ፈቃድ ሳይኖራቸው የኦንላይን ሚዲያ በመክፈት ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በኃይል ለመናድ፣ ሕዝብን ከሕዝብ ጋር ለማጋጨትና አንዱን ሃይማኖት ከሌላው ጋር ለማጋጨት በሕገወጥ መንገድ ሲንቀሳቀሱ ተደርሶባቸዋል በማለት ተጠርጥረው ታስረው የነበሩት ጋዜጠኛ ዳዊት በጋሻውና ጋዜጠኛ ቴዎድሮስ አስፋው እያንዳንዳቸው በ20,000 ብር ዋስ ከእስር እንዲፈቱ ትናንት ሚያዚያ 17 ቀን 2015 ዓ.ም. ውሳኔ ተሰጠ፡፡
ውሳኔውን የሰጠው የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ጊዜ ቀጠሮ ችሎት፣ ፖሊስ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ቢጠይቅም፣ ፍርድ ቤቱ ጥያቄውን ውድቅ በማድረግ ዋስተናውን ፈቅዷል፡፡
የኢትዮ ሰላም ኦንላይን ሚዲያ ጋዜጠኛ ቴዎድሮስ ሚያዚያ 5 ቀን 2015 ዓ.ም. እና የቀድሞው የ“አል አይን ኒውስ” ጋዜጠኛና የአራት ኪሎ ሚዲያ ዩቲዩብ አዘጋጅ ጋዜጠኛ ዳዊት በጋሻው፣ ሚያዚያ 4 ቀን 2015 ዓ.ም. ምሽት ላይ ባህርዳር ከሚገኘው “ሆምላንድ ሆቴል” በፀጥታ ኃይሎች መወሰዱን መዘገባችን ይታወሳል።