- ወረርሽኙ በ69 ወረዳዎች መስፋፋቱ ተጠቁሟል
በአራት ክልሎች የተከሰተው የኮሌራ በሽታ ወረርሽኝ በፍጥነት እንደ አዲስ እየተዛመተ መሆኑንና ከ13,700 ሰዎች መያዛቸውን፣ እንዲሁም 179 ሰዎች መሞታቸውን የኢትዮጵያ የማኅረበሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ማስታወቁን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የሰብዓዊ ዕርዳታ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት (UNOCHA) ባወጣው ሪፖርት አስታወቀ፡፡
ትናንት ማክሰኞ ሐምሌ 18 ቀን 2015 ዓ.ም. በወጣው ሪፖርት እንዳመላከተው፣ የወረርሽኙ ሥርጭት ምጣኔ 1.3 የደረሰ ሲሆን፣ ይህም ከአንድ መብለጥ የለበትም የሚባለውን ምጣኔ አልፏል፡፡
ወረርሽኙ የተከሰተው በአማራ፣ በኦሮሚያ፣ በደቡብ ሶማሌና በሲዳማ በሚገኙ 69 ወረዳዎች ውስጥ ነው፡፡ በአማራ ክልል ክልል ባለፈው ሳምንት የኮሌራ ተጠቂዎች ቁጥር 2,150 ደርሷል፡፡ ይህም በምዕራብ ጎንደር ዞን ቋራ በርሜሉ ቅዱስ ጊዮርጊስ ፀበልን ለመጎብኘት በሥፍራው የተገኙ ሰዎች መብዛትና ከሱዳን ከሚመጡ ስደተኞች ጋር የተያያዘ መሆኑ በሪፖርቱ ተመላክቷል፡፡
ባለፉት ሳምንታት ሪፖርተር ከጤና ሚኒስቴር፣ ከኢንስቲትዩቱና ከጤና ቢሮዎች በጉዳዩ ላይ መረጃ ለማግኘት ጥረት ሲያደርግ የቆየ ሲሆን፣ ኃላፊዎቹ መረጃ ለመስጠት ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል፡፡
ከኮሌራ በተጨማሪ የኩፍኝ፣ የወባና ሌሎች ወረርሽኝ በሽታዎች እየተስፋፉ መሆኑን ሪፖርቱ ጠቅሷል፡፡