ከ1.5 ቢሊዮን ብር በላይ ይፈጃል የተባለውን የዋና መሥሪያ ቤቱን ሕንፃ ያስመረቀው ዘመን ባንክ፣ ከዘመን ኢንሹራንስ ጋር ምንም ዓይነት የባለቤትነት ግንኙነት እንደሌለው አስታወቀ፡፡
ባንኩ የዋና መሥሪያ ቤቱን ምርቃት በማስመልከት በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ከጋዜጠኞች የቀረበለትን ጥያቄ መሠረት በማድረግ፣ የባንኩ የሥራ ኃላፊዎች በሰጡት ምላሽ ከዘመን ኢንሹራንስ አ.ማ. ጋር ምንም ዓይነት የባለቤትነት ግንኙነት እንደሌላቸው አስታውቀዋል፡፡
በብዙዎች ዘንድ ‹‹ዘመን ባንክና ዘመን ኢንሹራንስ እህትማማች ኩባንያዎች ናቸው›› የሚል ምልከታ ቢኖራቸውም፣ የባንኩ ኃላፊዎች ግን ይህ ትክክል አለመሆኑን አመልክተዋል፡፡ ብዙ ጊዜ ይህ ጥያቄ የሚነሳ ስለመሆኑ የገለጹት የባንኩ ዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ኤርሚያስ እሸቱ፣ ‹‹ዘመን ኢንሹራንስ›› በባንኩ ስያሜ መጠራቱ ግን ቅር እንደሚያሰኛቸው ገልጸዋል። ዘመን ኢንሹራንስም ከዘመን ባንክ ጋር በሥራም ሆነ በባለቤትነት ደረጃ የሚያገናኘው ነገር እንደሌለ አስታውቀል።
‹‹የዘመን ባንክ ባለአክሲዮኖች ራሳቸውን የቻሉ ባለአክሲዮኖች ናቸው፤›› ያሉት አቶ ኤርሚያስ፣ ዘመን ኢንሹራንስ ብለው የመሠረቱት ደግሞ ራሳቸውን የቻሉ ሌሎች ባለአክሲዮኖች መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ ዘመን ኢንሹራንስ የሚለው ስያሜ ለኢንሹራንስ ኩባንያው መፈቀዱ፣ የዘመን ባንክን ባለአክሲዮኖች ቅር እንዳሰኘ፣ የባንኩ ደንበኞችም በተደጋጋሚ ጥያቄ እንደሚያቀርቡላቸው ተናግረዋል።
‹‹በመሆኑም እኛ ምንም የሥራም የባለቤትነትም ግንኙነት እንደሌለን አሁንም ማሳሰብ እንፈልጋለን፤›› በማለት አስታውቀዋል፡፡
በዚህ ጉዳይ ላይ ተጨማሪ ማብራሪያ የሰጡት የዘመን ባንክ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ደረጀ ዘበነ፣ በኢንዱስትሪው ውስጥ እንዳለ ተቋም ከዘመን ኢንሹራንስ ጋር በትብብር ሊሠሩ እንደሚችሉ፣ ነገር ግን ባንኩ በዘመን ኢንሹራንስ ውስጥ ምንም የባለቤትነት ድርሻ እንደሌለው አረጋግጠዋል፡፡ የስም መጋራቱ የሚፈጥረው ብዥታ መኖሩን ያስታወሱት አቶ ደረጀ፣ ይህንንም ማኅበረሰቡ ሊያውቀው እንደሚገባ አመልክተዋል፡፡
ከዚህ ጥያቄ ባሻገር ዘመን ባንክን በመመሥረት በዋናነት የሚጠቀሱት አቶ ኤርሚያስ አመልጋን በተመለከተ፣ አሁን ያላቸው ድርሻ ምን እንደሆነና ለባንኩ ያበረከቱትን አስተዋጽኦን በመዘከር ረገድ ምን እንደታሰበ ለቀረበላቸው ጥያቄ አቶ ኤርሚያስ በሰጡት ምላሽ፣ በአሁኑ ወቅት አቶ ኤርሚያስ አመልጋ በዘመን ባንክ ውስጥ ምንም ዓይነት ድርሻ እንደሌላቸው አመልክተዋል፡፡ በዚህ ጥያቄ ላይ ማብራሪያ የሰጡት አቶ ኤርሚያስ እሸቱ፣ አቶ ኤርሚያስ ዘመን ባንክን በመመሥረት ረገድ ባለውለታ መሆናቸውን የገለጹት አቶ ኤርሚያስ እሸቱ፣ ይሁን እንጂ አቶ ኤርሚያስ አመልጋ በባንኩ ውስጥ የነበራቸውን የአክሲዮን ድርሻ በተለያየ ምክንያት ማጣታቸውን ወይም በአሁኑ ወቅት የሌሎች ሰዎች መሆኑን አብራርተዋል፡፡
‹‹ለዘመን ባንክ እዚህ መድረስ መሥራቾች ያበረከቱት አስተዋጽኦ ሊካድ አይችልም፤›› ያሉት አቶ ኤርሚያስ እሸቱ፣ በኢትዮጵያ ንግድ ሕግ መሠረት የባንክ መሥራች ተብለው የሚጠቀሱት አቶ ኤርሚያስ አመልጋና አቶ ተክሌ ዓለምነህ መሆናቸውን አስታውሰዋል፡፡ የባንኩ ጠንሳሽ መሆናቸውንም የገለጹት አቶ ኤርሚያስ፣ ይህንን ራዕይ ሰንቀው ሲነሱ የነበራቸው ዓላማ በዚህ መልኩ ተሳክቶ ሲያዩት መቶ በመቶ ደስተኛ ይሆናሉ ብለው እንደሚያምኑ ገልጸዋል፡፡ ነገር ግን ከባንኩ የምሥረታ ሐሳብ አመንጪነታቸው በአሁኑ ሰዓት በባንኩ ላይ አክቲቭ የሆነ ድርሻ የላቸውም፡፡
የባንኩ መሥራቾች ባንኩን እዚህ እንዲደርስ ስለማድረጋቸው ቦርዱም ሆነ ማኔጅመንቱ ከፍተኛ ከአክብሮት እንዳለው የገለጹት አቶ ደረጀ በበኩላቸው፣ ‹‹እንደ አጋጣሚና ዕድል ሆኖ ግን አቶ ኤርሚያስ ባንኩ ውስጥ ምንም ዓይነት ድርሻ ባይኖራቸውም፣ በባንኩ ምሥረታ ታሪክ የሚዘክራቸው ይሆናል፡፡ አቶ ተክሌ ግን አሁንም በባንኩ ውስጥ ድርሻ ያላቸውን መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
እንደ ምንጮች ገለጻ፣ አቶ ኤርሚያስ መሥራች ሆነው የባለቤትነት ድርሻውን ያጡት በተለያዩ ክሶች አክሲዮናቸው በፍርድ ቤት ውሳኔ ለሌላ እንዲተላለፍ በመደረጉ ነው፡፡ በባንኩ ውስጥም በመረጃ የተደገፈ ከ1.2 ሚሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸው አክሲዮኖች ባለቤት እንደነበሩም እነዚሁ ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡
አሥራ አምስተኛ ዓመቱን የያዘው ዘመን ባንክ በኢትዮጵያ የባንክ ኢንዱስትሪ ውስጥ ለየት ባለመልኩ ወደ ሥራ የገባና በየዓመቱ እያደገ የመጣ ባንክ መሆኑ ተገልጿል፡፡
የባንኩ የዳሬክተሮች ቦርድ ሊቀመንበር አቶ ኤርሚያስ እንደገለጹትም፣ ባለፉት ዓመት ባንኩ በየዓመቱ በአማካይ 40 በመቶ እያደገ መምጣቱን ነው፡፡ ከአትራፊነት አንፃርም ዕድገት እያሳየ በመምጣት በ2015 የሒሳብ ዓመት ባንኩ ከታክስ በፊት ከሦስት ቢሊዮን ብር በላይ ያተርፋል ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጸዋል፡፡
በቀዳሚው ዓመት ከታክስ በፊት 2.1 ቢሊዮን ብር በማትረፍ ያጠናቅቀ በመሆኑ፣ ዘንድሮ ያገኛል ተብሎ የሚጠበቀው ትርፍ ወደ አንድ ቢሊዮን ብር ብልጫ ያለው እንደሚሆን የሚያመለክት ነው፡፡
ያለፉት አምስት ዓመታት ትርፍ ድርሻም በአማካይ 40 በመቶ የደረሰ በመሆኑ፣ ይህም ዘመን ባንክ በባንክ ኢንዱስትሪው ውስጥ ከፍተኛ ተብሎ ከሚመደቡት ውስጥ አንዱ ያደርገዋልም ተብሏል፡፡
ይህ የባንኩን ፈጣን ዕድገት የሚሳይ ስለመሆኑ የሚያመለክተው የባንኩ መረጃ፣ በተለይ በውስን የሰው ኃይልና የባንክ ቅርንጫፎች ቁጥር፣ እንዲሁም በአነስተኛ አስተዳደራዊ ወጪ፣ የተመዘገበ በከፍተኛ ውጤት በመሆኑ፣ ባንኩ በአሠራሩ ሀብቱን በአግባቡ በመጠቀም ረገድ ልዩ ያደርገዋል ተብሏል፡፡ ይህንኑ ዕድገቱን ከዚህም ለማላቅ ባንኩ በቀጣይ ተደራሽነቱን የማስፋትና የደንበኞችን ቁጥር የመጨመር ሥራውን በስፋት እያከናወነና የአሥር ዓመት ስትራቴጂ ነድፎ ወደ ትግበራ መግባቱንም ጠቅሷል፡፡
የባንኩ የብድር ሥርጭትን በተመለከተ ከተሰጠው ማብራሪያ መረዳት እንደሚቻለው፣ ካለፉት አምስት ተከታታይ ዓመታት ወዲህ በከፍተኛ ፍጥነት እያደገ ነው ተብሏል፡፡ ባንኩ እስካሁን ለተለያዩ ዘርፎች ከ30 ቢሊዮን ብር በላይ የብድር አቅርቦትን አሠራጭቷል፡፡
የባንኩን ተቀማጭ ገንዘብን ከማሳደግ አኳያም ባደረገው ጥረት፣ በአሁኑ ሰዓት የባንኩ ተቀማጭ ገንዘብ ከ35 ቢሊዮን ብር በላይ ደርሷል፡፡ የባንኩ አጠቃላይ ካፒታል ከስድስት ቢሊዮን ብርና የተከፈለ ካፒታሉ ደግሞ 4.7 ቢሊዮን ብር መድረሱ ተገልጿል፡፡ ባንኩ ጠቅላላ ሀብቱ ከ40 ቢሊዮን ብር በላይ የደረሰ ሲሆን፣ የሀብት መጠኑን ለማሳደግ ይረዳል የተባለ ተጨማሪ ሥራዎችን በመሥራት ላይ እንደሚገኝም ተብራርቷል፡፡
ባንኩ የማኅበራዊ ኃላፊነትን ከመወጣት አኳም የዘንድሮ ጨምሮ ባለፉት አምስት ዓመታት በአጠቃላይ ከ150 ሚሊዮን ብር በላይ ለማኅበራዊ ኃላፊነት ድጋፍ አድጌያለሁ ብሏል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ዘመን ባንክ ወደ 1.5 ቢሊዮን ብር ወጪ ያወጣበትን ባለ 36 ወለል የዋና መሥሪያ ቤት ሕንፃ ግንባታ አጠናቅቆ ሥራ ማስጀመሩን በማስታወቅ በይፋ አስመርቋል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ በዘመናዊ መንገድ ከተገነቡ ሕንፃዎች አንዱ መሆኑ የተጠቀሰው ይህ ዘመናዊ ሕንፃ፣ አጠቃላይ ግንባታው ወደ አምስት ዓመታት የፈጀ ሲሆን ‹‹ቻይና ውዩ›› የተባለ የቻይና ኩባንያ የተገነባ ነው፡፡ ዲዛይኑን የሠራው ደግሞ አገር በቀሉ ‹‹ጂዳው ኮንሰልታንት›› ነው፡፡ የግንባታ ስምምነቱ በተደረገበት ወቅት በቁርጥ ዋጋ በ1.2 ቢሊዮን ብር ዋጋ ግንባታውን ለማጠናቀቅ ቢሆንም፣ ወደ ግንባታ ከተገባ በኋላ በተደረጉ ተጨማሪ ሥራዎች ምክንያት ተጨማሪ ወጪ በመጠየቁ፣ አሁን ላይ አጠቃላይ የግንባታ ወጪው ወደ 1.5 ቢሊዮን ብር ሊደርስ መቻሉ ተጠቅሷል፡፡
ይህ ዘመናዊ የባንኩ ዋና መሥሪያ ቤት ሕንፃ በዓለም አቀፍ ደረጃ ማረጋገጫ የተሰጣቸው ግብዓቶች ያሉት ሲሆን፣ ስምንት አሳንሰሮች የተገጠሙለትም ነው፡፡ ለከተማዋ አንድ ድምቀትና ለባለአክሲዮኖች ሀብት እንደሆነ የጠቀሱት አቶ ደረጀ ለደንበኞችም ዋስትና የሚሰጥ መሆኑን አመልክተዋል፡፡ ባንኩ ይህንን ሕንፃ አስገንብቶ ሥራ ማስጀመሩም ባንኩ ለዋና መሥሪያ ቤትነት ሲጠቀምባቸው ለነበሩ ሕንፃዎች በዓመት ይከፍል የነበረውን ከ40 ሚሊዮን ብር በላይ ያስቀረለት መሆኑም ተገልጿል፡፡
‹‹ይህ ሕንፃ አጠቃላይ ግንባታው በ1.5 ይጠናቀቅ እንጂ፣ አሁን ባለው ዋጋ ሲገመት ከ200 ሚሊዮን ዶላር በላይ (ከአሥር ቢሊዮን ብር በላይ) እንደሚሆን ደግሞ አቶ ኤርሚያስ ገልጸዋል፡፡ ስለዚህ ትልቅ ሀብት ያፈራ መሆኑን ያሳያል፡፡
እንዲሁም ዘመናዊ የፅዳትና የንፅህና መጠበቂያ፣ እንዲሁም የአካል ብቃት መጎልበቻ ክፍሎች፣ እስከ ሁለት በመቶ ተሳታፊዎችን የሚይዙ አቅም ያላቸው ስብሰባ አዳራሾች፣ እንዳንዳቸው 13 ተሳፋሪዎችን የሚያጓጉዝ ስድስት አሳንሰሮችና 200 ተሽከርከሪዎችን ማቆየት የሚያስችል የምድር ቤትና ፎቅ ተሽከርከሪ ማቆሚያዎችን ይዟል፡፡
እነዚህ ማቆያዎች ከምድር በላይ ከአምስት እስከ አምስተኛ ፎቅ የሚገኙም ናቸው፡፡ ሕንፃው በ2,300 ካሬ ሜትር ስፋት ላይ ያረፈሰ ሲሆን፣ ከፊልና ሙሉ ምድር ቤቱን ጨምሮ 36 ወለሎች አሉት፡፡ ዘመን ባንክ በአሁኑ ወቅት ካፒታሉን ወደ 15 ቢሊዮን ብር ለማሳደግ ውሳኔ ያሳለፈ ሲሆን፣ ከሐምሌ 2015 ዓ.ም. ጀምሮ አዲስ ያፀደቀውን ካፒታል ለማሟላት የአክሲዮን ሽያጭ ይጀምራል፡፡