ድመቶች አብዛኛውን ጊዜ በጨለማ ንቁ ናቸው። ከጨለመ በኋላ በአቅራቢያቸው ያሉ ነገሮችን ለይተው ለማወቅና አድነው የሚበሉትን እንስሳ ለመያዝ የሚረዷቸው ጢሞቻቸው እንደሆኑ ከሁኔታው መረዳት ይቻላል።
የድመት ጢሞች የሚበቅሉት ብዙ የነርቭ ጫፎች ባሏቸው ሕብረ ሕዋሳት ላይ ነው። እነዚህ ነርቮች በአየሩ ላይ የሚፈጠረው በጣም ትንሽ እንቅስቃሴ እንኳ ይሰማቸዋል። በዚህም የተነሳ ድመቶች በአቅራቢያቸው ያሉ ነገሮችን ባያዩአቸውም እንኳ መኖራቸውን ማወቅ ይችላሉ፤ ይህ ደግሞ በጨለማ እንደሚጠቅማቸው ግልጽ ነው።
የድመት ጢሞች ትንሹም እንቅስቃሴ ቶሎ የሚሰማቸው መሆኑ አንድ ነገር ወይም አድነው የሚበሉት አንድ እንስሳ ያለበትን ቦታና የሚያደርገውን እንቅስቃሴ ለይተው እንዲያውቁ ያስችላቸዋል። በተጨማሪም ድመቶች በአንድ ክፍተት በኩል ለማለፍ ሲሞክሩ ጢሞቻቸው የክፍተቱን ስፋት ለመለካት ይረዷቸዋል።
ኢንሳይክሎፒዲያ ብሪታኒካ እንደገለጸው ከሆነ የድመት ጢም ያለውን ጥቅም በተመለከተ ማወቅ የተቻለው ከፊሉን ብቻ ነው፤ ይሁን እንጂ ድመቱ ጢሙ ከተቆረጠበት ለጊዜውም ቢሆን እክል እንደሚገጥመው ታውቋል።
የሳይንስ ሊቃውንት፣ የድመት ጢሞችን ንድፍ በመኮረጅ በእንቅፋቶች መሃል እየተሹለከለኩ ለመሄድ የሚያስችሉ ጠቋሚ መሣሪያዎች ያሏቸው ሮቦቶች ለመሥራት ጥረት እያደረጉ ነው። ኢዊስከርስ ተብለው የተጠሩት እነዚህ ጠቋሚ መሣሪያዎች፣ ለተራቀቀ የሮቦት ቴክኖሎጂ፣ የተለያዩ መሣሪያዎችን ለአጠቃቀም ምቹ ለማድረግ እንዲሁም በባዮሎጂ መስክ የተለያየ አገልግሎት እንደሚኖራቸው በካሊፎርኒያ የሚገኘው የበርክሊ ዩኒቨርሲቲ የሳይንስ ሊቅ የሆኑት አሊ ጃቪ ተናግረዋል።
- ጄ ደብሊው ዶት ኦርግ