- ክቡር ሚኒስትር ከማኅበረሰባችን በተለያየ መልኩ ከፍተኛ ተቃውሞ እየደረሰብን መሆኑ ሥጋት ፈጥሮብኛል።
- አትሥጋ… መፍትሔ መፈለግ እንጂ መሥጋት ጥሩ አይደለም፡፡
- ለመፍትሔውም እኮ አቅም ያስፈልጋል።
- እንዴት? አቅም የለንም እያልክ ነው?
- ክቡር ሚኒስትር ነገሩ የተለመደው የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲዎች ጫና ሳይሆን ከፍተኛ የኢኮኖሚ አቅም የሚጠይቅ የማኅበረሰብ ተቃውሞ ነው።
- እንደለመድከው የኑሮ ውድነቱ ከቁጥጥር ውጪ እየወጣ ነው ልትል ነው አይደል?
- እሱ አንደኛው ነው ነገር ግን ሌላም ችግር ተከስቷል።
- የምን ችግር?
- የአፈር ማዳበሪያ ችግር።
- የማዳበሪያ ችግር ዓለም አቀፍ እንጂ በእኛ ሀገር ብቻ የተከሰተ አለመሆኑን አታውቅም?
- ቢሆንም ክቡር ሚኒስትር ይህንን ለአርሶ አደሩ ማስረዳት አስቸጋሪ ነው።
- ለምን?
- መሬቱን አባልጋችሁ ዛሬ ማዳበሪያ የለም ማለት አትችሉም ብሎ እያመጸ ነው።
- እያመጸ ነው ማለት?
- በተለያዩ አካባቢዎች ሰለማዊ ሠልፍ እየወጣ ሲሆን በአንዳንድ አካባቢዎች ደግሞ…
- እ… በአንዳንድ አካባቢዎች ምን?
- የማዳበሪያ መጋዘኖችን በመስበር መቆጣጠርና ያለውን ክምችት በራሱ መንገድ መከፋፈል ጀምሯል።
- ከአርሶ አደሩ ያልተለመደ ፀባይ ነው።
- ክቡር ሚኒስትር ይህንን ችግር ቶሎ መፍትሔ መስጠት ካልቻልን አደገኛ ልምምድ ነው። ለመንግሥት ሥልጣንም አስጊ ነው።
- የመንግሥትን ሥልጣን ለምን ያሠጋል?
- ክቡር ሚኒስትር በዚህ ሁኔታ ማለቴ ከከተማ እስከ ገጠሩ አርሶ አደር ተቃውሞ እያነሳብን ቀጣዩን ምርጫ እናሸንፋለን ብለው ያስባሉ?
- አትጠራጠር!
- እንዴት?
- እኛ የዚህን አገር የፖለቲካ ውድድር ጣሪያ ከፍ አድርገነዋልና አትሥጋ፣ የሚደረስብን የለም።
- እንዴት?
- እኛ ያደረግነውን መፈጸም የሚችል ተፎካካሪ የለም።
- ተፎካካሪ ፓርቲዎች ማድረግ የማይችሉት ምን የተለየ ነገር እኛ አደረግን።
- ለባለቤቱ ስላማይታይ እንጂ ብዙ የተለዩ ነገሮችን አድርገናል።
- ለምሳሌ ምን?
- የደካሞችን መኖሪያ ቤት ማደስ።
- እ…
- ችግኝ መትከል
- እ….
- ማዕድ ማጋራት።
- ክቡር ሚኒስትር አርሶ አደሩ እኮ የተቆጣው አሥግቶት ነው።
- ምን አሥግቶት?
- ማዕድ አጋሩኝ ማለት።
[ክቡር ሚኒስትሩ በአገሪቱ የተከሰተው ከፍተኛ የዋጋ ግሽበትን ለመቆጣጠር ያለመ ውይይት ከኢኮኖሚ ጉዳዮች አማካሪያቸው ጋር እያደረጉ ነው]
- የዋጋ ግሽበትን ለመቆጣጠርና ወደ ነጠላ አኃዝ ለማውረድ ለሕዝብ ቃል ብንገባም ግሽበቱ ተባብሶ ቀጥሏል።
- እውነት ነው ክቡር ሚኒስትር። ግሽበቱ ተባብሶ ቀጥሏል!
- ተባብሶ መቀጠሉን እንድታረጋግጥልኝ አይደለም የጠራሁህ?
- ገብቶኛል ክቡር ሚኒስትር። በፍጥነት መፍትሔ ካልሰጠነው ነገሮች ከቁጥጥራችን ውጪ ሊወጡ ይችላሉ፡፡
- እሱን እንድትነግረኝ አይደለም የጠራሁህ!
- ታዲያ ለምንድነው ክቡር ሚኒስትር?
- መሠረታዊ ሸቀጦች ላይ የተጣሉ ቀረጥና ታክስ፣ በተለይም ቫት ቢነሳ ግሽበቱን መቆጣጠር ይቻላል ባልከው የመፍትሔ ሐሳብ መሠረት እንዲነሳ ተደረጓል ነገር ግን ግሽበቱ ተባብሶ ቀጥሏል።
- እውነት ነው ክቡር ሚኒስትር። የመፍትሔ ሐሳቡ ይሠራል ብለን ቀረጥና ታክስ ብናነሳም የሸቀጦች ዋጋ ሊወርድ አልቻለም። እንደውም ተባብሶ ቀጥሏል።
- እሱን እንድታረጋግጥልኝ አይደለም የጠራሁህ!
- እሺ ለምንድነው?
- ያቀረብከው ሐሳብ መፍትሔ ያመጣል ባልከው መሠረት በስድስት ወራት ውስጥ 18 ቢሊዮን ብር የሚሆን ቀረጥና ታክስ እንዳይሰበሰብ ተደርጎ ምርቶች እንዲገቡ ተደርጓል ነገር ግን የዋጋ ግሽበቱ ተባብሶ ቀጠለ እንጂ አልተረጋጋም።
- እውነት ነው ክቡር ሚኒስትር። እንደተባለው 18 ቢሊዮን ብር የሚሆን ቀረጥና ታክስ እንዳይከፈል ቢደረግም የዋጋ ግሽበቱ ቀጥሏል።
- እኮ ይህን ያህል ገቢ ቀሪ ተደርጎ እንዴት ዋጋ ማረጋጋት አልተቻለም?
- እሱ የእኛም ጥያቄ ነው ክቡር ሚኒስትር። ነገር ግን የምጠረጥረው ነገር አለ።
- ምንድነው የጠረጠርከው?
- እኛ ቀረጥና ታክስ እንዳይከፈል ብንወስንም አስመጪዎቹ ግን ይከፍሉ እንደነበር እጠረጥራለሁ። ለነገሩ ጥርጣሬ ብቻ አይደለም።
- እንዴት? ይከፍሉ ነበር እያልክ ነው?
- ክቡር ሚኒስትር እኛ ቀረጥና ታክስ እንዲነሳ ብንወስንም ማዕከላዊ ባንኩ የዶላር ምንዛሪ ተመንን በየቀኑ ከፍ እያደረገ ስለነበር ቀረጥና ታክስ መነሳቱ ትርጉም አልነበረውም።
- እንዴት? ምን አገናኘው?
- አስመጪዎቹ ዶላር መንዝረው የዘይትና ሌሎች ሸቀጦች ግዥ ፈጽመው ሸቀጡ አገር ውስጥ ሲደርስ የዶላር ምንዛሪ ተመን በከፍተኛ ደረጃ ጨምሮ ያገኙታል።
- እኮ ምን አገናኘው? ያስመጡትን ዘይት በዶላር አይሸጡ?
- በዶላር ቢሸጡትማ ጉዳት አይገጥማቸውም ነበር።
- ምን እያልክ ነው?
- በመቶ ዶላር የገዙት ዘይት አዲስ አበባ ሲደርስ የመቶ ዶላር የብር ምንዛሪ አሻቅቦ ይጠብቃቸዋል። አሱ ላይ ትርፍ ጨምረው ዘይቱን ይሸጡታል። ስለዚህ የዘይትን ዋጋ ያስወደዱት አስመጪዎች ብቻ ናቸው ማለት አስቸጋሪ ነው።
- አሃ… መንግሥት የዕለት ፍጆታ ሸቀጦችን በውጭ ምንዛሪ እያስገባ በጎን በኩል ደግሞ የብር የመግዛት አቅምን ማዳከም መቀጠሉ ትክክል አይደለም እያልክ ነው? አሁን እያልክ ያለኸው ገብቶኛል መሰለኝ፣ አይደል?
- ልክ ነዎት ክቡር ሚኒስትር። ችግሩን በትክልል ተረድተውታል። በአጠቃላይ ከውጭ የሚገባ ዘይት ላይ መንግሥት ሳያውቀው ዋጋ እየጨመረ ነበር ማለት ይቻላል።
- እህ… እና ምን ማድረግ ይሻላል ትላለህ?
- የአጭር ጊዜ መፍትሔው የብር ምንዛሪን የማዳከም ሒደት ለጊዜው እንዲቆም ማድረግ ነው። ሌላው …
- ሌላው የረዥም ጊዜ መፍትሔ ነው።
- ምንድነው?
- ቢያንስ የዕለት ፍጆታ ሸቀጦችን በአገር ውስጥ ማምረት ወይም መተካት ካልቻልን ከችግሩ በዛላቂነት መውጣት አንችልም። የዋጋ ግሽበት የአገሪቱ አዙሪት ሆኖ ይቀጥላል።