Friday, September 22, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

[ክቡር ሚኒስትሩ አመሻሹን መኖሪያ ቤታቸው ሲደርሱ ባለቤታቸው በቴሌቪዥን የሚተላለፈው የማዕከላዊ ኮሚቴ ገለጻ እየተከታተሉ አገኟቸውና አጠገባቸው ተቀምጠው የደረሱበትን አብረው መከታተል እንደጀመሩ፣ ባለቤታቸው ቴሌቪዥኑን ትተው መጠየቅ ጀመሩ]

  • እኔ ምለው?
  • እሺ… አንቺ የምትይው?
  • የማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ አባላት እንዲያወሩ ወይም እንዲጠይቁ አይፈቀድም እንዴ?
  • እንዴት ይከለከላል?
  • ታዲያ ለምንድነው ፕሬዚዳንቱ ብቻ የሚያወሩት?
  • እያወሩ አይደለም፣ ገለጻ እያደረጉ ነው።
  • ቢሆንም አንድም አባል ሲጠይቅ ወይም ሐሳብ ሲያቀርብ አይቼ አላውቅም፡፡
  • አጋጣሚ ይሆናል።
  • ዛሬ ብቻ እኮ አይደለም፡፡
  • ቆይ ይህ ጉዳይ ለምን አሳሰበሽ?
  • እንዴት አገር የሚመሩ ሰዎች በሐሳብ አይሟገቱም የሚል ጥያቄ ተፈጥሮብኝ ነው፣ ግን ትሟገታላችሁ?
  • ለምን እንሟገታለን? የአንድ ድርጅት አባላት አይደለን አንዴ?
  • እሱማ ነው፣ ቢሆኑም የተለያየ ምልከታ ያላቸው አባላት የተሰባሰቡበት ድርጅት ነው ብዬ ነው፣ ያልገባችሁንስ ትጠይቃላችሁ?
  • ግልጽነት የሚሻ ጉዳይ ካለማ እንጠይቃለን።
  • እንደዚያ ከሆነ ጥሩ፣ በል እስኪ አሁን ሲተላለፍ ከሰማሁት ያልተረዳሁትን ልጠይቅህ?
  • ጠይቂኝ… ምንድነው ያልገባሽ?
  • የወል እውነት መፍጠር ያስፈልገናል ያሉት ገብቶኛል፣ ግን ቀጥሎ የተናገሩት ምን ማለት እንደሆነ ልረዳው አልቻልኩም።
  • የትኛውን ነው?
  • የወል እውነት ካልተፈጠረ የአንዱ ኢትዮጵያዊና የሌላው ኢትዮጵያዊ ኢትዮጵያ መስማማት አይችሉም ያሉት ነገር ግልጽ አልሆነልኘም።
  • ቆይ ቃል በቃል ያሉትን ልንገርሽ?
  • እሺ…
  • ‹‹የአንተ ኢትዮጵያ ዕውን የምትሆነው፣ የሌላው ኢትዮጵያዊም ኢትዮጵያ መሆን ስትችል ብቻ ነው፤›› ነው ያሉት፣ ቃል በቃል የተናገሩት ይኼንን ነው።
  • እኮ ምን ማለታቸው ነው?
  • እሳቸው የተናገሩትን ትንሽ ቀየር አድርጌ ባስቀምጠው የሚገባሽ ይመስለኛል።
  • እስኪ አስቀምጥልኝና ልረዳው።
  • በሌላ አነጋገር ምን ማለታቸው መሰለሽ?
  • እህ…?
  • ያንቺ ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ ሆና የምትቀጥለው፣ የሌላው ኢትዮጵያዊ ኢትዮጵያ ዕውን መሆን ስትችል ነው ማለታቸው ነው።
  • የሌላው ኢትዮጵያዊ?
  • አዎ፡፡
  • ሌላው ኢትዮጵያዊ ማነው? የሌላው ኢትዮጵያዊ ኢትዮጵያ እንዴት ያለች ነች?
  • የምጠይቅሽን ከመለስሽ ሌላው ኢትዮጵያዊ ማለት ማን እንደሆነ ይገባሻል።
  • እሺ ጠይቀኝ፡፡
  • አንቺ ኢትዮጵያን እንዴት ትገልጫታለሽ? ኢትዮጵያ ለአንቺ ማናት?
  • ከአበው የተረከብናት የጥንቷ የጠዋቷ፣ ቃል ኪዳን የተገባላት ባለ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ሰንደቋ ኢትዮጵያ ናታ፡፡
  • ይኸውልሽ ገና በአበው ላይ እንኳን የወል ዕውነት አልፈጠርንም፡፡
  • እ… ምን ማለት ነው?
  • እሱ ውስብስብ ታሪክ ስለሆነ እንተወውና ሰንደቅ ዓላማውን ምሳሌ አድርገን ብናወራ ይሻላል።
  • ሰንደቅ ዓላማው ደግሞ ምን ይወጣለታል?
  • አንቺ እንደዚያ ብታምኚም፣ የማይቀበሉትና አምርረው የሚቃወሙት አሉ።
  • ማነው የሚቃወመው?
  • ሌላው ኢትዮጵያዊ።
  • ሌላው ኢትዮጵያዊ የምትላቸው በሕገ መንግሥቱ ደስተኛ አይደሉም?
  • ደስተኛ አይደሉም ማለት?
  • አይቀበሉትም?
  • እንዲያውም ሕገ መንግሥቱ ያጎናፀፋቸው መብት እንዲከበር ነው የሚጠይቁት።
  • ታዲያ እኮ ሕገ መንግሥቱ የአገሪቱን ሰንደቅ ዓላማ እንዳለ ተቀብሎ የሚያስማማ ትርጓሜ ሰጥቷል፡፡
  • አዎ፣ ምን ነበር ድንጋጌው የሚለው?
  • የሰንደቅ ዓላማው ቀለሞች አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ ነው። መካከል ላይ ያለው ዓርማ ደግሞ የሕዝቦችንና ሃይማኖቶችን እኩልነትና በአንድነት ለመኖር ያላቸውን ተስፋ የሚያንፀባርቅ ነው ይላል።
  • ቢሆንም ሌላው ኢትዮጵያዊ ሰንደቅ ዓላማውን አምርሮ ይቃወማል።
  • ምክንያታቸው ምንድነው?
  • የአንድ ወገን ባህልና እምነት፣ ትውፊትና ማንነት በሌሎች ላይ መጫኑን የሚያስታውስ ምልክት ነው ይሉታል።
  • እህ… ከስንት ሺሕ ዘመን በፊት የነበረ የማንነታችን መገለጫ ሆኖ ለሌሎች አፍሪካዊያን ነፃ መሆን ጭምር ተስፋ የፈነጠቀ ምልክት አይደለም እንዴ?
  • እሱማ ልክ ነሽ።
  • እና ለሌላው ኢትዮጵያዊ ሲባል የሌላው ኢትዮጵያ መፍረስ አለባት?
  • ትፍረስ ሳይሆን ጥያቄው መመለስ አለበት ነው።
  • ቆይ አንተ የትኛው ኢትዮጵያዊ ነህ?
  • በግሌ ነው ወይስ በድርጅት ማንነቴ?
  • አንተን ባለቤቴን ነው የጠየቅኩት።
  • በቤተሰብ ደረጃማ አንለያይም።
  • ግልጽ አድርገህ መልስልኝ፡፡
  • ሁለት ኢትዮጵያማ በአንድ ቤት ውስጥ ልትኖረን አትችልም።
  • የትኛው ነህ ማለት ነው? ግልጽ አድርገህ መልስልኝ።
  • የአንቺ ኢትዮጵያ የእኔም ኢትዮጵያ ናት፣ ግን እንዳልኩሽ በቤተሰብ ደረጃ ነው።
  • በድርጅት ደረጃስ?
  • በድርጅት ደረጃ የአባላት ውሳኔ ገና አልተጠየቀም።
  • ሲጠየቅስ?
  • ሁኔታውን ዓይቼ እወስናለሁ።
  • ወይ ጉድ?
  • ምነው?
  • የራሳችሁን ሳትይዙ በአገር ደረጃ አልቸኮላችሁም?
  • የራሳችሁን ሳትይዙ?
  • እህ…?
  • ምንድን ያልያዝነው?
  • የወል እውነት!

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

የዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ባለሙያዎች ኮሚሽን ሪፖርት ምን ይዟል?

ለአሜሪካ ድምፅ አማርኛ ዝግጅት የስልክ አስተያየት የሰጡ አንድ የደንበጫ...

መንግሥት በአማራ ክልል ለወደሙ የአበባ እርሻዎች ድጋፍ እንዲያደርግ ተጠየቀ

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአማራ ክልል የተፈጠረው ግጭትና አለመረጋጋት በቢዝነስ...

አምናና ዘንድሮ!

እነሆ መስከረም ጠብቶ በአዲስ መንፈስ ተሞልተን መንገድ ጀምረናል። ‹‹አዲስ...

በሰጥቶ መቀበል መርህ መደራደርና ሰላም ማስፈን ለምን ያቅታል?

በያሲን ባህሩ አገር ግንባታ የትውልድን ትልቅና ታሪካዊ ኃላፊነት የሚጠይቅ ተግባር...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ ለሁለት ቀናት የተካሄደውን የፓርቲያቸውን የሥራ አስፈጻሚ ስብሰባ አጠናቀው ወደ ቢሯቸው ሲመለሱ ቢሯቸው ውስጥ አማካሪያቸው አንድ ጽሑፍ በተመስጦ እያነበበ አገኙት]

ምንድነው እንደዚህ መስጦ የያዘህ ጉዳይ? መጡ እንዴ ክቡር ሚኒስትር፣ የፓርቲው ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ያወጣውን መግለጫ እያነበብኩ ነው፡፡ ግን እኮ ፊትህ ላይ የመገረም ስሜት ይነበባል፡፡ አዎ፣ መግለጫው ላይ...

[ክቡር ሚኒስትሩ እየጠራ ያለውን ሞባይል ስልካቸውን ተመለከቱ፣ የህዳሴ ግድቡ ተደራዳሪ መሆናቸውን ሲያውቁ ስልኩን አነሱት]

ሃሎ... ጤና ይስልጥኝ ክቡር ሚኒስትር? ጤና ይስልጥልኝ ክቡር ተደራዳሪ... የጥረትዎን ፍሬ በማየትዎ እንኳን ደስ አለዎት፡፡ እንኳን አብሮ ደስ አለን፣ ምን ልታዘዝ ታዲያ? የውኃ ሙሌቱንና አጠቃላይ የግድቡን የግንባታ ሁኔታ...

[የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሩ ክቡር ሚኒስትር ሌሊቱን በእንቅልፍ ልባቸው በህልም እየተወራጩ ሳለ የሞባይል ስልካቸው ጥሪ አነቃቸው። አለቃቸው ስለነበሩ ስልኩን በፍጥነት አነሱት]

በሌሊት ስለደወልኩኝ ይቅርታ፡፡ ችግር የለውም ክቡር ሚኒስትር፣ ምን ልታዘዝ? አንድ የአውሮፓ ባለሥልጣን ነገ በጠዋት ወደ አዲስ አበባ ይገባል። እሺ። ሌሎች የመንግሥት አመራሮች ስላልቻሉ እርስዎ መንግሥትን ወክለው ቦሌ ኤርፖርት...