በዳንኤል ንጉሤ
በትግራይ ክልል ላለፉት አራት ወራት ዕርዳታ ተቋርጦብናል ያሉ ተፈናቃዮች፣ ትናንት ማክሰኞ ግንቦት 15 ቀን 2015 ዓ.ም. በተለያዩ አካባቢዎች ሰላማዊ ሠልፎች አደረጉ። በሰላማዊ ሠልፎቹ የተሳተፉት ተፈናቃዮች ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ ዕርዳታ በመቋረጡ ሕፃናት፣ እናቶችና አዛውንቶች በሕመምና በሞት እየተሠቃዩ ናቸው፡፡
ከሑመራ ተፈናቅለው በሽሬ ዳስ ተስፋይ መጠለያ ካምፕ የሚገኙት አቶ ኪሮስ ዝበሎ፣ መንግሥት በአስቸኳይ ዕርዳታ መስጠት እንዲጀምር ለማሳሰብ ሰላማዊ ሠልፍ መደረጉን ገልጸዋል። ሰላማዊ ሠልፍ አድራጊዎቹ ወደ ትውልድ ቦታቸውና ወደ እርሻቸው መመለስ እንደሚፈልጉ መጠየቃቸውን አክለዋል።
ሰላማዊ ሠልፎቹ ከጠዋት 2፡00 ሰዓት ጀምሮ እስከ እኩለ ቀን ድረስ ሲካሄዱ የአስቸኳይ ጊዜ ዕርዳታ አስፈላጊነትን የሚገልጹ መልዕክቶች በተጻፉባቸው ሰሌዳዎች፣ ‹‹ለልጆቻችን ዕርዳታ እንፈልጋለን››፣ ‹‹የትግራይ ሥቃይ ይቁም›› እና ‹‹ወደ ቀዬአችን ተመልሰን ማረስ እንፈልጋለን›› የሚሉ መፈክሮች ታይተዋል፡፡
በሰላማዊ ሠልፎቹ ሴቶች፣ ሕፃናትና አረጋውያንን ጨምሮ የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች መሳተፋቸው ታውቋል፡፡ መቀሌ፣ አዲግራት፣ አክሱምና ሑመራን ጨምሮ፣ በተለያዩ ከተሞች በጎዳናዎች ላይ በተደረጉ ሠልፎች ተመሳሳይ ጥያቄዎች ቀርበዋል።
ሰላማዊ ሠልፉን ያዘጋጁት የተለያዩ አካላትና የሲቪክ ማኅበራት ናቸው። የሲቪክ ማኅበራት አስተባባሪ አቶ ተወልደ ክንፈ እንዳሉት፣ መንግሥት አስቸኳይ ዕርዳታ በክልሉ እንዲጀምር ጥሪ ቀርቦለታል፡፡ አያይዘውም ሰላማዊ ሠልፎቹ ምንም ዓይነት ረብሻ ሳይኖር መጠናቀቃቸውን ተናግረዋል።
በሰላማዊ ሠልፎቹ የተሳተፉት ወገኖች በበኩላቸው፣ መንግሥት በክልሉ አስቸኳይ ዕርዳታ እስኪጀምር ድረስ በሰላማዊ ሠልፍ ጥያቄያቸውን እንደሚያቀርቡ ገልጸዋል፡፡
የትግራይ ክልል ጦርነት ከጀመረበት ከጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ ለሰብዓዊ ቀውስ መዳረጉ ይታወሳል። ጦርነቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች መፈናቀላቸው የሚታወስ ሲሆን፣ በርካቶች አሁንም በመጠለያ ካምፖች ውስጥ መሠረታዊ አቅርቦቶች ሳይሟሉላቸው በችግር ውስጥ መሆናቸው ይነገራል፡፡
በክልሉ ላለፉት አራት ወራት ዕርዳታ በመቋረጡ ምክንያት በርካታ ዜጎች በምግብ ዕጦትና በሕመም እየተሠቃዩ መሆናቸውን፣ በክልሉ ሊደርስ የሚችለውን ሰብዓዊ አደጋ ለመከላከል የፌዴራል መንግሥት በአስቸኳይ ጣልቃ እንዲገባ ተፈናቃዮቹ መጠየቃቸው ታውቋል፡፡
የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ስለሰላማዊ ሠልፉ የሰጠው መግለጫ ባይኖርም፣ በክልሉ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ በመገንዘብ ችግሩን ለመፍታት እየሠራ መሆኑን ለአስተዳደሩ ቅርበት ያላቸው ምንጮች ገልጸዋል። የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትና ሌሎች ዓለም አቀፍ ድርጅቶች በትግራይ ያለውን ሁኔታ ተገንዝበው፣ በአስቸኳይ ዕርዳታ እንዲጀምሩ መጠየቁ ይታወሳል።
ትናንት ማክሰኞ በትግራይ ክልል የተደረጉት ሰላማዊ ሠልፎች የትግራይ ተወላጆች በክልሉ ባለው ሁኔታ መከፋታቸውን የሚያሳይ እንደሆነ የተንቤን ተፈናቃዮች አስተባባሪ አቶ ገብረ መድኅን ገብረ እግዚአብሔር ተናግረዋል። በክልሉ የሚደርሰውን ሰብዓዊ አደጋ ለመከላከል መንግሥት አፋጣኝ ዕርምጃ እንዲወስድ ጥያቄ እንደቀረበለት አክለዋል፡፡