያካሄደ ባለው ንግግር ላይ ተመሥርቶ የሚወስዳቸው ዕርምጃዎች ጉዳይ ነው፡፡ ሁለቱ ኃያላን የዓለም የፋይናንስ ተቋማት የሚሰጧቸው ምክረ ሐሳቦችና እጅ ጥምዘዛዎቻቸው፣ ኢኮኖሚው ለገጠመው ሕመም የማይበጅ መድኃኒት አስገድደው እንደማስዋጥ የሚቆጠሩ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያም እንዲህ ዓይነቱን የግዳጅ ታብሌት ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ ውጣ ያተረፈችው ዕዳና ቀውስ ብቻ ነው፡፡ የመዋቅር ማስተካከያ ፕሮግራም በሚባለው የዓለም ባንክ አስገዳጅ ትዕዛዝ በርካታ ችግሮች አጋጥመው ነበር፡፡ ከዚያ በኋላም በአይኤምኤፍ ጫና በተደጋጋሚ የብር የምንዛሪ አቅም እንዲቀንስ በመደረጉ፣ ዜጎች ለማያባራ የዋጋ ግሽበት እንዲጋለጡ ተገደዋል፡፡ አሁንም የብርና የውጭ ምንዛሪ ተመን ከጥቁር ገበያው ጋር እኩል እንዲሆን ግፊት እየተደረገ ነው የሚለው ወሬ ሽው ሲል፣ መንግሥት በሕዝብና በአገር ላይ ሊደርስ የሚችለውን ቀውስ ከወዲሁ ለመከላከል ዝግጁ መሆን ይኖርበታል፡፡ የሕዝቡ ኑሮ ከመጠን በላይ እየደቀቀ ነው፡፡
ኢትዮጵያ ከሌሎች የአፍሪካ አገሮች በባሰ ሊባል በሚችል ሁኔታ ከፍተኛ የምግብ ችግር ያለባት አገር ናት፡፡ በተደጋጋሚ በሚያጋጥሙ ድርቅ፣ ጦርነትና ሌሎች የተፈጥሮ አደጋዎች ምክንያት በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች አስቸኳይ የምግብ ዕርዳታ ይለመንላቸዋል፡፡ ከአስቸኳይ ዕርዳታ በተጨማሪ በሴፍቲኔት ፕሮግራሞች ሕይወታቸውን የሚመሩ በሚሊዮኖች ይቆጠራሉ፡፡ አርሶ አደሩም ሆነ አርብቶ አደሩ ሕዝብ በኋላቀር አስተራረስና የእንስሳት ዕርባታ ሳቢያ፣ በቂና ጥራት ያለው ምርት ለአገር ውስጥም ሆነ ለውጭ ገበያ ማቅረብ ይቸገራል፡፡ ራሱም እጅግ የከፋ ድህነት ውስጥ ነው የሚኖረው፡፡ የከተማ ነዋሪዎች በጣም ጥቂት ከሚባሉት በስተቀር ብዙዎች ገቢያቸው ከወጪያቸው ስለማይመጣጠን፣ ለመግለጽ የሚያዳግት የሰቆቃ ሕይወት ነው የሚገፉት፡፡ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ መሠረታዊ የሆነ መዋቅራዊ ችግር ስላለበት በጥናት ላይ የተመሠረተ የመፍትሔ ዕርምጃ ያስፈልገዋል፡፡ የውጭ ብድርና ድጋፍ ለማግኘት በሚል ብቻ ጣጣ የሚያስከትሉ ውሳኔዎችን በጥድፊያ ከመወሰን በፊት፣ በመስኩ የደረጀ ዕውቀት ባላቸው ባለሙያዎች ዕገዛ አማራጮችን ማየት የመንግሥት ኃላፊነት ነው፡፡
በማኅበራዊ መስኮች በርካታ ችግሮች ያሉባት ኢትዮጵያ ከምንም በላይ የሚያሳስባት የወጣቶች ሥራ አጥነት ነው፡፡ ከአጠቃላይ ሕዝቡ 70 በመቶ የሚሆነው የወጣት ኃይል ውስጥ አብዛኛው ሥራ ፈላጊ ነው፡፡ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና ከቴክኒክና ሙያ ተቋማት በየዓመቱ በመቶ ሺዎች እየተመረቁ ቢወጡም፣ በጣም ትንሽ ከሚባሉት በስተቀር ሥራ ማግኘት አልቻሉም፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ በግብርና፣ በእንስሳት ሀብት፣ በማዕድናት ልማት፣ በቱሪዝምና ሆቴል ኢንዱስትሪ፣ በቴክኖሎጂ፣ በጤና፣ በትምህርትና በሌሎች መስኮች በርካታ ወጣቶችን በማሳተፍ የሥራ ዕድል ማመቻቸት ይቻላል፡፡ ትምህርትና ክህሎት ከሚጠይቁ ዘርፎች በተጨማሪ፣ ማንም ሰው ሊሳተፍባቸው የሚችሉ የልማት ሥራዎች በርካታ ናቸው፡፡ ወጣቶች በተቀጣሪነት፣ በሽርክና፣ እንዲሁም ራሳቸውን ችለው የሚሰማሩባቸው ዕድሎች በብዛት ሊገኙ የሚችሉት የፀጥታ ችግሮችን በማስወገድና አዋጭ ፖሊሲ በመንደፍ ነው፡፡ ይህችን የመሰለች በተፈጥሮ ፀጋዎች የታደለች አገር ወጣቶች በረሃና ባህር እያቆራረጡ ለስደት የሚዳረጉት፣ በዕውቀት ላይ የተመሠረቱ የፖሊሲ አማራጮችን ማየት ባለመፈለጉ ነው፡፡ የወጣቶች ጉዳይ ይታሰብበት፡፡
የፖለቲካው ጉዳይ በተደጋጋሚ ብዙ አስተያየቶች ይቀርቡበታል፡፡ የአገሪቱ የፖለቲካ ምኅዳር ቅርፅና ይዘት አልባ ሆኖ በርካታ ምስቅልቅሎች ይስተዋሉበታል፡፡ ቀድሞ የምናውቀው የፖለቲካ ባህል እንዴት እንደተቀየረ ሳይታወቅ፣ ርዕዮተ ዓለማዊ መሠረቶችን የጨበጡ ውይይቶችና ክርክሮች አይሰሙም፡፡ ፖለቲካው፣ ኢኮኖሚው፣ ዲፕሎማሲውና ሌሎች ማኅበራዊ ተግዳሮቶችን ለማዘመን የሚረዱ የፖሊሲ አማራጮች መስማት ብርቅ ሆኗል፡፡ የፌዴራል ሥርዓቱ ምን ዓይነት ቅርፅና ይዘት ይኑረው፣ የየትኞቹን አገሮች በምሳሌነት ይከተል፣ የግልና የቡድን መብቶች እንዴት ይከበሩ፣ የንብረትና የይዞታ መብት ምን ይምሰል፣ ኢኮኖሚው በምን ዓይነት ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ይመራ፣ የትምህርት ሥርዓቱ እንዴት ይስተካከል፣ የአገሪቱ ዲፕሎማሲ ምን ዓይነት ዓምዶች ይኑሩት፣ ወዘተ የሚሉ ክርክሮችና አማራጮች ከጠፉ ሰንብተዋል፡፡ ከዚህ ይልቅ ብዙዎቹ ፖለቲከኞች ለውይይትና ለድርድር ጀርባ በመስጠት ጦር ሰባቂ ሆነዋል፡፡ ብሔርና እምነት ውስጥ እየተለጠፉ ለሕዝብና ለአገር ግጭት ይጠምቃሉ፡፡ እንዲህ ዓይነቱ በቅራኔ የተጀቦነ የፖለቲካ ሥራ አገርን በተደጋጋሚ ለግጭቶችና ለአውዳሚ ጦርነት እየዳረገ በመሆኑ፣ ፖለቲከኞች ለአገርና ለሕዝብ የምታስቡ ከሆነ ይብቃ በሉ፡፡
ኢትዮጵያ ሰላም አግኝታ በዕድገት ወደፊት መገስገስ የምትችለው፣ ሁሉም ኢትዮጵያውያን በእኩልነትና በነፃነት የሚኖሩበት ሥርዓት በጋራ ለማነፅ ፈቃደኝነት ሲኖር ነው፡፡ የገዥው ፓርቲንና የመንግሥት ሥልጣንን የጨበጡ ሰዎች ሁሉንም ነገር የመጠቅለል አባዜ ውስጥ ሲሆኑ፣ የእነሱ ተፎካካሪዎችም በዚያው መንገድ በመንጎድ የሥልጣን ትንቅንቅ ውስጥ ሲገቡ ሁሌም ግጭትና ውድመት ይኖራል፡፡ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ምኅዳር ምን መምሰል እንዳለበት የጋራ አቋም ከሌለ፣ ኢኮኖሚው እንዴት ቢመራ ከድህነት ውስጥ መውጣት እንደሚቻል መግባባት ላይ ካልተደረሰ፣ በዘርፈ ብዙ ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ተቀራራቢ መሆን ካልተቻለ ከችግር አዙሪት ውስጥ ለመውጣት አይታሰብም፡፡ ምግብ በአግባቡ ማግኘት የማይቻልባት አገር ውስጥ ትርፍ አምርቶ ከድህነት ከመገላገል የበለጠ ምን ሌላ ተግባር አለ? ፖለቲካዊ ውዝግቦችን ፈር አስይዞ ሰላምን በማስፈን አውዳሚ ግጭቶችን ከማስቆም የበለጠ ምን የሚቀድም ሥራ አለ? ከውጭ ተፅፅኖና ጫና ለመገላገል የሚረዱ መፍትሔዎች ላይ ከማተኮር የበለጠ ምን ኃላፊነት ይኖራል? ለኢትዮጵያ እናስባለን የምትሉ በሙሉ ከችግር ፈጣሪነት ተቆጠቡ፡፡ ችግር ፈጣሪነት ያተረፈው ድህነትና ውርደት ብቻ ነው!