ዓለምን አንዴ በድርቅ ሌላ ጊዜ በጎርፍ ማዕበልና በሰደድ እሳት እንድትናጥ በማድረግ በብርቱ እየፈተነ ያለ ጉዳይ በመሆኑ የበለፀጉ አገሮችን ጨምሮ ሁሉም አገሮች በሚባል ደረጃ አካባቢን ዋነኛ አጀንዳቸው በማድረግ በየወቅቱ በስፋት ይወያዩበታል።
ኃያላን የሚባሉት አገሮች በግዙፍ ኢንዱስትሪዎቻቸው አማካይነት የሚለቁት ካርበን እየታየ ላለው የአየር ንብረት ለውጥ የአንበሳውን ድርሻ ይይዛሉ።
ምንም እንኳን ያላደጉ አገሮች የካርበን ልቀታቸው ዝቅተኛ እንደሆነ ቢነገርም ‹‹አይጥ በበላ ዳዋ ተመታ›› እንዲሉ ችግሩ በርትቶባቸው አንዴ በጎርፍ ሌላ ጊዜ በድርቅ ሲጎሳቆሉ ይስተዋላሉ፡፡ በተለይ ደግሞ የአየር ንብረት ለውጥ በሚያስከትለው ጦስ ወቅቱን ያልጠበቀ ዝናብ በመጣሉ ዜጎች ለረሃብ እንዲጋለጡ ምክንያት መሆኑ ይነገራል።
ችግሩን ለመፍታት የዓለም መሪዎች በየዘመኑ በመሰባሰብ በጉዳዩ ይመክራሉ፣ ይዘክራሉ፡፡ ይሁን እንጅ ጠብ የሚልና ተጨባጭ መፍትሔ ሳያፈልቁ ይልቁንስ ችግሩ ከዓመት ወደ ዓመት እየተስፋፋ ከፊሉን በከባድ አውሎ ነፋስ በጎርፍና በመሳሰሉት ክስተቶች ሲያናውጣቸው በሌላ በኩል ደግሞ በድርቅና በሰደድ እሳት ሲገርፋቸው ማየት የተለመደ ሆኗል፡፡

ተከላ በክረምቱ
ከረሃብና ከእርስ በርስ ጦርነት ጋር በተያያዘ ስሟ የማይጠፋው አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ እዚህ ግባ የሚባል ድርሻ ባይኖራትም የችግሩ ተካፋይ ከመሆን አልወጣችም፡፡
ኢትዮጵያም የችግሩ ገፈጥ ቀማሽ መሆኗ አልቀረም፡፡ ይሁን እንጂ የችግሩ ዋነኛ ጠንሳሾች የበለፀጉት አገሮች ናቸው በማለት አገሪቱ የራሷን አስተዋጽኦ ከማድረግ አልቦዘነችም።
ይልቁንስ ለአየር ንብረት ለውጥ መፍትሔ ይሆናል የተባለውን የአረንጓዴ አሻራ በማስቀመጥ ጉልህ አስተዋጽኦ እያደረገች መሆኑ እየታየ ነው።
ምንም እንኳን ችግኝ መትከል የኢትዮጵያ ቅድመ ልማድ እንደሆነ ቢነገርም ካለፉት አሠርት ወዲህ በመንግሥት እንዲሁም በተለያዩ ተቋማት በኩል በቢሊዮን የሚቆጠሩ ችግኞች ተተክለዋል፡፡
ከተተከሉት ችግኞች መካከል ምን ያህሉ ፀድቀው ለተፈለገው ዓላማ እየዋሉ ነው የሚለው በጥናት ተረጋግጦ ይፋ ባይደረግም፣ ነገር ግን በየዓመቱ ክረምት በገባ ቁጥር በየሸንተረሩ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ችግኞች ይሰፍራሉ፡፡
ለአብነት ከ2011 ዓ.ም. እስከ 2014 ዓ.ም ባካሄደችው የመጀመርያ የችግኝ ተከላ መርሐ ግብርም 25 ቢሊየን ችግኞችን መትከሏን ከግብርና ሚኒስቴር የወጡ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ዘንድሮ 6.5 ቢሊዮን ችግኝ ለመትከል ታቅዶ እየተሠራ ነው፡፡
መንግሥት በበኩሉ የችግኝ ተከላ ፕሮግራምን አቅዶ ቢንቀሳቀስም መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶቾ የራሳቸውን አሻራ በማስቀመጥ ማኅበራዊ ኃላፊነታቸውን ሲወጡ ይስተዋላሉ፡፡ ለዚህም ቀዳሚው ተጠቃሽ በእንጦጦ የተፈጥሮ ፓርክ አቋቁሞ ላለፉት 28 ዓመትና አገር በቀል ዛፍን በማልማት ላይ የሚገኘው የኢትዮጵያ ቅርስ ባለአደራ ማኅበር ነው፡፡
በተለይ የአገር በቀል ችግኞችን ለማስፋፋት በአንኮበር፣ በደሴና በድሬዳዋ አካባቢ በስፋት እየሠሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ደኖችን ማልማት የካርቦን ልቀትን ከመቀነስ ባሻገር የኢኮቱሪዝም ቦታዎችን በማብዛት ለአገር ገቢን ከማስገኘት አንፃር ትልቅ ፋይዳ አለው ብለዋል ዋና ሥራ አስኪያጁ፡፡
ማኅበሩ በየዓመቱ በርካታ ችግኞችን ይተክላል ያሉት አቶ መቆያ፣ በተከላ ወቅት ደግሞ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት ይሳተፋሉ ብለዋል፡፡ ለዚህም ማሳያ ፀሐይ ባንክ ይጠቀሳል፡፡
ፀሐይ ባንክ አንደኛ ዓመት የምሥረታ በዓሉን ምክንያት በማድረግ ሐምሌ 22 ቀን 2015 ዓ.ም. ከኢትዮጵያ ቅርስ ባለአደራ ማኅበር ጋር በመሆን በእንጦጦ አገር በቀል ችግኞችን ተክሏል።
የተራቆቱ መሬቶችን አረንጓደ በማልበስ የተፈጥሮ ሀብቶችን መጠበቅ የባንኩ አንዱ ዓላማ ነው፡፡ ይህንንም በተግባር ለማሳየት የባንኩ ሠራተኞች አገር በቀል ችግኞችን በመትከል ማኅበራዊ ኃላፊነታቸውን በመወጣት ላይ እንደሆኑ የገለጹት የባንኩ ማርኬቲንግ ኮርፖሬት ኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ አበባው ዘውዴ ናቸው።
ችግኞችን መትከል ብቻ ሳይሆን አድገው ለተፈለገው ዓላማ እንዲውሉ በጋራ እንደሚሠሩ በመናገር ጭምር በዕለቱ የተተከሉ ችግኞች በእንክብካቤ ጉድለት ካልፀደቁ በመጭው ታኅሣሥ መጥታችሁ ልትጠይቁን ትችላላችሁ ሲሉ ስለ ችግኞቹ መፅደቅ የመሰከሩት ደግሞ የኢትዮጵያ ቅርስ ባለ አደራ ማኅበር ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ መቆያ ማሞ ናቸው፡፡
ማኅበሩ ባለፉት ሦስት አሠርታት የአገር በቀል ችግኞችን በማልማት እየሠራ እንደሚገኝ የተናገሩ ሲሆን አገር በቀል ችግኞች ላይ ትኩረት ያደረገው ደግሞ ከሚሰጡት አገልግሎት አንፃር እንደሆነ ነው ያስረዱት፡፡
አገር በቀል ዛፎች ለጣውላነት፣ ለመድኃኒት ቅመማና ለሌሎች በርካታ የምርምር አገልግሎቶች ተፈላጊነታቸው ከፍተኛ ነው የሚሉት አቶ መቆያ ሌላው አገር በቀል ዛፎች ላይ ትኩረቱን ያደረገው ችግኞችን ለማራባት የሚወስደው ጊዜና ቦታ ሰፊ በመሆኑ እንዲሁም አገር በቀል ችግኝ አንድ ጊዜ ከጠፋ እንደሌላው መተካት የማይቻል በመሆኑ ነው ሲሉ አብራርተዋል፡፡
አገር በቀል ችግኞችን ከማፍላት ጀምሮ አገልግሎት ለመስጠት ዝግጁ የሚሆኑበት ጊዜ በጣም ረዥም በመሆኑ ከጥቅም ጋር አያይዞ ለሚሠራ ሰው ተመራጭ እንደማይሆኑ ገልጸው እነዚህ የተፈጥሮ ቅርሶች እንዳይጠፉ የኢትዮጵያ ቅርስ ባለ አደራ ማኅበር የአገር በቀል ችግኞችን በራሱ የችግኝ ጣቢያ በማፍላትና ለትምህርት ቤቶች እንዲሁም ለተለያዩ ተቋማት በማከፋፈል እንዲተክሉ በማድረግ ላይ መሆኑን አክለዋል፡፡
እንጦጦ አንዱ የአገር በቀል ችግኝ የዘር መገኛ እንዲሆንና የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ ማኅበሩ የራሱን አሻራ እያስቀመጠ መሆኑን አብራርተዋል፡፡ ይህም ወደፊት በአገር በቀል ተክሎች ላይ ሰፋፊ ጥናት ለሚያካሂዱ ማንኛውም ተቋም አመቺ እንዲሆን፣ እንዲሁም ተማሪዎችና ወጣቶች በአገራቸው ውስጥ ስለሚገኙ አገር በቀል ዕፀዋት እንዲያውቁና እንዲንከባከቡ ለማድረግ እንደሚረዳ ነው የተናገሩት፡፡
‹‹ችግኝን ያለ አግባብ መትከል የሰው ልጅን አፍኖ እንደመግደል ይቆጠራል፤›› ያሉት አቶ መቆያ፣ ስለ ችግኝ አተካከልና ክብካቤ ለተማሪዎች በየትምህርት ቤቱ፣ በክበባትና በሌሎች መንገዶች ግንዛቤ እየተፈጠረ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
የአገር በቀል ዛፎች በብዛት ተራራማ ቦታ ስለሚስማማቸው በብዛት በእነዚህ አካባቢዎች እንደሚሠራ ያወሱት ኃላፊው፣ ማኅበሩ ዘንድሮ ትኩረት አድርጎ እየሠራባቸው ካሉ አገር በቀል ችግኞች መካከል እንደ ኮሶ፣ ወይራ፣ ጥቁር እንጨት፣ ግራርና የመሳሰሉት ይገኙበታል ብለዋል፡፡
በአንኮበር ዛጎ አካባቢ ከዚህ ወጣ ባለ መንገድ ለአርሶ አደሩ ቶሎ ደርሰው ጥቅም ሊሰጡ የሚችሉ እንደ ቡና፣ ፓፓዬ፣ ሙዝና የመሳሰሉትን ተክሎች በማሠራጨት ላይ እንደሆኑ የተናገሩት አቶ መቆያ፣ ከወረዳው ተራራማ ቦታ በመቀበል ከአካባቢው ጋር ተዛማጅ የሆኑትን አገር በቀል ዝርያዎችን በመትከል ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
በየአካባቢው የሚተከሉ ችግኞች ከመትከል በዘለለ ለታለመላቸው ዓላማ ይውሉ ዘንድ የሚጠብቁ ሰዎችንና የችግኝ ጣቢያ ባለሙያዎችን በመመደብ ክብካቤ እንደሚደረግላቸው ነው የተናገሩት፡፡