- የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ወደ ፕሪምየር ሊግ አድጓል
የዘንድሮ ቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ጨዋታዎች በሃዋሳ ከተማ ከ25ኛ ሳምንት ጨዋታ ጀምሮ የሚካሄዱት የአምስት ሳምንታት ጨዋታዎች የቀጥታ የቴሊቪዥን ሥርጭት ሽፋን እንደማያገኙ የፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማኅበሩ አስታውቋል፡፡
ማኅበሩ ግንቦት 9 ቀን 2015 ዓ.ም. በማኅበራዊ ትስስር ገጹ እንዳስታወቀው፣ አክሲዮን ማኅበሩ ከመልቲቾይዝ አፍሪካ (ዲኤስቲቪ) ጋር ባለው የብሮድካስት ውል መሠረት፣ ከ25ኛ ሳምንት በኋላ ያሉ ጨዋታዎች በቀጥታ ሥርጭት ባይተላለፉም፣ የቪድዮ ቀረፃ ተከናውኖ ለአስፈላጊው አገልግሎት ከጥቅም እንዲውሉ ይደረጋል።
የሱፐር ስፖርት ሽፋን እያገኘ እስከ 24ኛ ሳምንት መርሐ ግብር የተካሄደው የሊጉ ውድድር ተመልሶ የቀጥታ ሥርጭት የሚያገኘው፣ በመጨረሻው የ30ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ላይ መሆኑን አክሲዮን ማኅበሩ አስታውቋል።
በሌላ ዜና ከፕሪሚየር ሊጉ በመውረዱ ምክንያት ለስድስት ዓመታት ተለይቶ የነበረው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፣ በምድብ ጨዋታው ተከታዩ የነበረው የቤንች ማጂ ቡና ክለብ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ 2ለ1 በመረታቱ ዳግም ወደ ፕሪሚየር ሊግ መመለሱን አረጋግጧል።
የንግድ ባንክ ክለብ በ2009 ዓ.ም. ከፕሪሚየር ሊጉ መውረዱን ተከትሎ የተበተነ ሲሆን፣ ህልውናውን ባጣ በሁለት ዓመቱ ተመልሶ በከፍተኛ ሊግ መወዳደር የቻለው ኢኮስኮን ክለብ በመግዛት እንደነበር ይታወሳል፡፡
የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ ምድብ ሀን እየመራ ያለው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ክለብ፣ ሁለት ጨዋታዎች እየቀሩት ነው ወደ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የ2016 የውድድር ዓመት ማደጉን ከወዲሁ ያረጋገጠው።