በኢትዮጵያ ውስጥ ከፍተኛ መጠን ያለው የገንዘብ እንቅስቃሴና ግብይት ከሚፈጸምባቸው ምርቶች መካከል ነዳጅ በቀዳሚነት የሚቀመጥ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ነዳጅ ድርጅት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ታደሰ ለሪፖርተር እንደገለጹትም፣ በየዓመቱ በአማካይ ከ200 ቢሊዮን ብር በላይ ግብይት የሚፈጸምበት ምርት ነው፡፡ ይህ የግብይት መጠን ከዓመት ዓመት እየጨመረ ሲሆን፣ ዘንድሮም በአሥራ አንድ ወር ተኩል ጊዜ ውስጥ ብቻ ከ225 ቢሊዮን ብር በላይ የነዳጅ ግብይት መፈጸሙን በምሳሌነት ጠቅሰዋል፡፡
ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ የሚወጣበት ይህ ምርት ግን በተለይ ከሥርጭት ጋር በተያያዘ ለብክነትና ለሕገወጥ ግብይት የተጋለጠ መሆኑ ሲነገር ቆይቷል፡፡ ወደ አገር የሚገባ የነዳጅ ምርት የዓለም ዋጋን መሠረት አድርጎ ግብይት እንዲፈጸምበት ከመወሰኑ ቀደም ብሎ ከ20 እስከ 30 በመቶ የአገሪቱ ነዳጅ በሕገወጥ መንገድ ወደ ውጭ እንደሚወጣ ይገመታል፡፡ ከዚህም ሌላ በተለያዩ መንገዶች ከማደያዎች ውጪ ነዳጅ በውድ ዋጋ እየተሸጠ መሆኑ በግብይት ሥርዓቱ ውስጥ የሚስተዋል ችግር ሆኖ ቆይቷል፡፡ ለዚህ ሕገወጥነት መስፋፋት አንዱና ዋነኛው ምክንያት ወደ አገር የሚገባውን ነዳጅ በአግባቡ የተፈለገበት ቦታ መድረስ አለመድረሱን ማረጋገጥ የሚቻልበት ጥብቅ መቆጣጠሪያ ዘዴ አለመኖሩ ነው፡፡
አቶ ታደሰም በዚህ ይስማማሉ፡፡ እስካሁን የነበረው አሠራር የነዳጅ ማደያዎች ምርቱን በአግባቡ ለተጠቃሚው በማቅረብ አለማቅረባቸውን የሚያረጋግጥ አለመሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ከጂቡቲ ወደብ ለአንድ ማደያ ተብሎ የሚላክ ነዳጅ ማደያው ደርሶ ስለመራገፉም ማረጋገጥ የሚቻልበት አሠራር ስለሌለ የተጫነው ነዳጅ በሕገወጥ መንገድ የሚሸጥበት ዕድል ሰፊ መሆኑን አውስተዋል፡፡
ይህንን የአገር ሀብት ከመጠበቅ አንፃር መንግሥት የነዳጅ ግብይትን በዲጂታል ክፍያ ሥርዓት ብቻ እንዲፈጸም ውሳኔ ከተላለፈ ወዲህ ግን በተወሰነ ደረጃ ከጂቡቲ የተጫነ ነዳጅ የተባለው ቦታ ስለመድረሱ ማረጋገጥ የሚቻልበትን ዕድል ፈጥሯል፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞ የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ባደረገው ጥናት ከጂቡቲ ወደ አገር የሚገባው የነዳጅ መጠን ቅናሽ ያሳየ ቢሆንም፣ በገበያው ውስጥ ግን ምንም ችግር ሳይኖር በቂ የሆነ ነዳጅ እየቀረበ ነው፡፡ ይህ የሚያሳየው ለእከሌ ነዳጅ ማደያ ተብሎ የሚጫን ነዳጅ ቦታው ሳይደርስ በጎን ይሸጥ እንደነበር ነው፡፡ የዲጂል የነዳጅ ክፍያ ሥርዓት መጀመር እንዲህ ያሉ ነገሮችን ጠቋሚ ሆኖ በመገኘቱ ቁጥጥሩን ለማጥበቅ መንግሥት የነዳጅ ኩባንያዎችና ማደያዎች ግብይታቸውን በዲጂታል የክፍያ ዘዴ ብቻ እንዲጠቀሙ የሚያስገድድ አዲስ ሥርዓት ሊዘረጋ ችሏል፡፡
ይህ በኢትዮ ቴሌኮም የበለፀገው ሥርዓት በአገሪቱ ውስጥ ያሉ የነዳጅ ኩባንያዎች ሁሉ ከሚቀጥለው ሳምንት ጀምሮ የሚተገበር ሆኖ በቅድሚያ ግን በአዲስ አበባና በሸገር ከተሞች ባሉ ወደ 160 በሚደርሱ ማደያዎች እንደሚጀምር አቶ ታደሰ ገልጸዋል፡፡ አዲሱ ሥርዓት በኩባንያዎችና በነዳጅ አዳዮች መካከል የነበረውን አሠራር ከመቀየሩም በላይ እያንዳንዱን ግብይታቸውን ለመቆጣጠር እንደሚያስችል አቶ ታደሰ አስረድተዋል፡፡ ይህ ውሳኔ በኢትዮጵያ ነዳጅ ድርጅት ቦርድ ተወስኖ ከሐምሌ 1 ቀን 2915 ዓ.ም. ጀምሮ ተግባራዊ እንደሚደረግም አቶ ታደሰ ገልጸዋል፡፡ ከእነዚህ ከተሞች ውጪ ባሉ በሁሉም ክልሎች ደግሞ በአንድ ወር ውስጥ የሚተገበር ይሆናል፡፡
‹‹ይህ የነዳጅ አቅርቦት ሥርዓት ብዙ ነገሮችን ይቀይራል፤›› ያሉት አቶ ታደሰ፣ ‹‹ከዚህ በፊት የነበረው የነዳጅ ሽያጭ ሥርዓት አንድ ነዳጅ ማደያ ነዳጅ ሲፈልግ መቼ እንዳዘዘና መቼ እንደሚፈልግ አይታወቅም ነበር፡፡ እስካሁን ሲካሄድ የነበረውም የነዳጅ ሽያጭ ጂቡቲ ላይ የነዳጅ ኩባንያዎች በሚያቀርቡት ጥያቄ መሠረት የሚላክ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ግን ጂቡቲ የነበረው የነዳጅ ሽያጭ ወደ አዲስ አበባ እንዲመጣ በማድረግ፣ አጠቃላይ ግብይቱ አዲስ በሚዘረጋው ሲስተም አማካይነት ከማዕከል ውሳኔ የሚጥበት ይሆናል፤›› ብለዋል፡፡
በዚህ ሲስተም መሠረት የነዳጅ ግዥ መፈጸም የሚፈልግ አንድ ነዳጅ ማደያ የሚፈልገውን ነዳጅ ለመግዛት መጀመርያ አቅራቢውን እንደሚጠይቅ፣ አቅራቢው ደግሞ የነዳጅ ማደያው ያዘዘውን የነዳጅ ግዥ ትዕዛዝ ለኢትዮጵያ ነዳጅ ድርጅት እንደሚያቀርብ ገልጸዋል፡፡ ማደያውም ሆነ ነዳጅ አቅራቢው የነዳጅ ግብይቱን ለመፈጸም የሚያቀርቡት ጥያቄ በሙሉ በተዘረጋው ሲስተም በዲጂታል የክፍያ ዘዴ ብቻ እንደሚያከናውን አስረድተዋል፡፡ የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ድርጅቶችም በሲስተሙ የተጠየቀውን የነዳጅ ግዥ ጥያቄ በማየት የነዳጅ ኩባንያው (አቅራቢው) በሒሳቡ ውስጥ በቂ የሆነ ገንዘብ መኖሩን በማረጋገጥ ነዳጁ እንዲጫን ይደርጋል ብለዋል፡፡
የነዳጅ ማደያውም ግብይቱን በቴሌብር ወይም በሲቢኢ ወይም በሌሎች የነዳጅ ክፍያ ሥርዓት በዘረጉ የፋይናንስ ተቋማት ሲያከናውን ብቻ የነዳጅ ግብይቱ እንዲፈጸምለት ገልጸዋል፡፡ ለዚህም ለእያንዳንዱ ማደያ የየራሱ ኮድ የሚሰጠው ሲሆን ተጠቃሚውም (ከማደያ የሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎች) በዚህ ኮድ ተጠቅመው የነዳጅ ግዥውን እንዲፈጽሙ እንደሚደረግ ገልጸዋል፡፡ በዚህ መንገድ የተደረጉ ሽያጮች በሙሉ በሲስተሙ በተዘጋጀው ማዕከላዊ ዳታ እንዲገቡ በማድረግ የእያንዳንዱ ኩባንያና ማደያ ሽያጭ በየዕለቱ የሚመዘገብ መሆኑን፣ ይህም በሕገወጥ መንገድ የሚሸጥ ነዳጅ እንዳይኖር ይከላከላል ተብሎ ታምኖበታል፡፡
ይህ ዓይነት ሥርዓት የተረከበው ነደጃ ሳያልቅበት አንድ ነዳጅ ማደያ የተረከበው ነዳጅ ሳያልቅበት አልቆብኛል ብሎ ቢያመለክት ሥርዓቱ የማይቀበለው መሆኑን አቶ ታደሰ ተናግረዋል፡፡ ተጨማሪ ነዳጅ ማግኘት የሚቻለው የተቀበለውን ነዳጅ ሸጦ ስለመጨረሱ ሥርዓቱ ሲያረጋግጥ ብቻ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡ ይህ ሲስተም ችግር ቢያጋጥም እንኳን መፍትሔ ተበጅቶለት የተሰናዳ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ አንድ ነዳጅ የጫነ ቦቴ መንገድ ላይ ችግር ቢገጥመው ፈቃድ ጠይቆ በቅርብ በሚያገኘው ነዳጅ ማደያ ሊገለብጥ የሚችልበት ዕድል እንደሚሰጥም ጠቁመዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ከጂቡቲ የተጫነው ነዳጅ ግዥውን ከፈጸመው የነዳጅ ማደያ ውጪ ነዳጁን መገልበጥ የተከለከለ ነው፡፡ ይህንን ሲስተም መዘርጋት ያስፈለገበት ዋናው ዓላማም ነዳጅ የት ገባ? የት ሄደ? የሚለውን በቀላሉ ለመቆጣጠር በመሆኑ በበርሜል ተሞልተው በኮንትራባንድ የሚወጡ የነዳጅ ምርቶችን ለመቆጣጠር እንደሚያስችል አቶ ታደሰ ተናግረዋል፡፡ ይህ ሥርዓት ከዚህ በኋላ ነዳጅ በኮንተሮባንድ ሊወጣ ሲል ተያዘ የሚለውን ዜና ያስቀራል የሚል እምነት አላቸው፡፡
እያንዳንዱ ነዳጅ ኩባንያ ምን ያህል ተረክቦ ምን ያህል ሸጠ የሚለውን ሁሉ በማዕከል ለመቆጣጠር የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ከዚህ በኋላ የነዳጅ ኩባንያዎችም ሆኑ ነዳጅ ማደያዎች አዲስ በተዘረጋው የግብይት ሥርዓት ተጠቅመው ግብይታቸውን በዲጂታል የክፍያ ዘዴ ማከናወን ካልቻሉ ምንም ዓይነት ነዳጅ እንደማያገኙ ገልጸዋል፡፡
ከነዳጅ ግብይት ጋር በተያያዘ ለጀነሬተርና መሰል አገልግሎቶች የሚሰጥ ነዳጅን በተመለከተም አዲስ አሠራር መዘርጋቱን አቶ ታደሰ ገልጸዋል፡፡ ነዳጅ በበርሜል መቅዳት የሚቻል ቢሆንም፣ ይህ አገልግሎት ሲሰጥ ግብይቱ በዲጂታል የክፍያ ሥርዓት መፈጸም ይኖርበታል ብለዋል፡፡
የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ ለጀነሬተር አገልግሎት ነዳጅ ለሚፈልጉ ድርጅቶች አስፈላጊውን የነዳጅ መጠን ጠቅሶ ፈቃድ እንደሚሰጥም ጠቁመዋል፡፡ ‹‹ይህንን ፈቃድ በመያዝ ካልሆነ በቀር ሽያጩ አይካሄድም፡፡ ይህም ሽያጭ ቢሆን የዲጂታል ክፍያዎችን መጠቀም ይሻል፡፡ ንግድ ቢሮው የሚሰጠውም ፈቃድ ቢሆን ቁጥጥር የሚደረግበት እንጂ በዘፈቀደ ፈቃዱን አይሰጥም፤›› ብለዋል፡፡
ይህ ሲስተም የነዳጅ ፍጆታን ለማወቅ የሚያስችል መሆኑን የገለጹት አቶ ታደሰ፣ እስካሁን ትክክለኛ መረጃ እንደሌለም ጠቅሰዋል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ 1.4 ሚሊዮን ተሽከርካሪ አለ እየተባለ ምን ያህሉ የቤንዚን፣ ምን ያህሉ የናፍጣ ተጠቃሚ መሆናቸውን የሚገልጽ መረጃ እንኳን እንደሌለ ተናግረዋል፡፡ አሁን የዲጂታል ክፍያ ሥርዓቱ ከጀመረ ወዲህ ይህንን መረጃ ለማሰባሰብና ለመለየት መቻሉን ገልጸዋል፡፡
በዚህ መረጃ መሠረት በአዲስ አበባ ከተማ ካሉ ተሽከርካሪዎች ከ60 በመቶ በላይ የሚሆነው የቤንዚን ተጠቃሚ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡ በመሆኑም የአዲሱ ሲስተም ሌላው ጠቀሜታ ትክክለኛ አገራዊ የነዳጅ ፍጆታን በአግባቡ ለመለየት እንደሚያስችል ጠቁመዋል፡፡ ይህ ሲስተም በትክክል እንዲተገበር ለነዳጅ ማደያዎች በቂ ሥልጠና የተሰጠ ሲሆን የኩባንያዎቹ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች በተግባር ሥልጠናው እየተሰጣቸው መሆኑን አቶ ታደሰ ገልጸዋል፡፡
ይህንን ሲስተም ሥራ ላይ ለመተግበር እንዲቻል አስፈላጊው ዝግጀት ሁሉ የተጠናቀቀ ሲሆን የነዳጅ ኩባንያዎቹ በሙሉ በኔትዎርክ እንዲተሳሰሩ መደረጉንም አቶ ታደሰ ተናግረዋል፡፡ ሥልጠናዎቸውንም እየወሰዱ በመሆኑ በተተቀሰው ጊዜ በአዲስ አበባና በሸገር ከተሞች ሥራው እንደሚተገበር፣ አንድ ወር ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ ደግሞ በክልል ከተሞች ሠልጠናው ተሰጥቶ ሁሉም የነዳጅ ኩባንያዎችና ማደያዎች በዚህ ሲስተም እንዲገቡ ይደረጋል ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ድርጅት አዲስ በዘረጋው ሲስተም ዙሪያ የነዳጅ ኩባንያዎችና ማደያዎች እንዴት ተቀብለውታል ለሚለው ጥያቄ አቶ ታደሰ ሲመልሱ፣ ‹‹ደስተኛ ላይሆኑ ይችላ ብለዋል፡፡ ነገር ግን ነዳጅ የሕዝብ ሀብት ነው፡፡ አገሪቱ ከፍተኛ የሆነ የውጭ ምንዛሪ የምታፈስበት ስለሆነ የ40 ኩባንዎች ጉዳይ ብቻ ባለመሆኑ እያንዳንዱ ሰው ከዚህ አገልግሎት መጠቀም አለበት፡፡ ይህንን ለማድረግ ደግሞ እንዲህ ያሉ አሠራሮች ተገቢ ናቸው፤›› ብለዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ 45 የሚሆኑ የነዳጅ ኩባንያዎች አሉ፡፡ እነዚህ የነዳጅ ኩባንያዎች በሥራቸው የሚገኙ የነዳጅ ማደያዎች ቁጥር ደግሞ 1502 ናቸው፡፡ ተመዝግበው በሥራ ላይ ያሉት 1,359 ሲሆኑ፣ በአዲሱ ሲስተም ውስጥ ተካትተው አገልግሎቱን የሚሰጡ ማደያዎች ደግሞ 1,235 ናቸው፡፡
ሥራ ላይ ከሚገኙ የነዳጅ ማደያዎች ውስጥ በርካታ ማደያዎች የሚገኙት በኦሮሚያ ሲሆን አማራና አዲስ አበባ ተከታይ ናቸው፡፡ አነስተኛ ቁጥር ያለው የነዳጅ ማደያ ያለው በጋምቤላ ክልል ሲሆን በክልሉ ያሉ ማደያዎች 12 ብቻ መሆናቸው ታውቋል፡፡