የኢትዮጵያ ማዕድን፣ ነዳጅና ባዮፊዩል ኮርፖሬሽን ዋና መሥሪያ ቤት ዘረፋ እንደተፈጸመበት የሪፖርተር ምንጮች ገለጹ፡፡
ዘረፋው የተካሄደው ባለፈው ሳምንት እንደሆነ የተናገሩት ምንጮቹ፣ በዋና መሥሪያ ቤቱ ውስጥ የሚገኙ የከበሩ ማዕድናትና የድርጅቱ ንብረቶች እንደተዘረፉ ተናግረዋል፡፡
የኮርፖሬሽኑ ዋና መሥሪያ ቤት 22 አካባቢ አውራሪስ ሆቴል ጀርባ የሚገኝ ሲሆን፣ ከዘረፋው ጀርባ የድርጅቱ ሠራተኞች ተጠርጥረው በሕግ መያዛቸውን ምንጮቹ ተናግረዋል፡፡
በጉዳዩ ላይ ሪፖርተር መረጃ የጠየቃቸው የኮርፖሬሽኑ የኮሙዩኒኬሽን ኃላፊ አቶ ባጫ ፋጂ፣ የዓመት ፈቃድ ላይ መሆናቸውን ገልጸው ምላሽ ለመስጠት ባይችሉም፣ የኮርፖሬሽኑ ሥራ አስፈጻሚ ራሔል ጌታቸው፣ ዘረፋውን በተመለከተ ጉዳዩ በሕግ መያዙንና ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ተናግረዋል፡፡
ስለተፈጸመው ጉዳይ ዝርዝር ሁኔታ መረጃ እንደሌላቸው ገልጸው በሕግ የተያዘ ጉዳይ ሳይጣራ ለሚዲያ ተቋማት መረጃ መስጠት እንደማይችሉም ገልጸዋል፡፡
ኮርፖሬሽኑ በ2007 ዓ.ም. በ15 ቢሊዮን ብር የተፈቀደ ካፒታልና በአራት ቢሊዮን ብር በጥሬ ገንዘብና በዓይነት በተከፈለ ካፒታል የተቋቋመ ነው፡፡
በኦሮሚያ ክልል በጉጂ ዞን አዶላ ወርቅ፣ የቀንጥቻ ታንታለምን ጨምሮ ያዩ ማዳበሪያ ፋብሪካና ሌሎችም ፕሮጀክቶች ላይ ኮርፖሬሽኑ ይሠራ እንደነበር ይታወሳል፡፡
ይሁን እንጂ በታኅሳስ ወር 2014 ዓ.ም. በጉጂ ዞን የሚገኘው የቀንጢቻ ታንታለም ምርት ፈቃዱ ተሰርዞ ለኦሮሚያ ማዕድን ሼር ካምፓኒ መሰጠቱ ይታወሳል፡፡
ኮርፖሬሽኑ በኢትዮጵያ የሚገኘውን የተፈጥሮ ሀብት እንዲያለማ በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ የተቋቋመ የመንግሥት የልማት ድርጅት ነው፡፡
ነዳጅን ጨምሮ በተለያዩ የማዕድን ዘርፎች ላይ እንዲሠራ በከፍተኛ ሁኔታ የተጠበቀ ኮርፖሬሽን ሲሆን፣ በፋይናንስ እጥረትና አሳማኝ ባልሆኑ ምክንያቶች የተለያዩ የማዕድን ፕሮጀክቶቹ ተወስደው ለሌላ ተሰጥተዋል፡፡
ኮርፖሬሽኑ በፊት በመንግሥት የልማት ድርጅቶች ሆልዲንግና አስተዳደር ሥር የነበረ ሲሆን፣ ከዚያም ወደ ማዕድን ሚኒስቴር፣ በቅርቡ ደግሞ በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ሥር ከተጠቃለሉት 27 የመንግሥት ልማት ድርጅቶች ውስጥ አንዱ ነው፡፡