በመላው አፍሪካም ሆነ በሌላው አህጉር የሚገኙ የአትሌቲክስ ደጋፊዎች ፊታቸውን 19ኛውን የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናን ወዳዘጋጀችው የሃንጋሪ ዋና ከተማ ቡዳፔስት አዙረዋል።
ይኼው የቡዳፔስቱ 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ትናንትና ነሐሴ 13 ቀን 2015 ዓ.ም. ተጀምሯል፡፡ እስከ ነሐሴ 21 ቀን ድረስ በአጠቃላይ 49 ውድድሮች በብሔራዊ አትሌቲክስ ማዕከል ይካሄዳሉ።
ዓርብ ምሽት ማተሚያ ቤት በመግባታችን ትናንት በተደረገው በሴቶች 10 ሺሕ ሜትር ፍፃሜ ኢትዮጵያ በብቸኝነት አራት አትሌቶችን ያወዳደረችው፣ የዓምናውን ሻምፒዮና በለተሰንበት ግደይ አማካይነት በማሸነፏ ነው፡፡
ዓምና በኦሪገን በተካሄደው ውድድር ኢትዮጵያና ኬንያ በሜዳሊያ ሠንጠረዥ 2ኛ እና 4ኛ ሆነው ሲያጠናቅቁ፣ ሌሎች የአፍሪካ አገሮች ግን በተወሰነ ደረጃ ውጤት አስመዝግበዋል፡፡
በአጠቃላይ ከአፍሪካ ሰባት አገሮች 28 ሜዳሊያዎች ያገኙ ሲሆን ሞሮኮ፣ ናይጄሪያና ዑጋንዳ ከወርቃማዎቹ ከኢትዮጵያና ኬንያ ጋር በመቀላቀል ቢያንስ አንድ አንድ ወርቅ አግኝተዋል።
ዓምና በኦሪገን በ1500 ሜ በሁለተኛነት ያጠናቀቀችው ጉዳፍ ፀጋይ በ5000 ሜትር ያጠለቀችውን ወርቅ ዳግም መጨበጥ ትፈልጋለች፡፡
ጉዳፍ አሁን ትኩረቷን በረዥም ርቀት ላይ ያደረገች ስትሆን፣ የዘንድሮውን ውድድር አስመልክታም ‹‹በድጋሚ የዓለም ሻምፒዮናን ማሸነፍ እፈልጋለሁ፤›› ስትል ተናግራለች።
የዓምናዋ የ10,000 ሜትር ሻምፒዮኗ ለተሰንበት ግደይም ሌላ ድል በርቀቱ ለማስመዝገብ አልማለች፡፡ በመክፈቻው ቀን የ3000 ሜትር ወንዶች መሠናክልና የ1500 ሜትር ሴቶች ማጣሪያ ውድድሮች ተከናውነዋል፡፡
ዛሬ እሑድ ነሐሴ 14 ቀን በሁለቱም ፆታ የ1500 ሜትር ግማሽ ፍፃሜና የ10 ሺሕ ሜትር ወንዶች ፍፃሜ ውድድሮች ይከናወናሉ፡፡ በወንዶች በሪሁ አረጋዊ፣ ሰለሞን ባረጋና ይስማው ድሉ የሚወዳደሩ ሲሆን፣ ታደሰ ወርቁ በተጠባባቂነት ተይዟል፡፡
ኢትዮጵያ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናው በ5000 ሜትር ሐጎስ ገብረ ሕይወት፣ ዮሚፍ ቀጄልቻና ጥላሁን ኃይሌ የሚወዳደሩ ሲሆን በሪሁ አረጋዊ ተጠባባቂ ነው፡፡
በሴቶች የዓምናዋ አሸናፊ ጉዳፍ ፀጋይ፣ እጅጋየሁ ታዬ፣ መዲና ኢሳና ፍሬወይኒ ኃይሉ የሚወዳደሩ ሲሆን ለተሰንበት ተጠባባቂ ሆናለች፡፡
የሴቶች 5000 ሜትር ማጣሪያ ረቡዕ ነሐሴ 17 ቀን፣ የወንዶች 5000 ሜትር ማጣሪያ ደግሞ ሐሙስ ነሐሴ 18 ቀን ተከናውኖ ፍፃሜውን በሻምፒዮናው መዝጊያ ነሐሴ 21 ቀን ይሆናል፡፡
የኢትዮጵያ ብርቱ ተፎካካሪዎች የኬንያና የዑጋንዳ አትሌቶች እንደሚሆኑ ይጠበቃል፡፡ ኬንያዊቷ የመካከለኛ የረዥም ርቀቶች ባለ ክብረ ወሰኗ ፌይዝ ኪፒይገን፣ እንዲሁም ኔዘርላንዳዊቷ ሲፋን ሐሰን ኢትዮጵያውያንን አትሌቶችን ሊፈታተኑ እንደሚችሉ ተዘግቧል፡፡
በቤጂንግና በሞስኮ የዓለም ሻምፒዮናዎች፣ በሪዮ ኦሊምፒክ፣ እንዲሁም በአገር አቋራጭ ውድድሮች ባለ ድሉ ሐጎስ ገብረ ሕይወት በ5000 ሜትር፣ የአሸናፊነት ግምት ካገኙ መካከል ይገኛል፡፡
በአንፃሩ ኢትዮጵያውያንን ይፎካከራል ተብሎ የተገመተው የቶኪዮ ኦሊምፒክ ባለ ወርቁ ዑጋንዳዊው ጆሹዋ ቺፕቲጌ በጉዳት ምክንያት ከውድድሩ ውጪ ቢሆንም፣ በአውሮፓ የ1500 እና 3000 ሜትር ርቀቶች ምርጥ አትሌት የሆነው ኖርዌያዊ ጃኮብ እንግቢርሰን ፈታኝ ሊሆን እንደሚችል ተገምቷል፡፡
በ3000 መሠናክል የዓለም ክብረ ወሰን ባለቤቱ ኢትዮጵያዊው ለሜቻ ግርማና ራሱን ‹‹የመሠናክል ንጉሥ›› እያለ ከሚጠራው የቶኪዮ ኦሊምፒክ ባለወርቁ ሞሮኮዊ ሱፍያነ ኤል ባካሊ የሚያደርጉት የፍፃሜ ፉክክር ከወዲሁ ተጠባቂ ሆኗል፡፡
ሞሮካዊው የ27 ዓመት አትሌት ላለፉት 15 ዓመታት የቆየውን የኬንያ የበላይነት በማቆሙና ከመስከረም 2014 ዓ.ም. ጀምሮ በርቀቱ ሳይሸነፍ ሃንጋሪ መድረሱም ተዘግቧል፡፡
ለሜቻ ግርማ ኦሊምፒክን ጨምሮ በሁለት ውድድሮች በኤል ባካሊ በመረታቱ በብር ሜዳሊያ መወሰኑ ይታወሳል፡፡
ይሁን እንጂ የ22 ዓመቱ ሯጭ ባለፈው ሰኔ ወር ማንነቱን በፓሪስ 7፡52.11 በሆነ ጊዜ በመሮጥ በማሸነፍ ብቻ ሳይሆን የዓለምን ክብረ ወሰን በመስበር ነግሷል፡፡
የ20 ዓመት ኬንያዊ ሳይሞን ኮችም በ3000 ሜትር መሠናክል ለአገሩ ተስፋን ያሰነቀ ሆኗል፡፡ ዘንድሮ በዓለም ከለሜቻ ግርማና ኤል ባካሊን በመቀጠል ሦስተኛው ፈጣን ጊዜን ይዟል፡፡
ኢትዮጵያ በዘንድሮው ሻምፒዮና ብሔራዊ ቡድኗን መርተው ቡዳፔስት የተገኙት አራት የዓምና ሻምፒዮኖቹ በማራቶን ጎተይቶም ገብረሥላሴና ታምራት ቶላ፣ በ5000 ሜትርና በ10000 ሜትር ጉዳፍ ፀጋይና ለተሰንበት ግደይ ናቸው፡፡
የኢትዮጵያ ድሎች
የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በሃንጋሪ ብሔራዊ አትሌቲክስ ማዕከል እየተካሄደ ያለው ለ19ኛ ጊዜ ነው። ኢትዮጵያ በሁሉም ያለፉ 18 ሻምፒዮናዎች ተሳትፋለች። ብሔራዊ ቡድኗ እስካሁን 33 ወርቅ፣ 34 ብር፣ 28 ነሐስ ሜዳሊዎችን ሰብስቧል፡፡ ሦስት አትሌቶች – ቀነኒሳ በቀለ (5)፡ ጥሩነሽ ዲባባ (4)፡ ኃይሌ ገብረሥላሴ (4) – ከጠቅላላ 33 ወርቅ ሜዳሊያዎች 13 አስገኝተዋል፡፡
ከ202 አገሮች የመጡ ከ2100 በላይ አትሌቶች ለዘጠኝ ቀናት በቡዳፔስት የከተሙ ሲሆን በዓለም ደረጃ ከአንድ ቢሊዮን በላይ ተመልካቾች ውድድሮቹን በቴሌቪዥን ይከታተሉታል ተብሏል።