ትውልድና ዕድገቱ በኦሮሚያ ክልል አርሲ ዞን ሙኔሳ ወረዳ ነው፡፡ በ1976 ዓ.ም. የአትሌቲክስ ውድድር ወረዳውን ወክሎ በ400፣ በ800 እና 1,500 ሜትር ርቀቶች በቆጂ በተሰናዳው ሻምፒዮና ተካፈለ፡፡ በ1977 የወረዳውን ሻምፒዮና በድል በመወጣቱ፣ አሰላ ጭላሎ በተካሄደው የአርሲ ምርጥ ሻምፒዮና ለመካፈል በቃ፡፡ በጊዜው እምብዛም አትሌቲክስ ትኩረት ባልተሰጠበት ወቅት፣ ሁሉንም ውድድሮች በድል ተወጥቶ፣ በ1977 ዓ.ም. በጅማ ከተማ ተሰናድቶ በነበረው የኢትዮጵያ ሻምፒዮና አርሲን መወከል መቻሉ ይነገራል፡፡
በ1978 ዓ.ም. ለፌዴራል ማረሚያ ቤት በፖሊስነት የተቀጠረው ሁሴን እስከ 1983 ዓ.ም. የክለቡ አትሌት ሆኖ በመካከለኛ ርቀቶች ክለቡን አገልግሏል፡፡
ከአትሌትነት ወደ አሠልጣኝነት
ረዳት ኮሚሽነር ሁሴን፣ የአሠልጣኝነት ሕይወት የጀመሩት ከቀድሞ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ብሔራዊ ቡድን ዋና አሠልጣኝ ወልደ መስቀል ኮስትሬ (ዶ/ር) ጋር በ1984 ዓ.ም. ከተገናኙ በኋላ ነው፡፡
በዚያው ዓመት የ1992 የባርሴሎና ኦሊምፒክ ጨዋታዎች ጀምሮ ወደ አሠልጣኝነት የገቡት ሁሴን፣ ላለፉት 31 ዓመታት የፌዴራል ማረሚያ ቤት አትሌቲክስ ክለብና የብሔራዊ ቡድን አሠልጣኝ በመሆን እያገለገሉ ናቸው፡፡ በዓለም አትሌቲክስ፣ በኦሊምፒክና በተለያዩ ዓለም አቀፍ አትሌቲክስ መድረኮች፣ በተለይ በ10 ሺሕና በ5 ሺሕ ሜትር ስኬታማ መሆን ከቻሉ ስማቸው ደምቆ ከተጻፈላቸው ጥቂት አሠልጣኞች መካከል አንዱ ናቸው፡፡
ሁሴን በ12 የዓለም ሻምፒዮናዎች፣ ስድስት ኦሊምፒኮች፣ ስድስት የመላ አፍሪካ ጨዋታዎች ባስመዘገቡት ውጤት ምክንያት ‹‹ሜዳሊያ አዳኙ›› የሚል ቅጽል ስም አግኝተዋል፡፡
‹‹ለሥልጠና ያለኝ ፍቅር፣ ፍላጎት፣ ቅንነት፣ ዕውቀትና ታማኝነት ለዚህ አብቅተውኛል፤›› በማለት ረዳት ኮሚሽነር ሁሴን ስለ ስኬታቸው ምስጢር ለሪፖርተር ያስረዳሉ፡፡
ለሁለት ዓመታት ወጥ በሆነ አቋም ማሠልጠን ከባድ በሆነበት በዚህ ወቅት፣ ለ31 ዓመታት የትራክ ላይ ፈርጦችን ማፍራታቸውን የሚጠቅሱት ሁሴን፣ በተለያዩ የአትሌቲክስ መድረኮች በልጆቻቸው አማካይነት ከ400 በላይ ሜዳሊያዎችን መሰብሰብ ችለዋል፡፡ በዘመናት ጉዞ ላስመዘገቡት ስኬትም መሥርያ ቤታቸው፣ በቅርቡ የረዳት ኮሚሽነርነት ማዕረግ አልብሷቸዋል፡፡
ሁሴን የዓለም አትሌቲክስ (በቀድሞ አጠራሩ አይኤኤኤፍ) የአንደኛ ደረጃ የአሠልጣኝነት ትምህርት፣ የአገር ውስጥ አንደኛና ሁለተኛ ደረጃ አሠልጣኝነት ሥልጠና፣ የሕክምና ትምህርት፣ የአመጋገብ ሥርዓትና የጂምናዚየም አጫጭር ትምህርቶችን በመውሰድ ዕውቀታቸውን ማሳደግ ችለዋል፡፡
ከዚህም ባሻገር በ2007 ዓ.ም. ከኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ በስፖርት ሳይንስ የመጀመርያ ዲግሪያቸውን አግኝተዋል፡፡
የረዳት ኮሚሽነር ሁሴን ሼቦ የኦሊምፒክ ተሳትፎ
በ2000 በሲድኒ፣ በ2004 በአቴንስ፣ በ2008 በቤጂንግ በተካሄዱት የኦሊምፒክ ጨዋታዎች የኢትዮጵያ አትሌቲክስን በምክትል አሠልጣኝነት መምራት ችለዋል፡፡
የ2012 የለንደን፣ የ2016 የሪዮ እና የ2020 የቶኪዮ ኦሊምፒክ ጨዋታዎችን በዋና አሠልጣኝነት ቡድኑን መምራት ከቻሉት መካከል ግንባር ቀደሙ ናቸው፡፡
በእነዚህም ኦሊምፒኮች ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በ5 ሺሕና 10 ሺሕ ሜትር ላሳኳችው ሜዳሊያዎች የአሠልጣኝ ሁሴን አስተዋጽኦ የጎላ ነው፡፡ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድን በተነሳ ቁጥር አብሮ ስማቸው ሳይነሳ የማይቀረው የሜዳሊያ አዳኙ ረዳት ኮሚሽነር ሁሴን፣ ሰባተኛው የኦሊምፒክ ተሳትፏቸው በ2024 የፓሪስ ኦሊምፒክ ይጠበቃል፡፡
የኢትዮጵያ የረዥም ርቀት ውጤት ከዘመን ዘመን በቅብብሎሽ እየቀጠለ የመጣ ሲሆን ከደራርቱ ቱሉ፣ ከኃይሌ ገብረ ሥላሴና ከቀነኒሳ በቀለ ተሻገሮ ዛሬ በእነ ሰለሞን ባረጋና በነለተሰንበት ግደይ ተተክቷል፡፡ በዚህ ሒደት ውስጥ የአሠልጣኝ ሁሴን አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነው፡፡
የአሠልጣኙ የዓለም ሻምፒዮና ተሳትፎ
ዘንድሮ በሃንጋሪ ቡዳፔስት ለሚከናወነው 19ኛ የዓለም ሻምፒዮና የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድን የ10 ሺሕ ሜትር ተወዳዳሪዎች አሠልጣኝ በመሆን ቡድኑ ዝግጅቱን ከጀመረ ሰነባብቷል፡፡ ሁሌም ከስታዲየም የማይጠፉት አሠልጣኝ ሁሴን፣ ዘንድሮ ለ12ኛ ጊዜ የዓለም ሻምፒዮና ተሳትፎ ያደርጋሉ፡፡
እ.ኤ.አ. 2007 የአቴንስ ዓለም ሻምፒዮና በብሔራዊ ቡድን አሠልጣኝነት ያመሩ ሲሆን በኦሳካ፣ ሄልሲንኪ፣ ፓሪስና ፉካካን ጨምሮ በ12 የዓለም ሻምፒዮናዎች ቡድን መምራት ችለዋል፡፡ ከነዚህም መካከል ለሄልሲንኪው የዓለም ሻምፒዮና ልዩ ስሜት እንዳለቸው ይገልጻሉ፡፡
‹‹ለእኔ ከሁሉም በላይ በጣም የምደሰትበት የዓለም ሻምፒዮና በሴቶች 5 ሺሕ እና ሴቶች 10 ሺሕ በተመሳሳይ ተከታትለው የገቡበት፣ እንዲሁም በወንዶች 10 ሺሕ ሜትር ቀነኒሳ በቀለና ስለሺ ስህን ተከታትለው የገቡበት የማልረሳው የዓለም ሻምፒዮና ነው፤›› በማለት ረዳት ኮሚሽነር ሁሴን ጊዜውን ያስታውሳሉ፡፡
በጊዜው አሠልጣኝ ወልደ መስቀል ኮስትሬ (ዶ/ር) ጡረታ መውጣታቸውን ተከትሎ አሠልጣኝ ቶሎሳ ቆቱና ሁሴን ነበሩ ቡድኑን ይመሩት የነበረው፡፡
አሠልጣኝ ሁሴን ከሄልሰንኪ የዓለም ሻምፒዮና በዘለለ፣ ዓምና በአሜሪካ ኦሪጎን የተከናወነው የዓለም ሻምፒዮና ሌላው ትልቅ ቦታ ይሰጡታል፡፡ ኢትዮጵያ በኦሪጎን 4 ወርቅ፣ 4 የብርና ሁለት የነሐስ በድምሩ 10 ሜዳሊያዎችን በመሰብሰብ አዘጋጇን አሜሪካ ተከትላ ከዓለም ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ያጠናቀቀችበት ስኬታማው ሻምፒዮን ነበር፡፡
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ዕድገት
የኢትዮጵያ ታላላቅ አትሌቶች በተለያዩ የትራክና የጎዳና ውድድሮች ላይ በርካታ ድሎችን መጎናፀፍ ችለዋል፡፡ ሆኖም ቀድሞ አትሌቶች በረዥም ርቀቶች የነበራቸው ተሳትፎና አሁን ካለው ጋር ሲነፃፀር ተመጣጣኝ አይደለም የሚሉ አሉ፡፡
በአንፃሩ አሠልጣኝ ሁሴን በርካታ አትሌቶችን ማፍራት መቀጠሉን ጠቅሰው፣ ከፍተኛ ዕድገት እያሳየ መምጣቱን ያነሳሉ፡፡ ‹‹ውጤት በሜዳሊያ ብቻ አይለካም፤›› የሚሉት አሠልጣኝ ሁሴን፣ የዘመኑ አትሌቶች የውድድር ሰዓት ከማሻሻል በዘለለ፣ ለአገር ከፍተኛ ኢኮኖሚ መፍጠር እየቻሉ መምጣታቸውን ያብራራሉ፡፡
‹‹በዓለም አቀፍ ደረጃ በሁለቱም ፆታ የውድድር ሰዓቶች ተሻሽለዋል፡፡ በርካታ አዳዲስ አትሌቶች እየተተኩ ነው፣ ስኬታማም ናቸው፡፡ ከውጤቱ ባሻገር ደግሞ ከውጭ በሚያስገቡት ምንዛሪ የአገሪቱን ኢኮኖሚ እያንቀሳቀሱ ነው፤›› ሲሉ ያብራራሉ፡፡
አትሌቶቹ ከውጭ በሚያገኙት የውጭ ምንዛሪ በተለያዩ ኢንቨስትመንቶች መሰማራትን ባህል ማድረጋቸውንም ያነሳሉ፡፡
በአሥር ሺሕ ሜትር ምሩፅ ይፍጠር፣ ኃይሌ ገብረ ሥላሴ እንዲሁም ቀነኒሳ በቀለ ይገቡበት የነበረው ሰዓት በሒደት እየተሻሻለ መምጣቱን የሚያነሱት ረዳት ኮሚሽነሩ፣ በምሳሌነትም ‹‹በ10 ሺሕ ሴቶች፣ 29፡31 የነበረው ዛሬ 29፡06 እንዲሁም 5 ሺሕ ሜትር ሴቶች 14፡30 የነበረው 14፡04 ተሻሽሏል፤›› በማለት ዕድገቱን ያስረዳሉ፡፡ የቴክኖሎጂዎች ማደግ በአትሌቲክሱ ላይ የራሱ አስተዋጽኦ ማሳደሩንም በማከል፡፡
‹‹የአትሌቲክስ ውጤት ተለዋዋጭ ነው፤›› ብለው የሚጠቅሱት አሠልጣኝ ሁሴን፣ በየዘመኑ ውጤቱ ከአገር አገር ይዘዋወራል በማለት ይገልጻሉ፡፡
የአትሌቲክስ ውጤትና የተሰጠው ትኩረት በአሠልጣኙ ዕይታ
አትሌቲክሱ በኢትዮጵያ ‹‹በእጅ የያዙት ወርቅ…›› ነው የሚሉት አሠልጣኙ፣ ቢለፉበት ከክብር፣ ከሜዳሊያና ከዝና በላይ ከፍተኛ የኢኮኖሚ አቅም መሆን እንደሚችል ያነሳሉ፡፡
በአንፃሩ መንግሥት ለአትሌቲክሱ ትኩረት ባለመስጠቱ ምክንያት የሚፈለገው ደረጃ ላይ መድረስ እንዳልተቻለ ይጠቀሳል፡፡ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድን በተለያዩ መድረኮች ድል ሲያደርግ፣ ከመንግሥት የሚደረግለት አቀባበል ዝቅተኛ መሆንና አትሌቶች በከፍተኛ ደረጃ የልምምድ ሥፍራ ዕጦት እየተፈተኑ መሆኑ የአትሌቲክሱ እንቅፋት ሆኖ እንደቀጠል ረዳት ኮሚሽነሩ ያስረዳሉ፡፡
‹‹ከውጤት በኋላ በመንግሥት ደረጃ የሚሰጠው ሽልማት አሠልጣኞችን ታሳቢ ያላደረገና አንዱን ከአንዱ የሚያበላልጥ ነው፤›› በማለት ረዳት ኮሚሽነሩ ይጠቁማሉ፡፡
በከፍተኛ የልምምድ ቦታ ዕጦት ታጅቦ ልምምዱን እያደረገ የሚገኘው ብሔራዊ ቡድን፣ ከቀናት በኋላ በሃንጋሪ ቡዳፔስት በሚጀመረው የዓለም ሻምፒዮን ይካፈላል፡፡ ረዳት ኮሚሽነር ሁሴንም፣ የ10 ሺሕ ሜትር ተወዳዳሪዎችን ይዘው ይጓዛሉ፡፡ በሻምፒዮናው ‹‹ስንት ወርቅ ያሳካሉ?›› የሚለው ከቀናት በኋላ የሚታይና ምላሽ የሚያገኝ ይሆናል፡፡