ለቀጣዩ በጀት ዓመት ከቀረበው 801.65 ቢሊዮን ብር አጠቃላይ በጀት ውስጥ 281 ቢሊዮን ብር የሚሆነው ያልተጠራ የበጀት ጉድለት መሆኑ ተገለጸ።
የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴ ዛሬ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረቡት የበጀት ሪፖርት እንደገለጹት ለ2016 ዓ.ም. በጀት ዓመት የቀረበው አጠቃላይ በጀት አብዛኛው ከአገር ውስጥ የገቢ ምንጮች የሚሸፈን ነው።
ነገር ግን ለበጀቱ መሸፈኛ ይገኛል ተብሎ በታቀደው አጠቃላይ ገቢና ወጪ ይሆናል በተባለው 801.65 ቢሊዮን ብር መካከል፣ 281 ቢሊዮን ብር ያልተጣራ የበጀት ጉደለት መሆኑን ተናግረዋል።
ይህ የበጀት ጉድለት የሚሸፈነውም ከአገር ውስጥና ከውጭ ብድር እንደሚሆን የጠቀሱት ሚኒስትሩ፣ ከአጠቃላይ የበጀት ጉድለቱ ውስጥ 39 ቢሊዮን ብር ከውጭ ብድር እንደሚሸፈን ተናግረዋል። የተቀረው 242 ቢሊዮን ብር ደግሞ ከአገር ውስጥ ብድር እንደሚሸፈን ገልጸዋል።
ይገኛል ተብሎ ከታቀደው የአገር ውስጥና የውጭ ብድር ውስጥ 53.7 ቢሊዮን ብር የሚሆነው ተመልሶ ለአገር ውስጥና ለውጭ ዋና ብድር ክፍያ የሚውል በመሆኑ፣ የበጀት ዓመት የተጣራ የበጀት ጉድለት 227 ቢሊዮን ብር እንደሚሆንና ይህም ከአጠቃላይ የአገር ምርት ያለው ድርሻ 21 በመቶ መሆኑን ተናግረዋል።
ለበጀት ጉድለቱ መሸፈኛ የሚሆነው አብዛኛው ብድር ከአገር ውስጥ ምንጮች የሚወሰድ ከመሆኑ አኳያ የዋጋ ንረት ሊያስከትል የሚችል ቢሆንም በዋጋ ንረት ላይ የጎላ ተጽዕኖ እንዳይፈጥር ብድሩ በግምጃ ቤት ሰነድና የመካከለኛ ዘመን ቦንድ በመሸጥ ለማግኘት መታቀዱን ገልጸዋል።