ከሦስት ዓመት በፊት ከአፀደ ሥጋ የተለዩት ሠዓሊና መምህር የአየር ኃይል ሻምበል ለማ ጉያ (1921-2013)፣ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነትን በሥነ ጥበባዊ ገጽታ፣ ብሂልን ከባህል አዛምደው በጥበብ ገበታ ለዓለም ያስተዋወቁ ናቸው፡፡ በሥዕል የለሙ፣ ሥዕልን ያለሙ ሥዕልን በጉያቸው ይዘው ለሰባት አሠርታት አቅራቢያ የዘለቁ ናቸው፡፡
በተለይ ከሌሎች ጠቢባን የሚለያቸው በፍየል ቆዳ ላይ የሚነድፏቸው ምስለ አካሎች (ፖርትሬት) በግዝፈት አንግሷቸዋል፡፡ ይህንኑ ጥበባቸውን ተከትሎ ሥልታቸው ‹‹ለሚዝም›› የሚል ጥበባዊ አጠራርን ተጎናጽፏል፡፡

ለሚዝም ማለትም ‹‹ለማነት››ን ያጎናፀፋቸው፣ በጥበብ ሰው ታደለ ገድሌ (ዶ/ር) አገላለጽ፣ ከሠዓልያን ሁሉ ለየት ያለ የአሣሣል ጥበብን መከተላቸው ነው፡፡ በዋነኛነት ትኩረት የሚያደርጉትም ቪዡዋል አርት በሚባለው የአሣሣል ጥበብ ማለትም የሚታይ፣ የሚዳሰስ፣ የሚጨበጥ ሆኖ የሚጠቀሙበት ቁሳቁስ የፍየል ወይም የበሬ ቆዳ፣ የውኃ ቀለም፣ የዘይት ቀለም፣ ከሰል (ቻርኮል) ነው ሲሉም ያክሉታል፡፡
እኚህ በኩር (ሌጀንድ) ለማ ጉያ በ2013 ዓ.ም. ባረፉና ሽኝት በተደረገላቸው ጊዜ ‹‹የጥበበኛው ታሪክ ይቀጥላል፡፡ የአባቴን ታሪክና ገድል ለማስቀጠል ዝግጁ ነኝ፤›› በማለት ቤተሰባቸውን ወክላ የሐዘን መግለጫዋን ያሰማቸው ሠዓሊት ሰላማዊት ጉያ ቃሏን በተግባር ገልጣዋለች፡፡ ከቤተሰቦቿ ጋር ሁና ነቢብን ወደ ገቢር ቀይራዋለች፡፡
በኢትዮጵያ የኪነ ጥበብ መድረክ የማይረሳ አሻራ ያሳረፉትን ጥበባዊ ትሩፋት ለማስቀጠል፣ የለማ ጉያ ፋውንዴሽንን በአዲስ አበባ አቋቁማና በኃላፊነት እየመራች ነው፡፡
‹‹የለማ ጉያ ፋውንዴሽን ከዋና ተልዕኮቹ አንዱ የሰው ልጆችን በሥነ ጥበብ መልሶ ማስተሳሰር ነው፤›› የምትለው ሰላም እንዳሰመረችው፣ ‹‹በሥነ ጥበብ አማካይነት የኢትዮጵያን ባህላቸውን የሚወክሉ የተለያዩ ቅርሶችና ኪናዊ ሥራዎችን በማካፈል፣ በዓለም ደረጃ ለመገናኘት እንፈልጋለን፡፡ ሁሉ ሰው ማን መሆኑን እንዲረዳ ለማድረግም እንዲሁ፡፡››
‹‹የለማ ጉያ ፋውንዴሽን አንዱ ዋና ተልዕኮ የሰው ልጅን በኪነ ጥበብ መልሶ ማገናኘት ነው፤›› የምትለው ሰላም፣ ታዳጊ አርቲስቶችን በአካታች ፕሮግራሞቹ ለመደገፍ ያለመ ነው። ተማሪዎች የለሚዝም ሥልት ትምህርት የሚያገኙበትና ልዩ አካሄዱን ለትውልድ የሚያራምዱበት ማሠልጠኛ ተቋምም በመቋቋም ላይ መሆኑንም አውስታለች፡፡
ፋውንዴሽኑ የአባቷን ውርስ ከማስቀጠል ጎን ለጎን ጋለሪዎችንና ሙዚየሞችን ማቋቋምና መደገፍ እንደሆነ ገልጻለች።
ፋውንዴሽኑ በኢትዮጵያ ብሔረሰቦች የተለያዩ ባህሎችና ጥበቦች ላይ ጥናት ያደርጋል።
ሕፃናት ሐሳባቸውን እንዲገልጹ የዲጂታል ጥበብና በሥነ ጥበብ ሥልጠና፣ በመጻሕፍት ላይ ውይይት፣ አዋቂዎች የሕይወትና የዕውቀት ልምዳቸውን የሚያጋሩበት መድረክ የማዘጋጀት ትልምም አለው፡፡
የለማ ጉያ ፋውንዴሽን የቴክኖሎጂ ዕድገቶችን ተከትሎ በቀጣይነት የሚሻሻሉ ዲጂታል ጥበብን ጨምሮ የተለያዩ የጥበብ መድረኮችን ይጠቀማል። በሁሉም የዕድሜ ክልል ላሉ ተማሪዎች ሥነ ጥበብን መፍጠር የሚችሉበትና በምረቃቸው ጊዜ ሥራዎችን በጋለሪ በዓውደ ርዕይ የሚያቀርቡበት መንገድ ሥልጠና ይሰጣል።
ፋውንዴሽኑ ከሁለት ሳምንት በፊት ከተባበሩት ዓረብ ኢምሬትስ ኤምባሲ ጋር በመተባበር ዓውደ ርዕይ አዘጋጅቶ ነበር፡፡ ይህም የተከናወነው ‹‹ኪነ ጥበብንና ባህልን ማስተዋወቅና መጠበቅ፤›› በሚል መሪ ቃል ሲሆን፣ በኢትዮጵያና በተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስና መካከል መልካም ግንኙነትን ለመፍጠር የባህልና ቅርሶችን ለማሳየትና ለኢትዮጵያውያን አርቲስቶች የሥልጠናና ኤግዚቢሽን ዕድሎችን ለመስጠት ያለመ ነው።
በቦሌ የአፍሪካ ጎዳና አካባቢ የሚገኘው ፋውንዴሽኑ የበኩር ሠዓሊ ለማ ጉያ ሥራዎችን በዓውደ ርዕይ ለማሳየት ዕቅድ አለው፡፡
ከሥነ ጥበብ ትሩፋታቸው
ልሂቅ ሥነ ጥበበኛ ለማ ገጸ ታሪካቸው እንደሚያሳየው፣ በቆዳ ላይ መሣል የጀመሩት በኅብረተሰብዓዊት ጊዜያዊ ወታደራዊ አስተዳደር ደርግ ዘመን ጀምሮ መሆኑንና በመጀመርያ በፍየል ቆዳ ላይ የሣሉትም የቀድሞው የዚምባቡዌ ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤን ሲሆን፣ ከኢትዮጵያ ነገሥታትና መሪዎች መካከል ከአፄ ቴዎድሮስና አፄ ዮሐንስ እስከ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ድረስ የነበሩትን ሠርተዋል። ሥዕላቱ በቢሾፍቱ ከተማ በገነቡት አፍሪካ አርት ጋለሪ/ሙዚየማቸው ውስጥ ይገኛሉ፡፡ የየብሔረሰቡን የአለባበስና የአኗኗር ዘይቤን የሚገልጹ በተለይም የኦሮሞን ሕዝብ ትውፊትን የሚያጎሉ ሥዕሎችን በመሣል ይታወቃሉ፡፡፡
በ65 ዓመታት የጥበብ ጉዞአቸው ያፈሩት የጥበብ ሥራ 10,000 እንደሚደርስ ይወሳል፡፡ ሥዕሎቻቸውን ከአገር ውስጥ እስከ ውጭ አገር አሜሪካን ጨምሮ በተለያዩ አገሮች በዓውደ ርዕይ አሳይተዋል፡፡
ሥዕሎቻቸውን በግል በአስመራ፣ በአዲስ አበባና በደብረ ዘይት በዓውደ ርዕይ ለዕይታ ከማቅረባቸው ባሻገር በውጭ አገሮች በኅብረት ካቀረቡቧቸው መካከል የናይጄሪያ መዲና ሌጎስና የሴኔጋሏ ዳካር ይገኙባቸዋል፡፡ በልጃቸው ሠዓሊት ነፃነት ለማ አማካይነትም በአሜሪካ ኒው ዮርክ ከተማ ያዘጋጁትን ዓውደ ርዕይ የከፈቱት በወቅቱ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ ኮፊ አናን ናቸው፡፡
ነገረ ቋንጣ
ስመጥር ካደረጓቸው ሥራዎቻቸው መካከል በግንባር ቀደምነት የምትጠቀሰው ‹‹ቋንጣ›› የተሰኘችው ናት፡፡ የዚህችን ሥዕል አንድምታ ጅማ ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ በሰጣቸው ጊዜ እንደሚከተለው አቅርቦታል፡-
‹‹በተለይ በሕዝብ ዘንድ ትልቅ አድናቆትን የሰጠውና በሹማምንት ልዩ ትርጉምና አቃቂር በማውጣት ከየወቅቱ አዛዦች ጋር እንዲላተም ካስደረጉት የበኩር ሥራዎች ሳትጠቀስ የማታልፈው ቋንጣ የምትባለው ሥዕል ነች፡፡ ቋንጣ የአፍሪካን የሀብት ምዝበራ ወይም ሙስናን ፍንትው አድርጋ ታሳያለች፡፡
‹‹በአንድ ቤት ጓዳ ውስጥ ቋንጣ በቀይ መልኩ ተዘልዝሎ ይታያል፡፡ ድመቶች ቋንጣውን መዥርጠው ለመብላት ይታገላሉ፡፡ ጠፍሩ አልጋ ላይ በድምሩ አራት ድመቶች ወጥተዋል፡፡ አንደኛው ግድግዳው በጥፍሩ ቧጥጦ ያወርዳል፡፡ አንዱ ቁመቱ አልደርስ ብሎታል፡፡ አንደኛው ደግሞ በእጁ የገባለትን እንደያዘ ሌላ ለማግኘት አንጋጧል፡፡ በእነርሱ ግፊያና ግርግር ጮጮ ሙሉ ወተት ተደፍቷል፡፡
‹‹የወተቱ አወራረድ የዓባይ ፋፏቴን ተመስሎ ቀርቧል፡፡ የመጨረሻው ድመት የሸረሪት ድር የወረሰውን ድብኝት አፍጦ በሸረፋት ድር የተያዘውን ነፍሳት ለመያዝ ያስባል፡፡ ይህ ሁሉ ሲደረግ ግን ከአልጋው ሥር አይጥ እሸት በቆሎ ትቀረጥፋለች፡፡ ይህንን ሥዕል ስትመለከቱት የራሳችሁ ፍርድ ትሰጣላችሁ፡፡››
ቢቢሲ በአንድ ወቅት ስለ ቋንጣውና ስለድመቶቹ እንዲሁም ስለወተቱ ሠዓሊ ለማ ጉያ እንዲያብራሩለት ጠይቋቸው፣ ሥዕሉን ከሠሩት 42 ዓመታት ማስቆጠሩንና በዚህ ሥራቸውም አፍሪካና ችግሮቿን ያሳዩበት እንደሆነ እንደሚከተለው ገልጸውለት ነበር።
‹‹የአፍሪካ መሪዎችን በድመቶቹ መስለው የአገራቸውን ሀብት በሙስና ሲመዘብሩ፣ በአልጋው ሥር የሚታዩት የአኅጉሪቷ ጠላት አይጦች ደግሞ የአፍሪካን ሀብት ሲቀራመቱ ይታያሉ፡፡ እየፈሰሰ ያለው ወተትም ያለጥቅም ለዘመናት የሚፈሱት የአፍሪካ ወንዞች ምሳሌ ነው።››
ሥነ ጠቢቡ ለማ በኦሮሚያ ክልል ያለውን የሃይማኖቶች መቻቻል፣ ኢሬቻን፣ የተፈጥሮ ሀብትና የሕዝቡን አኗኗር የሚያሳይ ‹‹እናት›› ሌላኛዋ ዕውቅ ሥራቸው ስትሆን ከኢሬቻ ከክብረ በዓል ጋር ተያያዥነት ያላቸውን ሌሎች ባህላዊ ተግባራትን የሚሳየው ‹‹ኦዳ››ም ተጠቃሽ ነው፡፡
ሻምበል ለማ ጉያ፣ እንደ ሌሎቹ የአካባቢው ተመሳሳይ ልጆች ተለምዶአዊው የአባታዊ የሥራ ፈለግ ውርስ ሳይሆን፣ ያልተለመደውን የወ/ሮ ማሬ ጎበናን የዕደ ጥበብ ብቃት ነቅሶ በመያዝ ከዕቃ ዕቃ ጨዋታው በላይና ከሚያዩት የመገልገያ መሣሪያ የሸክላ ውጤቶች ውጪ ከዕድሜያቸው በላይ ወደሠሯቸው ቅርፃ ቅርፆች እንደነበረ ግለ ታሪካቸው ያሳያል፡፡
ልሂቁ ሥነ ጥበበኛ ሻምበል ለማ ጉያ ሦስት ሴቶች (ትዕግሥት፣ ነፃነት፣ ሰላማዊት) እና ሁለት ወንድ ልጆችን (ዳዊት፣ ደረጀ) አፍርተዋል፡፡ አምስቱም ልጆቻቸው የአባታቸውን ፈለግ የተከተሉ ሥነ ጠቢባን ናቸው፡፡ የልጆቻቸው አጎቶችም አሰፋ ጉያ እና ቱሉ ጉያ እንደዚሁ በሠዓሊነትና በደራሲነት ይታወቃሉ፡፡
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አለ የሥነ ጥበብና ዲዛይን ትምህርት ቤት ዲን ሠዓሊ አገኘሁ እንግዳ ሥነ ጠቢቡን እንዲህ ገለጹ፡- ‹‹ሻምበል ለማ ጉያ አንጋፋ የሥነ ጥበብ ሰው ነበሩ፡፡ የሥዕል ማስተማሪያ መጽሐፋቸው ‹ሥዕል ያለ አስተማሪ› ብዙዎቻችንን የሥነ ጥበብ ‹ሀ ሁ› ያስቆጠረ፣ ተሰጧችንን ፈልገን እንደናገኝ የረዳ ነበር፡፡ ይህን የማይረሳ ውለታቸውን የኢትዮጵያ ዘመናዊ ሥነ ጥበብና ጠቢባኑ ሲያስታውሱት ይኖራሉ፡፡ ለሙያው ታምኖና በትጋት ሳያቋርጡ ሠርቶ ስምና ዝና ማትረፍ እጅግ ከባድ በሆነበት በኛ ሙያ፣ ይህን ድልና ገድል መቀዳጀታቸው ያስመሠግናቸዋል፡፡ ጠንካራ ሙያተኛ ነበሩ፡፡››